12/10/2022
#አሳፋራችሁናል #አሳዝናችሁናል
የዐማራ ማኅበረሰብ ልጁን የሚያስተምረው አፈር እየገፋ፣ አፈር እንደመሰለ ነው። እናቶች ልጆቻቸውን የሚያስተምሩት ለወፍጮ የሰገዱበት ጉልበታቸው መጅ ሆኖ፤ መጅ የያዙበት እጃቸው መጅ አብቅሎ፣ አብስሎ ለማብላት በጭስ ዓይናቸው እያለቀስ የተጨናበሰ ህይወት እየገፉ ነው ልጆቻቸውን የሚያስተምሩት። ድሮ እናቴ የቤት ሥራ ለመሥራት ሳመሽ ከጎኔ ቁጭ ብላ አብረኝ ታመሽ ነበር፣ ከሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ከምኝታዬ ቀስቅሳ "ልጄ ዛሬ አታነብም" ትለኝ ነበር። እናቴ ሳትማር እንደዚህ ነው ያስተማረችኝ፤ እህል ሽጣ ብር እየላከች ነው ያስተማረችኝ። ይህ የአብዛኛዎቹ እናቶች ሁኔታ ነው፣ በየሁሉም ቤት አለ።
እናቶች ብጫቂ ቀሚስ ለብሰው፣ ጀርባ በሚያጎብጥ ነገርግን ከእጅ ወዳፍ በማያልፍ መራራ ሕይወት እየተሰቃዩ ልጆቻቸውን ለማስተማር የማይከፍሉት መሰዋእትነት የለም። ልጆቻቸው ተምረው ሲመረቁ እንኳን የሚያርሱትን በሬ ከማረድ ወደኋላ አይሉም።
የእነዚህን ወላጆች ህልም "አልፈተንም" ብሎ ማጨልም ከነውር በላይ ትልቅ ወንጀል ነው። የእነዚህ ሚስኪን አርሶአደሮች ቅስም መስበር፤ ልፋታቸውን ከንቱ ማስቀረት ነው። የተማሪዎች ድርጊት በራሳቸው አንገት ላይ ሸምቀቆ አስገብተው እራሳቸውን እንዳጠፉ ነው የምቆጥረው። አፈር እየገፉ ያስተማሩ ቤተሰቦችን ማሳዘን ነው።