04/05/2023
የሥራ ዕድል ፈጠራ የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ቅንጅት እንደሚፈልግ ተገለፀ
በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሥራ፣ ሥራ ስምሪት እና ገበያ ዘርፍ ከ15 ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ፣ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ፣ ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ እና ከአነስተኛ ብድርና ቁጠባ ተቋማት ማህበር ተወካዮች ጋር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራን በፌደራል ደረጃ የሚያስተባብር ፣ የሚደግፍ እና የሚከታተል አደረጃጀት ለመፍጠር የሚያስችል ውይይት አካሂዷል፡፡
የአደረጃጀቱን ዓላማ እና አስፈላጊነት በተመለከተ ማብራሪያ የሰጡት በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሥራ፣ ሥራ ስምሪት እና ገበያ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ ንጉሡ ጥላሁን በመቀናጀት እና በመተባበር ባለመሥራት የሚስተዋሉትን ችግሮች በመፍታት ሥራውን በአግባቡ ለመምራት እና ለማስተባበር ተቀናጅቶ መስራቱ አስፈላጊ ሆኗል ብለዋል፡፡
በሀገራችን ማክሮ ኢኮኖሚ ትልቅ ጉዳይ የሆነውን የሥራ ዕድል ፈጠራ በተመለከተ የሚፈጠረው የጋራ ቅንጅት ጠንካራ አደረጃጀት ይሆናል ያሉት ክቡር አቶ ንጉሡ የሥራ ዕድል ፈጠራ ተግባር በአንድ ተቋም አደረጃጀት ተጀምሮ የሚያልቅ እና የሚመራ ባለመሆኑ ሁሉንም ባለድርሻ አካላት በማካተት በአዲስ መልክ ለተሻለ ውጤት መስራት አስፈላጊ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
የሥራ ዕድል ፈጠራ በኢትዮጵያ የሚመራበትን የተቋም አሰራር እና የዘርፉን ትኩረት በተመለከተ ለመድረኩ ተሳታፊዎች ገለፃ የተደረገ ሲሆን ኮሚቴው ሊመራበት የሚችል መመሪያም ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል፡፡
የሥራ ዕድል ፈጠራ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ማዕከል እየሆነ በመምጣቱ በመንግስት በኩል በብሔራዊ ደረጃ በከፍተኛ ደረጃ የሚመራ ጠንካራ አደረጃጀት እንዲኖር አቅጣጫ መቀመጡ በመድረኩ ላይ የተገለፀ ሲሆን የሚፈጠረው አደረጃጀት በቀጣይ እንደሚጠናከር ተገልጿል፡፡
ሚያዝያ 26/2015 ዓ.ም፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር
04/05/2023
01/03/2023
26/09/2022
04/09/2022
06/02/2022