የደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የቤተ አብርሃም ሰ/ት/ቤት ገጽ

የደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የቤተ አብርሃም ሰ/ት/ቤት ገጽ

Share

መንፈሳዊ ገጽ its a spritual page...

19/06/2026

አንድ አምላክ በኾነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሰኔ ዐሥራ ሁለት በዚች ዕለት የከበረ የመላእክት አለቃ የመልአኩ የሚካኤል የመታሰቢያውን በዓል ያከብራሉ፡፡ የሚያከብሩበትም ምክንያት እንዲህ ነው፤
እስክንድርያ በምትባል ከተማ አክላወበጥራ የተባለች ንግሥት የንጉሥ በጥሊሞስ ልጅ ዙሐል በሚባል ኮከብ ስም ያሠራችው ታላቅ ምኵራብ ነበረና በየዓመቱ ሰኔ በባተ በዐሥራ ሁለት ቀን በዚያ ምኵራብ ሕዝቡ ተሰብስቦ ታላቅ በዓል ያደርጉ ነበር፡፡ በዚያም ምኵራብ ውስጥ ዙሐል የሚሉት ታላቅ የነሐስ ጣዖት ነበረና በዓሉ በሚከበርበት ዕለት ብዙ ፍሪዳዎችን ያርዱለት ነበር፡፡
አባ እለእስክንድሮስ እስከተሾመበት ዘመን ድረስ ለዚያ ጣዖት እንዲህ ሲያደርጉ ኖሩ፡፡ ይኸውም ሦስት መቶ ዓመተ ምሕረት ተፈጽሞ በአራተኛው ምዕት ውስጥ ነበር፡፡ አባ እለእስክንድሮስ በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ፣ ጻድቅ ቆስጠንጢኖስም በነገሠ ጊዜ የክርስትና ሃይማኖት ስለ ተስፋፋች ያን ጣዖት ሊሠብረው ወድዶ ሳለ ጐስቋሎች ሰዎች ከለከሉት፡፡ እንዲህም አሉት፤ ‹‹እኛ በዚህ ቦታ ይህን በዓል ማክበርን ለምደናል፡፡ እነሆ ከአንተ በፊት ዐሥራ ስምንት ሊቃነ ጳጳሳት አልፈዋል፤ ይህን ልማዳችንንም አልለወጡብንም፡፡››
አባ እለእስክንድሮስ ግን ገሠፃቸው፤ አስተማራቸው፡፡ ስሕተታቸውንም በመግለጥ እንዲህ አላቸው፤ ‹‹ይህ ጣዖት የማይጎዳና የማይጠቅም ነው፡፡ እርሱንም የሚያመልክ ሰይጣናትን ያመልካቸዋል፡፡ ምክሬንስ ብትሰሙ ቀድሞ እንደ ነበረ አድርጌ ይህን በዓል እሠራላችኋለሁ፤ ይኸውም ጣዖቱን እንድንሰብረው፣ ምኵራቡንም እንድንባርከውና በከበረ መልአክ በመላእክት አለቃ በሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አድርገን እንድንሰይመው ነው፡፡ እኛም ይህን ታላቅ በዓል እንሠራለን፡፡ የሚታረዱትም ላሞችና በጎች ለድኆችና ለጦም አዳራዎች፣ ለችግረኞችም በከበረው መልአክ ስም ምግብ ይኹኑ፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነት ያለው ስለ ኾነ ስለ እኛ ይማልዳልና፡፡›› ይህንንም ብሎ በዚህ በጎ ምክር አስወደዳቸው፤ እነርሱም ታዘዙለት፡፡
ከዚህም በኋላ ያንን ምኵራብ አድሰው በዚህ የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አደረጉት፡፡ በዚችም ዕለት አከበሩዋት፡፡ እርሷም የታወቀች ናት፡፡ እስላሞችም እስከ ነጉሡበት ዘመን ኑራ ከዚያ በኋላ አፈረሱዋት፡፡ ይህም በዓል ተሠራ፤ እስከ ዛሬም ጸንቶ ይኖራል፡፡
ዳግመኛም በዚች ዕለት እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን በነገዱ ውስጥ በመላእክት ዅሉ ላይ በብዙ ክብር ሾመው፡፡ ይህም የከበረ መልአክ ክብር ይግባውና በጌታችን ፊት ስለ ሰው ልጆችና ስለ ፍጥረትም ዅሉ ይለምናል፤ ይማልዳልም፡፡ የዚህ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ተአምራቱ ብዙዎች ናቸው፡፡ ከእነርሱም አንዱ ይህ ነው፤
እግዚአብሔርን የሚፈራ አንድ ሰው ነበረ፡፡ እርሱም የከበረ የሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለተኛው ቀን ይልቁንም በሰኔ እና በኅዳር ወር አብልጦ ያከብር ነበር፡፡ በጐረቤቱም ርኅራኄ የሌለው አንድ ባለ ጠጋ ሰው ነበረ፡፡ ይህን እግዚአብሔርን የሚፈራውን ሰው የከበረ መልአክ የሚካኤልን በዓል በሚያደርግበት ጊዜ ይጠላውና ያቃልለው ነበር፡፡ ለድኆች ስለ መራራቱም ይዘባበትበት ነበረ፡፡ የሕይወቱ ዘመንም ተፈጽሞ የሚሞትበትና ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ድካምም የሚያርፍበት ጊዜ ሲቀርብ የክቡር መልአክ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ታደርግ ዘንድ፣ ምጽዋት ሰጭም ትኾን ዘንድ ሚስቱን አዘዛት፡፡ ከዚህም በኋላ ዐረፈና ገንዘው ቀበሩት፡፡
ሚስቱም ፀንሳ ነበረች፡፡ የመውለጃዋ ጊዜም ደርሶ ምጥ ያዛት፡፡ በታላቅ ጭንቀት ውስጥ ሳለችም እንዲህ ብላ ጸለየች፤ ‹‹የእግዚአብሔር መልአኩ ሆይ ራራልኝ፡፡ በእርሱ ዘንድ ባለሟልነት አለህና፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ስለ እኔ ለምንልኝ፡፡›› ይህንንም በአለች ጊዜ በቤቷ ውስጥ ብርሃን በራ፡፡ ከችግርም ዳነች፤ መልአኩ ውብ የኾነ ወንድ ልጅንም ወለደች፡፡ የእግዚአብሔርም መልእክተኛ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ሕፃኑን እንዲህ ብሎ ባረከው፤ ‹‹ርኅራኄ የሌለውን የዚህን ባለ ጠጋ ገንዘብና ሀብት፣ ጥሪቱንም ዅሉ ይህ ሕፃን እንዲወርስ እግዚአብሔር አዝዟል፡፡››
ባለ ጠጋውም በቤቱ፣ በዐልጋው ላይ ሳለ ጌታ ጆሮውን ከፍቶለት ይህን ነገር ከመልአኩ ሰማ፡፡ ይህንን በሰማ ጊዜ ታላቅ ኀዘን ደረሰበት፡፡ ሕፃኑንም የሚገድልበትን ምክንያት ይፈልግ ጀመረ፡፡ ነገር ግን ክብር ይግባውና ጌታ ይጠብቀው ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ያ ባለጠጋ ምክንያት አዘጋጅቶ ‹‹የሚያገለግለኝ ልጅ ይኾነኝ ዘንድ ልጅሽን ስጪኝ፡፡ እኔም እየመገብኹና እያለበስኹ አሳድገዋለሁ፡፡ ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለሁ፤›› አላት፡፡ ይህንንም ነገር ከባለጠጋው በሰማች ጊዜ ስለ ችግሯ እጅግ ደስ አላት፡፡ ልጅዋንም ሰጠችው፡፡ እርሱም ሃያውን ወቄት ወርቅ ሰጣት፡፡ ልጅዋንም ወሰደው፡፡ የምሻው ተፈጸመልኝ ብሎ ደስ አለው፡፡
ከዚህም በኋላ በልጁ ቁመት ልክ ሣጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሣጥኑ ውስጥ አስገብቶ ዘጋበት፡፡ እስከ ባሕርም ተሸክመው ወስደው በባሕር ጣሉት፡፡ ክብር ይግባውና በጌታችን ፈቃድ ያ ሣጥን ሳይሠጥም ከዚያች አገር የሃያ ቀን መንገድ ያህል ርቃ ወደምትገኝ ወደ አንዲት አገር ወደብ እስከሚደርስ በባሕሩ ላይ ተንሳፈፈ፡፡ በባሕሩም አካባቢ በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ሣጥኑን በውኃ ላይ ተንሳፎ አየው፡፡ እርሱም ከባሕሩ አውጥቶ ወደ ቤቱ ወሰደው፡፡ ይህን ሣጥን እንዴት እንደሚከፍተው ያስብ ጀመረ፡፡ ይህንም ሲያስብ ወደ ባሕሩ ይሔድ ዘንድ ጌታችን በልቡናው ሐሳብ አሳደረበት፡፡ ወዲያውኑም ተነሥቶ ወደ ባሕሩ ሔደና አንድ ዓሣ የሚያጠምድ ሰው አገኘ፡፡
ዓሣ አጥማጁንም ‹‹መረብህን በኔ ስም ጣል፡፡ ለሚያዘውም ዓሣ ዋጋውን እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ አጥማጁም እንዳለው አደረገ፡፡ ያን ጊዜም ታላቅ ዓሣ ተያዘ፡፡ ዋጋውንም ይዞ ወደ ቤቱ ሔደ፡፡ ለራትም ይጠብሰው ዘንድ አረደው፡፡ በሆዱም ውስጥ መክፈቻ አገኘ፡፡ በልቡም ‹‹ይህ መክፍቻ ይህን ሣጥን ይከፍተው ይኾን?›› አለ፡፡ በሣጥኑ ቀዳዳም በአስገባው ጊዜ ፈጥኖ ተከፈተ፡፡ በውስጡም ይህን ታናሽ ብላቴና አገኘ፡፡ ልጅ የለውም ነበርና ታላቅ ደስታ ደስ አለው፡፡ ጌታችንንም አመሰገነው፡፡ ሕፃኑንም በመልካም አስተዳደግ አሳደገው፡፡ ሕፃኑም አድጎ ጐልማሳ ኾነ፡፡
ከብዙ ዘመናትም በኋላ ያ ባለ ጠጋ ተነሥቶ ወደዚያ አገር ሔደ፡፡ በመሸም ጊዜ ወደ በግ ጠባቂው ደጅ ደረሰ፡፡ በግ ጠባቂውን ‹‹እስከ ነገ የምናድርበት ማደሪያ በአንተ ዘንድ እናገኛለን? ኪራዩንም እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ በግ አርቢውም ‹‹እንዳልኽ ይኹንና እደር›› አለው፡፡ ባለ ጠጋውም በዚያ አደረ፡፡ ራት በሚቀርብም ጊዜ ሕፃኑን ‹ባሕራን› ብሎ ጠራው፡፡ ባለ ጠጋውም ሰምቶ ‹‹ልጅህ ነውን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ በግ ጠባቂውም ‹‹አዎን፤ ታናሽ ሕፃን ኾኖ ሳለ ከባሕር አግኝቼዋለሁና እግዚአብሔር የሰጠኝ ልጄ ነው›› አለው፡፡ ባለ ጠጋውም ‹‹በምን ዘመን አገኘኸው?›› አለው፡፡ እርሱም ‹‹ከሃያ ዓመት በፊት›› ብሎ መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም እርሱ ወደ ባሕር የጣለው መኾኑን ዐውቆ እጅግ አዘነ፡፡

በማግሥቱም ጎዳናውን ሊጓዝ በተነሣ ጊዜ ሰይጣናዊ ምክንያት አመካኝቶ በግ ጠባቂውን እንዲህ አለው፤ ‹‹ዕገሊት ወደምትባል አገር በቤቴ የረሳሁት ጉዳይ ስላለ እንድልከው ልጅህን ትሰጠኝ ዘንድ እሻለሁ፡፡ እኔም የድካም ዋጋውን ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ የብላቴናውም አባት ስለ ገንዘቡ ደስ ብሎት ልጁ ባሕራንን ሰጠው፡፡ እንዲህም ብሎ አዘዘው፤ ‹‹ልጄ ባሕራን፣ ይህ የከበረ ሰው ስለ ጉዳዩ ወደ ቤቱ ይልክህ ዘንድ ና፤ ወደ ቤትህም በሰላም ትመለሳለህ፡፡››
ያን ጊዜም ባለ ጠጋው ወደ መጋቢው እንዲህ ብሎ ደብዳቤ ጻፈ፤ ‹‹ይቺን ደብዳቤ በምታነባት ጊዜ ደብዳቤዋን ይዞ የመጣውን ገድለህ በጉድጓድ ውስጥ ጣለው፡፡ ማንም ዐይወቅ፡፡›› በመካከላቸውም የሚተዋወቁበትን ምልክት ጽፎ አሸጋት፤ ለባሕራንም ሰጠው፡፡ ለመንገዱም የሚኾነውን ስንቅ ሰጠው፡፡ ባሕራንም ተነሥቶ ጉዞውን ጀመረ፡፡ ሲጓዝም ሰንብቶ የአንዲት ቀን ጉዞ ሲቀረው እነሆ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል በንጉሥ ጭፍራ አምሳል በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ ‹‹አንተ ጐልማሳ የያዝኸው ምንድነው›› አለው፡፡ ‹‹ወደ ዕገሌ አገር ወደ ቤቱ ለማድረስ ከአንድ ባለ ጠጋ የተጻፈች መልእክት ናት›› አለው፡፡ ‹‹ያቺን ደብዳቤ አሳየኝ›› አለው፡፡ እርሱም ስለ ፈራ ሰጠው፡፡ በዚያን ጊዜም የከበረው መልአክ ሚካኤል ያቺን የሞት መልእክት ደመሰሳት፡፡ በእርሷ ፈንታም በንፍሐት ለውጦ እንደህ ብሎ ጻፈ፤ ‹‹ይቺን ደብዳቤ ይዞ ለመጣ ባሕራን ለሚባል ሰው ይቺ ደብዳቤ ደርሳ በምትነበብበት ጊዜ ልጄ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ በውስጥና በውጭ ያለ ንብረቴንና ጥሪቴን፣ ወንዶችና ሴቶች ባሮቼን፣ ጠቅላላ ንብረቴንም አውርሼዋለሁና የፈለገውንም ሊያደርግ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና እኔን አትጠብቁኝ፡፡ እኔ ብዙ እዘገያለሁ የኔ ሹም እገሌ ሆይ! በእኔና በአንተ መካከል ይቺ ምልክት እነኋት፡፡›› ከዚህ በኋላ አሽጐ ለባሕራን ሰጠውና ‹‹ወደ ባለ ጠጋው ቤት ሒደህ ይቺን ደብዳቤ ለሹሙ ስጠው፡፡ በጎዳናም እኔ እንደ ተገናኘሁህ አትንገረው፡፡ እንዳይገድልህም ይህን የሞት ደብዳቤ ለውጬልሃለሁ›› አለው፡፡ ባሕራንም ‹‹እሺ ጌታዬ ያዘዝኸኝን ዅሉ አደርጋለሁ›› አለ፡፡
ባሕራንም ወደ ባለ ጠጋው ቤት በደረሰ ጊዜ ያቺን ደብዳቤ ለሹሙ ሰጠው፡፡ በአነበባት ጊዜ በመካከላቸው ያለውን ምልክት አገኘ፡፡ አስተውሎም እርግጠኛ እንደ ኾነ ዐወቀ፡፡ ከዚህም በኋላ ለባሕራን ሠርግ አዘጋጅቶ እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል የባለ ጠጋውን ልጅ አጋቡት፡፡ ዐርባ ቀን ያህልም ደስታና ሐሴት እያደረጉ ኖሩ፡፡ ከዚህ በኋላ ባለ ጠጋው ከሔደበት መመለሻው ጊዜ ኾኖ በደስታ የኾነውን የመሰንቆና የእንዚራ ድምፅ ሰምቶ ‹‹ይህ የምሰማው ምንድነው›› ብሎ ጠየቀ፡፡ እነርሱም ‹‹ስሙ ባሕራን ለተባለ የአንተን ደብዳቤ ላመጣ ጐልማሳ ሰው ልጅህ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ እነሆ ለዐርባ ቀናት በሠርግ ላይ ነው፡፡ ገንዘብህንና ጥሪትህን ዅሉ ወንዶችና ሴቶች ባሮችህን አንተ እንዳዘዝኽ ሰጥተውታል›› አሉት፡፡ ይህንም በሰማ ጊዜ ደንግጦ ከፈረሱ ላይ ወደቀ በድንገትም ሞተ፡፡
ባሕራንም በጎ ሥራዎችን የሚሠራ ኾነ፡፡ የተገለጠለትና ከመገደል ያዳነው የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል እንደ ኾነ፤ ሊገድለው የሚሻውን የባለ ጠጋውን ጥሪቱን ዅሉ ያወረሰውም እርሱ እንደ ኾነ ተረዳ፡፡ የዚህንም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን መታሰቢያ በየወሩ ያደርግ ጀመረ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠራለት፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕሉን አሥሎ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ አደረገው፡፡ ከእርሱም ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡ ባሕራንም ቅስና ተሹሞ እስከ ዕለተ ሞቱ በዚያች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያገለግል ኾኖ ኖረ፡፡ በዚህ በከበረ የመልአክት አለቃ ሚካኤል አማላጅነት ከእናቱና ከአባቱ፣ ከልጆቹም ጋራ የዘለዓለም ሕይወትን ወረሰ፡፡
መድኃኒታችን በተነሣባትም ቀን ይህ ክቡር መልአክ ሚካኤል ከውስጠኛው መጋረጃ ውስጥ ገብቶ በክብር ባለቤት ፊት እንዲህ እያለ ይለምናል፤ ‹‹እውነት ስለ ኾነ ቃል ኪዳንህ በምድር መታሰቢያዬን የሚያደርጉትን ትምርልኝ ዘንድ፤ ፈጣሪዬ ሆይ! እኔ አገልጋይህና መልእክተኛህ ከቸርነትህ እለምናለሁ፡፡ አንተ መሐሪና ይቅር ባይ ነህና፡፡›› የክብር ባለቤት ጌታችንም እንዲህ ብሎ ይመልስለታል፤ ‹‹የመንፈሳውያን ሰማያውያን መላእክት አለቃቸው ሚካኤል ሆይ! መታሰቢያህን የሚያደርገውን ዅሉ መሸከም እንደምትችል ከሲኦል ሦስት ጊዜ በክንፎችህ ተሸክመህ እንድታወጣ እነሆ እኔ አዝዤሃለሁ፡፡›› ይህንንም ቃል በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት የበዓሉን መታሰቢያ ከሚያደርጉት በክንፎቹ ተሸክሞ የእሳቱን ባሕር አሳለፋቸው፡፡ እነርሱንም ከብቻው ጌታ በቀር የሚቈጥራቸው የለም፡፡
ስለዚህም የዚህን ታላቅ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ለማድረግ መታገል ይገባናል፡፡ እርሱ ከሰይጣን ወጥመድ ያድነን ዘንድ በዘመናችን ዅሉም ይጠብቀን ዘንድ፤ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይ ዘንድ፤ መከራችንንም ያርቅ ዘንድ፤ የምድራችንንም ፍሬ ይባርክ ዘንድ፤ ፈቃዱንም ለመሥራት ይረዳን ዘንድ፤ ከእኛ ወገን የሞቱትን ዕረፍተ ነፍስ ይሰጥ ዘንድ፤ ወደ መንገድ የሔዱ አባቶቻችንና ወንድሞቻተንን ወደ ቤቶቻቸው በሰላም፣ በጤና ይመልሳቸው ዘንድ፤ በመካከላችንም ፍቅር ያደርግልን ዘንድ፤ እስከ መጨረሻዪቱም ሕቅታ ድረስ በቀናች ሃይማኖት ያጸናን ዘንድ፤ የክርስቶስ ወገኖች የኾኑ መኳንንቶቻችንንም ጠብቆ በወንበሮቻቸው ላይ ያጸናቸው ዘንድ፤ የሳቱትንም ወደ ቀናች ሃይማኖቱ ይመልሳቸው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ ይለምናልና፡፡
ዳግመኛም በዚህች ቀን እግዚአብሔርን የሚፈራ አስተራኒቆስ የሚስቱ የቅድስት አፎምያ የዕረፍቷ መታሰቢያ ኾነ፡፡ ይህም ሰው በየወሩ ሦስት በዓላቶችን እያከበረ ኖረ፡፡ እሊህም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ በየወሩ በሃያ ዘጠኝ፤ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓል መታሰቢያ በየወሩ በሃያ አንድ፤ የከበረ የመላእክት አለቃ የኾነ የቅዱስ ሚካኤል በዓል መታሰቢያም በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን ናቸው፡፡ የሚሞትበትም ጊዜው ሲቀርብ እርሱ ሲሠራው የነበረውን ምጽዋት ይልቁንም እሊህን ሦስቱን በዓላት እንዳታስታጉል ሚስቱን ቅድስት አፎምያን አዘዛት፡፡
እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባሏን ለመነችው፡፡ እርሱም አሠርቶ ሰጣትና በቤቷ ውስጥ በክብር አኖረችው፡፡ ባሏም ከዐረፈ በኋላ ባሏ ያዘዛትን መሥራት ጀመረ፡፡ ሰይጣን ግን ቀናባት፡፡ በመበለት ሴት መነኵሲት ተመስሎ ከእርሷ ጋር ተነጋገረ፡፡ እንዲህም አላት፤ ‹‹እኔ አዝንልሻለሁ፤ እራራልሻለሁም፡፡ ገንዘብሽ ሳያልቅ፣ የልጅነትሽም ወራት ሳያልፍ አግብተሽ ልጅ ትወልጂ ዘንድ እመክርሻለሁ፡፡ ባልሽም መንግሥተ ሰማያትን ወርሷል፡፡ ምጽዋትም አይሻም፡፡›› አፎምያም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ ‹‹እኔ ከሌላ ሰው ጋራ ላልገናኝ በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን አድርጌያለሁ፡፡ ርግቦችና መንጢጦች እንኳ ሌላ ባል አያውቁም፡፡ በእግዚአብሔር አርአያ ከተፈጠሩ ሰዎች ይህ ሊኾን እንዴት ይገባል?››

ምክሩንም ባልሰማች ጊዜ አርአያውን ለውጦ በላይዋ ጮኸባት፡፡ እንዲህም አላት፤ ‹‹እኔ በሌላ ጊዜ እመጣለሁ፡፡›› እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ይዛ አሳደደችው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን የከበረ የመልአኩ የሚካኤል በዓል በሚከብርበት ዕለት እርሷም የበዓሉን ዝግጅት ስታዘጋጅ ሳለች ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ ‹‹አፎምያ ሆይ! ሰላም ላንቺ ይኹን! እኔ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ነኝ፡፡ ጌታ ወደ አንቺ ልኮኛልና እርሱም ይህን መመጽወትሽን ትተሽ ለአንድ ምእመን ሚስት ትኾኚ ዘንድ አዞሻል፡፡›› ባል የሌላት ሴት መልሕቅ የሌለውን መርከብ እንደምትመስል ዕወቂ፤ እንደ አብርሃምና ያዕቆብ እንደ ዳዊትም እንደነርሱ ያሉ ብዙ ሴቶችን እንዳገባ፤ እግዚአብሔርንም ደስ እንዳሰኙት ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጥቅሶችን ያመጣላት ጀመረ፡፡
ቅድስት አፎምያም መልሳ ‹‹አንተ የእግዚአብሔር መልአክ ከኾንኽ የመስቀል ምልክት ከአንተ ጋር ወዴት አለ? የንጉሥ ጭፍራ የኾነ ዅሉ የንጉሡን ማኅተም ሳይዝ ወደ ሌላ ቦታ አይሔድምና›› አለችው፡፡ ሰይጣኑም ይህንን በሰማ ጊዜ መልኩ ተለወጠና አነቃት፡፡ እርሷም ወደ ከበረው መልአክ ወደ ሚካኤል ጮኸች፡፡ ወዲያውኑም ደርሶ አዳናት፡፡ ያንም ሰይጣን ይዞ ይቀጣው ጀመረ፡፡ ሰይጣኑም ጮኸ፡፡ ‹‹ማረኝ፤ ያለ ጊዜዬ አታጥፋኝ፤ እግዚአብሔር እስከ ዓለም ፍጻሜ ታግሦናልና›› እያለ ለመነው፡፡ ከዚያም ተወውና አባረረው፡፡
የከበረ መልአክ ሚካኤልም እንዲህ አላት፤ ‹‹ብፅዕት አፎምያ ሆይ! ሒደሽ የቤትሽን ሥራ አዘጋጂ፡፡ አንቺ ዛሬ ከዚህ ዓለም በሞት ትለዪአለሸና፡፡ እነሆ እግዚአብሔርም ዐይን ያላየውን፣ ጆሮም ያልሰማውን፣ በሰው ልብም ያልታሰበውን አዘጋጅቶልሻል፡፡›› ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጣት፡፡ ወደ ሰማያትም ዐረገ፡፡ የበዓሉንም ዝግጅት እንደሚገባ ከፈጸመች በኋለ ወደ ኤጲስቆጶሱና ወደ ካህናቱ ዅሉ ላከች፡፡ ወደ እርሷም በመጡ ጊዜ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ይሰጧቸው ዘንድ ገንዘቧን ዅሉ አስረከበቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ተነሥታ ጸለየች፡፡ የከበረ የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤልንም ሥዕል አንሥታ ታቅፋ ሳመችው፡፡ ያን ጊዜም በሰላም ዐረፈች፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በጸሎቷ ይማረን፡፡ የዚህም የከበረ መልአክ ሚካኤል የረድኤቱ ኃይል ዅላችን የክርስቲያን ወገኖችን ይጠብቀን፡፡ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡– መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፲፪ ቀን፡፡

Photos from የደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የቤተ አብርሃም ሰ/ት/ቤት ገጽ's post 14/06/2026

‎የቤተ አብርሃም ሰንበት ትምህርት ቤት ለተማሪዎቿ የ፳፻፲፰ ዓ.ም. የሁለተኛ ወሰነ ትምህርት አጋማሽ (Mid) ፈተና ሰጠች።

፯/፲/፳፻፲፰ ዓ.ም.
#ደሴ|ኢትዮጵያ
ቤ.አ.ሚ.

‎በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃና መምሪያ የመንበረ ፓትርያርክ (ዓለም አቀፍ) የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ያዘጋጀውን ሥርዓተ ትምህርት መሠረት ያደረገ ፈተና ተሰጠ። ፈተናውን የወሰዱት በደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የቤተ አብርሃም ሰንበት ትምህርት ቤት ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ተማሪዎች ናቸው። የዚህ የሁለተኛ ወሰነ ትምህርት (Semester) አጋማሽ (Mid) ፈተና ሰኔ ፮ እና ሰኔ ፯ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም. በቅድስት ሥላሴና በቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል ግቢ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ክፍል እንዲሁም አምስተኛ እና ሰባተኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች ናቸው በቀጣይም የ፬ኛ እና የ፰ኛ ክፍል የሚኒስትሪ ተፈታኝ ተማሪዎች የሞዴል (የሙከራ) ፈተና በቀጣይ ከሃገረ ስብከቱ በሚገለጸው ቀን የሚቀጥል መሆኑ ታውቋል። የሰንበት ትምህርት ቤቱ ተማሪዎች በቆይታቸው ሲቀስሙት የነበረውን መንፈሳዊና ሞራላዊ ትምህርት ለመመዘን ፈተናው ተሰጥቶ በአግባቡ መጠናቀቁ ተገልጿል።

ዘገባው:- የቤተ አብርሃም ሰ/ት/ቤት ሚዲያና ሕዝብ ግንኙነት ማስተባበሪያ ነው።

ቤተ አብርሃም ዘደብረ ቤቴል ደሴ is LIVE | TikTok 07/06/2026

የዝማሬ ጰራቅሊጦስ ጉባዔ ሁለተኛና የመጨረሻ ቀን።
በቲክቶክ አካውንታችን ይከታተሉ።

https://vt.tiktok.com/ZS92nqJDAfUNa-Eua4P/



#ደሴ #ኢትዮጵያ

ቤተ አብርሃም ዘደብረ ቤቴል ደሴ is LIVE | TikTok ዝማሬ ጰራቅሊጦስ. | Check out ቤተ አብርሃም ዘደብረ ቤቴል ደሴ's LIVE streams on TikTok! Watch, follow, and discover the latest content from ቤተ አብርሃም ዘደብረ ቤቴል ደሴ.

Photos from የደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የቤተ አብርሃም ሰ/ት/ቤት ገጽ's post 07/06/2026

የዝማሬ ጰራቅሊጦስ የመጀመሪያ ቀን አገልግሎት በከፊል። ዛሬም ይቀጥላል።



#ደሴ #ኢትዮጵያ

31/05/2026

የኃዘን መግለጫ

“መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፥ ሩጫውን ጨርሻለሁ፥ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ ወደፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል።”
(፪ኛ ጢሞቴዎስ ፬፥፯)

በደሴ ርዕሰ አድባራት ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ወልድ ዋሕድ ሰንበት ትምህርት ቤት በትሕትና፣ በብርቱ አገልግሎትና በቅንነት ስታገለግል የነበረችው ውድ እህታችን የሺ ምጽዋት (አጸደ ማርያም) ወደማያልፈው ዓለም መሻገሯን ስንሰማ ታላቅ መንፈሳዊ ኃዘንና ክርስቲያናዊ ተስፋ ተሰምቶናል።
ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “የቅዱሳኑ ሞት በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው።” (መዝ ፻፲፭፥፲፭) እንዳለ፣ እህታችን አጸደ ማርያም በምድር ቆይታዋ የእግዚአብሔርን ቤት በታማኝነት ያገለገለች የመልካም ሥራ አርአያ ነበረች። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “ክርስቲያን በመልካም ሥራው እንጂ በምድር ዕድሜው ብዛት አይመዘንም” እንዳለው፣ የእርሷ የትሕትናና የትጋት አሻራ ሁልጊዜም በልባችን ታትሞ ይኖራል። እኛ የደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የቤተ አብርሃም ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ለአገልግሎት አጋራችን ለወልድ ዋሕድ ሰንበት ትምህርት ቤት፣ ለወዳጅ ዘመዶቿና ለቤተሰቦቿ በሙሉ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚሰጥ ሰማያዊ መጽናናትን እንመኛለን።
ልዑል እግዚአብሔር የምድር አገልግሎቷን ተቀብሎ ነፍሷን ከአብርሃም፣ ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጎን ያሳርፍልን። በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌምም የክብር አክሊልን ያጎናጽፋት።
“ጻድቅስ ለዘለዓለም ይታሰባል።” (መዝ ፻፲፩፥፮)
የደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል
የቤተ አብርሃም ሰንበት ትምህርት ቤት
ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም.

29/05/2026

ደብረ ምጥማቅ

ግብጽ በምትገኘው በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም በተሠራችው ደብረ ምጥማቅ ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ላይ ድንግል ማርያም ከግንቦት ፳፩ ጀምሮ እስከ ፳፭ ቀናት በተከታታይ በመገለጧ ሕዝበ ክርስቲያን በዓሏን ያከብራሉ፡፡
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ምድረ ግብጽና ኢትዮጵያ በተሰደደች ጊዜ በአሁኑ ጊዜ ደብረ ምጥማቅ ተብሎ በሚጠራው ቦታ ላይ ዐርፈው ነበር። ጌታችንም ቦታውን ባርኮ የእርሷ መገለጫ እንዲሆን ቃል ኪዳን ገብቶላት ስለነበር ጊዜው በደረሰ ሰዓት ደብረ ምጥማቅ ተገድሞ የበርካታ መነኮሳት በዓት ሆነ። በደብረ ምጥማቅም እመቤታችንም ቅድስት ድንግል ማርያም ብርሃን ተጎናጽፋና በሠራዊት መላእክት ታጅባ ተገልጣለች፤ በዚያን ጊዜም ሱራፌል ማዕጠንታቸውን ይዘው ሰገዱላት፤ እንዲህ እያሉም አመሰገኗት፤ ‹‹አብ በሰማይ አይቶ እንዳንቺ ያለ አላገኘም፤ ባንቺም ሰው ሆነ፡፡›› (መጽሐፈ ስንክሳር ግንቦት ፳፩ ገጽ. ፫፻፲፰)
ሰማዕታትም እንደየክብራቸው ማዕረግ ለእመቤታችን ድንግል ማርያም ሊሰግዱ ረቂቃን በሆኑ ፈረሶቻቸው ተቀምጠው ወደ እርሷ ቀረቡ፤ በመጀመሪያ ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሁሉም ቀድሞ ከሰገደላት በኋላ ሌሎቹም በተመሳሳይ መልኩ ሰገዱላት፡፡ ከዚህም በኋላ ቅዱስ መርቆሬዮስ በዱሪ ፈረስ ተቀምጦ ወደ እርሷ በመምጣት ሰገደላት፡፡ ጻድቃን በአንድነት ቀርበው ለክብሯ ሰገዱላት፤ ቀጥሎም በንጉሥ ሄሮድስ በግፍ የተገደሉት ሕፃናት ለእርሷ ሰገዱ፤ በደስታና በፍቅርም ተጫወቱ፡፡ በዚያ የተሰበሰቡትም ክርስቲያኖች፣ አረማውያን ይህን በዐዩ ጊዜ ደስታ ሞልቶባቸው በተለየ ዓለም ያሉ ይመስላቸው ነበር፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ግንቦት ፳፩ ገጽ. ፫፻፲፰)
አባ ጽጌ ድንግልም በደብረ ምጥማቅ በታላቅ ክብር ለምእመናን የታየችው የአምላክ እናት የድንግል ማርያምን መገለጥ በማኅሌተ ጽጌ ድርሰቱ እንዲህ በማለት ገልጾታል፤ ‹‹አመ ትበርቂ በደብረ ምጥማቅ ኀምሰ ዕለታተ፣ ትእምርተ ገጽኪ ይርአይ እስከ ይትነሣእ ዘሞተ፣ሚ መጠነ ማርያም ታሥተፌሥሒ ትፍሥሕተ፣ ኅድጊሰ ጽጌ ፍቅርኪ በጊዜ ንቃሁ መዓልተ፣ ብፁዕ ዘርእየኪ በሕልሙ ሌሊተ፤ የፊትሽን መልክ ያይ ዘንድ የሞተ ሰው እስኪነሣ ድረስ በደብረ ምጥማቅ ለአምስት ቀናት ያህል በተገለጽሽ ጊዜ ማርያም ምን ያህል ደስ ታሰኚ ኖሯል! በቀን የታየው የፍቅርሽ አበባ ይቅርና ሌሊት በሕልሙ ያየሽ ምስጉን ነው፡፡›› (ማኅሌተ ጽጌ)
በደብረ ምጥማቅ ከተሰበሰቡት ሕዝብ መካከል እናትና አባታቸው፣ ዘመዶቻቸው እንዲሁም ባልንጀሮቻቸው የሞቱባቸው ሰዎች ቅድስት ድንግል ማርያም እንድታሳያቸው በለመኗት ጊዜ እንደ ቀደመ መልካቸው አድርጋ ታሳያቸው ነበር፡፡ አንዳንዶች ደግሞ መሀረባቸውን ወደ ላይ በሚወረውሩት ጊዜ እርሷ የወደደቻቸው እንደሆነ በእጅዋ ተቀብላ መልሳ ትጥልላቸዋለች፤ ሁሉም ለበረከት ይካፈሉታል፡፡ እነርሱም ወደ ቤታቸውም ለመሄድ በሚፈልጉ ሰዓት ተሰናብተውና በተባርከውም ይሄዳሉ፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ግንቦት ፳፩ ገጽ. ፫፻፲፱)
የደብረ ምጥማቅና የአካባቢዋ ሰዎች እመቤታችን ድንግል ማርያምን ያዩባቸው ቀናት አረማውያኑ ያመኑበት፣ የበደሉት በምልጃዋ ቸርነትን ምሕረትን ያገኙበት፣ ያመኑት ደግሞ የተባረኩበት ዕለታት ነበሩ፡፡ ሕዝቡ እርሷን ተመኝተው ያጡት ወይንም ጠይቀው ያልተፈጸመላቸው ምንም ነገር አልነበረም:: ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት፣ ደናግል፣ መነኮሳት መላእክትና ሊቃነ መላእክትም ለድንግል ማርያም ሲሰግዱ ይታዩ ነበር::
ከዚህ በኋላ በዘመናት ይኖሩ የነበሩ ቅዱሳን የአምላክን እናት ለማየት ብዙዎች ተመኝተዋል፤ የመልክአ ማርያም ደራሲ ዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ የአምላኩን እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን ፊቷን ለማየት ሽቶ ‹‹ሰላም ለመልክእኪ ዘተሠርገወ አሜረ ዘያበርህ ወትረ ፍቅርትየ አንቲ እንተ ታበድሪ ፍቅረ አርእዪኒ ገጸ ዚኣኪ ማርያም ምዕረ ዘኢይሰምዖ ካልእ እንግርኪ ነገረ፤”
ዘወትር የሚያበራ ፀሐይን ጌጥ ላደረገ መልክሽ ሰላምታ ይገባል፤ ፍቅርን የምትመርጪ (የምታስቀድሚ) አንቺ የምወድሽ ማርያም ሌላ የማይሰማው ነገርን እነግርሽ ዘንድ አንድ ጊዜ ያንቺን ፊት ግለጪልኝ (አሳይኝ)›› በማለት ተማፅኗታል፡፡ (መልክአ ማርያም)
ነቢዩ ዳዊት ‹‹ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኲሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤ የምድር ባለጠጎች አሕዛብ ሁሉ በፊትሽ ይማለላሉ›› በማለት ትንቢትን እንደተናገረላት በርካት ቅዱሳን ሰዎች ቅድስት ድንግል ማርያምን ተገልጻላቸው ለማየት ተመኝተዋል፤ ልመናቸው ተሰምቶላቸው የአምላክ እናት ተገልጻላቸው ፊቷን ለማየትን ክብሯን ለመግለጥ ቅዱሳን አባቶች፣ ጻድቃን ሰማዕታት በቅተዋል፡፡ ይህም የሆነው በፍጹም ልቡናቸው በመማፀናቸውና በፍጹም ትጋት የጌታቸውን እናት ሲያገለግሉ በመኖራቸው እንደሆነ የጻድቃኑ ገድል ምስክር ነው፡፡ እነርሱም ሌት ከቀን ምኞታቸው ይሳካላቸው ዘንድ በጸሎት ይማፀኑ ነበር፡፡ (መዝ. ፵፬፥፲፪)
እመቤታችን ድንግል ማርያምም ጸሎታቸውን ሰምታ ያሰቡትን ትፈጽምላቸው ነበር፤ ምኞታቸው ከተሳካላቸው ቅዱሳን አባቶች መካከል አባ ይስሐቅ አንዱ ነው፤ ይህ ቅዱስ አባትም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በፍጹም ልቡናው ይወዳት ስለነበር ለሰባት ዓመታት አምላኩን ክብርት እናቱን ያሳየው ዘንድ በጸሎቱ ተማጸነ፡፡ ዘወትር ከሠርክ ጸሎት በኋላ ሌሎች መነኮሳት ለመኝታ ወደ የበዓታቸው ሲሄዱ አባ ይስሐቅ ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ በቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕሏ ፊት ቆሞ ሦስት መቶ ስግደትን እየሰገደ ይማፀን ነበር፡፡ ከስግደቱም ጋር ‹‹ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ አርእየኒ እመከ አሐተ ሰዓተ፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ለአንዲት ሰዓት እናትህን አሳየኝ›› እያለ ይጸልይ ነበር፡፡ በእንደዚህም ሁኔታ ለሰባት ዓመት ከቈየ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በታላቅ ግርማ ተገለጸችለት፤ የልቡም መሻት ምን እንደሆነ ጠየቀችው፤ አባ ይስሐቅም የርሷን ገጽ ያዩ ዐይኖቹ ሌላ ነገርን ማየት እንደማይሹ ነገራት፤ ከተወደደ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ እንድታማልደውም ተማጸናት፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምም ልመናውን ተቀበለች፤ ከዚያም በኋላ የዕረፍቱ ቀን ከሦስት ቀን በኋላ መሆኑን አሳወቀችው፤ ባርካውም ወደ ሰማይም በክብር ዐረገች፤ ይህ ቅዱስ አባት ይስሐቅም እርሷን ካየ በሦስተኛው ቀን ዐረፈ፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ታኀሣሥ ፳፩ ገጽ.፬፻፺፪)
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ ተገልጣ የሕዝቡን ምኞት እንደፈጸመችላቸው የእኛንም በጎ መሻት ትፈጽምልን፤ አሜን፡፡

ምንጭ:- ማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ

21/05/2026

በዓለ ዕርገት

የበዓለ ዕርገት ታሪካዊ አመጣጥ ከራሱ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራ ጋር የተያያዘ ነው። ጌታችን ከትንሣኤው በኋላ ለሐዋርያቱ ለአርባ ቀናት እየተገለጸ፣ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት አስተምሯቸዋል። (ግብረ ሐዋርያት ፩፥፫) እነዚህ አርባ ቀናት ሐዋርያት ትንሣኤውን እንዲያረጋግጡና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እንዲያውቁ ያደረገባቸው ጊዜያት ነበሩ።
በአርባኛው ቀን ጌታችን ሐዋርያቱን እስከ ቢታንያ አወጣቸው፤ ይህም በደብረ ዘይት ተራራ አካባቢ ነው። እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው፤ እየባረካቸውም ሳለ ከእነርሱ ተለየ፤ ወደ ሰማይም ዐረገ። (ሉቃስ ፳፬፥፶-፶፩) ሐዋርያትም እርሱ ሲያርግ በዓይናቸው ተመልክተዋል። ደመናም ከዓይናቸው ሠውራዋለች።
እነርሱም ወደ ሰማይ ትኵር ብለው ሲመለከቱ፣ እነሆ ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት ሰዎች በአጠገባቸው ቆመው “እናንተ የገሊላ ሰዎች ሆይ፥ ወደ ሰማይ እየተመለከተ ስለምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ፥ ወደ ሰማይ ሲወጣ እንዳያችሁት፥ እንዲሁ ዳግመኛ ይመጣል” አሏቸው። (ግብረ ሐዋርያት ፩፥፱-፲፩)
የጌታችን ዕርገት ድንገተኛና ያልተጠበቀ ክስተት አልነበረም። በብሉይ ኪዳን ነቢያት ስለዚህ ነገር ትንቢት ተናግረው ነበር። ለምሳሌ፡- “እግዚአብሔር በእልልታ ዐረገ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ።” (መዝሙረ ዳዊት ፵፮፥፭)
“ወደ ላይ ዓረግህ፥ ምርኮን ማረክህ፥ ስጦታንም ለሰዎች ሰጠህ።” (መዝሙረ ዳዊት ፷፯፥፲፰)
ስለዚህ የበዓሉ ታሪካዊ መሠረት ጌታችን ራሱ ያከናወነው የዕርገቱ ሥራ ነው።
የጌታችን ዕርገት በርካታ መጽሐፍ ቅዱሳዊና የአበው ምሥጢራዊ ምንጮች አሉት። ከእነዚህም መካከል ዋና ዋናዎቹ፡-
የክርስቶስ በምድር የነበረው አገልግሎት ማጠናቀቂያና የክብሩ መገለጫ፦ ዕርገቱ የክርስቶስ የማዳን ሥራ ምድራዊ ክፍል ፍጻሜ ነው። በሥጋ ተገልጦ፣ አስተምሮ፣ ተሰቅሎ፣ ሞቶ፣ ተነሥቶ ካሳየን በኋላ፣ ወደ ቀደመ ክብሩ፣ ወደ አባቱ መመለሱን ያመለክታል። ቅዱስ አትናቴዎስ ዘእስክንድርያ “ጌታችን ያረገው ሥጋ ለባሽ ሆኖ ነው፤ ይህም ሥጋችን በሰማያት ቦታ እንዳለውና እንደሚከብር ያረጋግጥልናል” በማለት እንደሚያስተምረው፣ የሰው ልጅ በበደሉ ያጣውን የልጅነት መብትና ክብር ክርስቶስ በዕርገቱ መልሶለታል።
ክርስቶስን የተዋሐደው ሥጋችን መክበሩ (የተዋሕዶ ምሥጢር ፍጻሜ)፦
ጌታችን አምላክ ወልደ አምላክ ሲሆን የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ፣ በተዋሕዶ ሥጋ ማረጉ ለሰው ልጆች ሁሉ ታላቅ ክብር ነው። ቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ “ወልድ በባሕርይው ከአብ ጋር በባሕርይ አንድ ሆኖ ሳለ፤ በተለየ አካሉ ሥጋችንን ተዋሕዶ ወደ ሰማይ አሳረገው፤ ይህም እኛም እርሱን ተከትለን፤ ወደዚያ ክብር እንደምንደርስ የሚያሳይ ነው” በማለት የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ኅብረትና ክብር ያሳያል።
የመንፈስ ቅዱስ ስጦታና የቤተ ክርስቲያን መመሥረት፦
ጌታችን ለሐዋርያቱ “እኔ ካልሄድሁ አጽናኙ መንፈስ ቅዱስ ወደ እናንተ አይመጣም፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ” ብሏቸው ነበር። (ዮሐንስ ፲፮፡፯) ስለዚህ ዕርገቱ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ (የበዓለ ጰራቅሊጦስን) የገለጠ ነው። ጌታችን ጰራቅሊጦስ የተባለውን መንፈስ ቅዱስ እንደሚልክላቸው ነግሯቸው ነበር፡፡ (ዮሐንስ ፲፬፥፳፮)
የቤተ ክርስቲያን ራስ መሆኑ፦
ክርስቶስ ወደ ሰማይ በማረጉ፣ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደሆነ የተገለጠበት ነው። (መልእክት ኀበ ሰብአ ኤፌሶን ፩፥፳-፳፫) ቤተ ክርስቲያንም አካሉ ናት፤ እርሱም ዘወትር ቤተ ክርስቲያን ይመራል፤ ይጠብቃል፤ ያጸናል።
የዳግም ምጽአቱ የተስፋ ቃል ማረጋገጫ (የዳግም ምጽአት ተስፋና የፍርድ ቀን ማስታወሻ)፦ መላእክት እንዳበሠሩት፣ ጌታችን እንዳረገ እንዲሁ ዳግመኛ በክብር ይመጣል። ዕርገቱ ለዳግም ምጽአቱና ለፍርዱ ማረጋገጫ ነው። (ግብረ ሐዋርያት ፩፥፲፩)
ለእኛ የሰማያዊ ቦታ ዝግጅት፦ ጌታችን “በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ … ሄጄም ስፍራ አዘጋጅላችኋለሁ” ብሏል። (ዮሐንስ ፲፬፥፪-፫) ዕርገቱ ይህንን የተስፋ ቃል የሚያረጋግጥና ለእኛም በሰማያዊው መንግሥት ቦታ እንዳለን ተስፋ የሚሰጥ ነው።
በዓለ ዕርገት በክርስቲያኖች ሕይወት ያለው ቦታ
የጌታችን ዕርገት በክርስቲያኖች መንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ ጥልቅ አንድምታ አለው፡-
የሰማያዊ ተስፋ ምንጭ፦ የክርስቶስ ዕርገት የእኛም የወደፊት ዕርገትና በሰማያዊው መንግሥት የመኖር ተስፋችንን ያጸናል። ልባችንንና ሐሳባችንን ወደ ሰማያዊ ነገር እንድናደርግ ያሳስበናል፤ (ልባችንን ወደ ሰማይ የማሳረግ ጥሪ)፦ “እንግዲህ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ፥ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን እሹ። በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም።” (መልእክት ኀበ ሰብአ ቆላስይስ ፫፥፩-፪)
በመንፈሳዊ አገልግሎት እንድንበረታ ያደርጋል፦ ጌታችን ከማረጉ በፊት ታላቅ ተልእኮ ሰጥቷል። (ማቴዎስ ፳፰፥፲፱-፳) ዕርገቱ ይህንን ተልእኮ በኃይልና በሥልጣን እንድንፈጽም ያበረታታናል።
ዕርገቱ የመንፈስ ቅዱስን መምጣት እንደገለጠ ሁሉ፣ እኛም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ታድሰንና በርተን እንድንኖር ያስታውሰናል።
በዓለ ዕርገትን ስናከብር ልናደርጋቸው ስለሚገቡ ክርስቲያናዊ ተግባራት
በዓለ ዕርገትን ስናከብር የሚከተሉትን ክርስቲያናዊ ተግባራት ከአበው አስተምህሮ ጋር በማስተባበር ልናከናውን ይገባል፡-
በጸሎት፣ በምስጋናና በቅዳሴ መትጋት፦ ዕርገት የድልና የክብር በዓል ነው። ስለዚህ ጌታችን ላደረገልን የማዳን ሥራ፣ በተለይም ሥጋችንን አክብሮ ወደ ሰማይ ስላሳረገልን ልባዊ ምስጋና ማቅረብ ይገባል። በቤተ ክርስቲያን ተገኝቶ በቅዳሴ ሥርዓት መሳተፍ፣ የዕለቱን ምስጋና፣ ጸሎትና የቅዱስ ቊርባን ሥርዓት በመካፈል ከጌታችን ጋር ያለንን ኅብረት ማጽናት ይገባል።
የቅዱሳት መጻሕፍትንና የአበውን ትርጓሜ ማጥናት፦ የዕርገቱን ምሥጢር በሚገባ ለመረዳት ተገቢ የሆኑትን የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎች (ግብረ ሐዋርያት ምዕ. ፩፣ ሉቃስ ምዕ. ፳፬፣ መልእክት ኀበ ሰብአ ኤፌሶን ምዕ. ፩ እና መልእክት ኀበ ዕብራውያን ምዕ. ፩) እንዲሁም የአበውን ድርሳናት ማንበብ መንፈሳዊ ዕውቀታችንን ያሰፋል።
ልብን ከምድራዊ ነገር ለይቶ በሰማያዊው ላይ ማድረግ፦ አበው እንዳሳሰቡን፣ የጌታችን ዕርገት አሳባችንን ከዚህ ዓለም ጊዜያዊ ነገር ላይ አንሥተን በሰማያዊውና በዘላለማዊው ነገር ላይ እንድናደርግ ያነሳሳናል።
ምጽዋትና የፍቅር ሥራዎች፦ ጌታችን “ለእነዚህ ከታናናሾቹ ለአንዱ ያደረጋችሁት ለእኔ እንዳደረጋችሁት ነው” እንዳለው፣ የክርስቶስን ፍቅር በተግባር መግለጽና በረከትን ማካፈል ነው። (ማቴዎስ ፳፭፥፵)
አምላካችን እግዚአብሔር ከበዓሉ በረከት ረድኤት ይክፈለን፤ አሜን!

ምንጭ:- ማኅበረ ቅዱሳን

19/05/2026

ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ

ቅዱስ ያሬድ ውልደትና እድገቱ ኢትዮጵያ ወስጥ፣ አክሱም ከተማ ከአባቱ ከአብዩድና ከእናቱ ታውክሊያ ነው፤ ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ እናቱ መምህር ወደ ሆነው አጎቱ አባ ጌዲዮን ትወስደዋለች፡፡ እርሱ ግን በመጀመሪያ ትምህርት ሊገባው አልቻለም፡፡ ከዕለታት በአንድ ቀን መምህር ጌዲዮን ያሬድን ሲገርፈው በምሬት አለቀሰ፤ ማይኪራህ ወደምትባል ቦታም ተጓዝ፤ በመንገድ ላይ ሳለ ውኃ ስለተጠማ በዚያች ስፍራ ካለ ምንጭ ውኃ ጠጥቶ በዛፉ ሥር ለማረፍ ቁጭ አለ፤ ወደ ላይም በሚመለከትበት ጊዜ ከዛፉ ላይ አንዲት ትል ፍሬ ለመብላት ከታች ወደ ላይ ስትወጣ ስትወርድ ተመለከተ፡፡ እርሱም ትኩር ብሎ አያት፤ ትሏም ስድስት ጊዜ ያለመሰልቸት ከወጣች ከወረደች በኋላ በሰባተኛው ፍሬው ካለበት መድረስ ቻለች፤ ፍሬውንም መብላት ጀመረች፡፡ በዚያን ወቅት ቅዱስ ያሬድ አሰበ፤ እንዲህም አለ፤ «ይህች ትል ፍሬውን ለመብላት እንዲህ ከታገሠች እኔም እኮ ትምህርት ለመማር ብታገሥ እግዚአብሔር አምላክ ይገልጽልኛል፡፡» ወደ ጉባኤው ተመልሶ መምህሩን ይቅርታ ከጠየቀ በኋላ መማር ጀመረ፤ እግዚአብሔር አምላክም የ፹፤፩ መጽሐፍትንና የሊቃውንት መጽሐፍትን እንዲሁም ሌሎች ቤተ ክርስቲያን የተቀበለቻቸውን የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ገለጸለት፤ መምህር ጌዲዮን ሲሞት የእርሱን ቦታ ተረክቦ ማሰተማር ቀጠለ፡፡

በ፭፻፴፬ ዓ.ም. ኅዳር ፮ ቀን ወደ ሰማይ ተነጠቀ፤ በሰማይ ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን ልዩ በሆነ ጣዕመ ዝማሬ ሲያመሰግኑ ሰማ፡፡ ወደ ምድርም በተመለሰ ጊዜ አክሱም ጽዮን ውስጥ ወደ ምሥራቅ በኩል በመዞር ከሰማይ የሰማውን ዝማሬ ዘመረ፤ አርያም ብሎም ሰየመው፡፡ በዚሁም በ፭፻፴፰ ዓ.ም. ቅዱስ ያሬድ ማኅሌትን ጀመረ፡፡ ታኅሣሥ ፩፣ በዕለተ ሰኞ ምህላ ያዘ፤ እሰከ ታኅሣሥ ፮፣ ቀዳሚት ሰንበት ድረስም ዘለቀ፤ በዚያች ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል አንደተሰቀለ ሆነ ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገለጸለት፡፡
ቅዱስ ያሬድም ጌታ የተገለጸለትን የመጀመሪያውን ሳምንት ‹ስብከት› ብሎ ሰየመው፤ በሳምንቱም እንደገና በብርሃን አምሳል ስለተገለጸለት ያን ዕለት ‹ብርሃን› ብሎ ሰየመው፤ በሦስተኛው ሳምንት እንዲሁ በአምሳለ ኖላዊ ስለተገለጸለት ‹ኖላዊ› ብሎ ሰየመው፡፡ በመጨረሻም ሳምንት በአምሳለ መርዓዊ ሲገለጽለት ዕለቱን ‹መረዓዊ› ብሎ ሰይሞታል፡፡
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሬድ ፭ የዜማ መጻሕፍትን ደረሰ፤ እነዚህም ድጓ፣ ጾመ ድጓ፣ ምዕራፍ፣ ዝማሬና መዋሥዕት ናቸው፡፡ ከደረሳቸው የዜማ መጽሐፍቶችም ውስጥ ትልቁ ድጓ ነው፤ በሦስትም ይከፈላል፤ የዮሐንስ፤ አስተምህሮና ፋሲካም ይባላሉ፡፡ በንባባት ብቻ ይቀደስባቸው የነበሩትን ፲፬ቱ ቅዳሴያት በዜማ የደረሳቸው ቅዱስ ያሬድ ነው፤ ዝማሬም በ፭ ይከፈላል፤ኅብስት፣ጽዋዕ፣መንፈስ፣አኮቴትና ምሥጢር ይባላል፡፡
ይህ ቅዱስ ደራሲ በተወለደ በ፸፭ ዓመቱ በሰሜን ተራራ ውስጥ ደብረ ሐዊ ከሚባል ገዳም ግንቦት ፲፩ ቀን ተሠውሯል፡፡ የዝማሬና መዋሥዕት መምህራን የቅዱስ ያሬድን ጉባኤ ተክተው አሁን በማስተማር ላይ እስካሉት መጋቤ ብርሃናት ፈንታ ድረስ ፵፮ ናቸው፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለውለታ፣ ቅዱስ ያሬድ መምህር ወሐዋርያ፣ መጻሕፍትን በጣዕመ ዜማ የደረሰ፣ መዝሙረ ዳዊትን ጨምሮ ሌሎችንም ቅዱሳት መጻሕፍትን በተለያየ ዜማ ያመሳጠረ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ነው፡፡

13/05/2026

ይህ የደሴ ደብረ ቤቴል ቅድስት ሥላሴ እና ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል የቤተ አብርሃም ሰንበት ትምህርት ‎ቤት የሎጎ መግለጫ ነው።

‎፩./ የሁለቱ መቅደሶች ጥምረት :-

‎ይህ አርማ የሰንበት ትምህርት ቤቱን ትላንት እና ዛሬ በአንድ ምስል ላይ ያገናኛል።
‎✝️ የግርማ ሞገስ መገለጫ (ጉልላቶች)፦ በአርማው አናት ላይ በኩራት ጎልተው የሚታዩት ሁለት ‎ጉልላቶች የተወሰዱት ከትልቁ ካቴድራል ሲሆን፣ ይህም የቤተክርስቲያኗን ወቅታዊ ስፋትና ‎ግርማ ያመለክታል።
‎✝️ የመሠረት መታሰቢያ (መካከለኛው ምስል)፦ በሎጎው እምብርት ላይ የሚታየው፣ ሦስት አካላት ‎(የቅድስት ሥላሴ ምስል) ያሉበት እና በድንጋይ ሕንፃ የተከበበው ንድፍ የተወሰደው ከትንሿ ‎(ጥንታዊቷ) ቤተክርስቲያን ነው። ይህም ሰንበት ትምህርት ቤቱ አገልግሎቱን የጀመረበትን ያንን ‎ቅዱስና ታሪካዊ መሠረት ዘላቂ መታሰቢያ እንዲሆን ተደርጎ የተቀረጸ ነው።

‎፪./ የ፶ ዓመታት መንፈሳዊ ጉዞ:-
‎✝️ ወርቃማው ኢዮቤልዩ፦ በሎጎው መሐል ላይ የሰፈሩት "፶" እና "50" ቁጥሮች ከ፲፱፻፷፱ ዓ.ም. ‎እስከ ፳፻፲፱ ዓ.ም. ያለውን ግማሽ ክፍለ ዘመን የተሻገረ የአገልግሎት ስኬት ያበስራሉ።
‎✝️ የድልና የሰላም ምልክት፦ በአርማው ግርጌ የተቀመጡት የወይራ ቅጠሎች ሰንበት ትምህርት ቤቷ ‎ባለፉት አምስት አሥርት ዓመታት ያፈራቸውን መንፈሳዊ ፍሬዎችና የሰላም ጉዞን ይወክላሉ።

‎፫./ ቀለማትና ድባብ :-
‎✝️ ጥልቀት ያለው ቡናማና ወርቃማ ቀለማት መጠቀማቸው የአርማውን ታሪካዊነትና "የወርቅ ‎ኢዮቤልዩ" ክብረ በዓልን ድምቀት በላቀ ሁኔታ ይገልጻሉ።

Want your school to be the top-listed School/college in Dessie?

Click here to claim your Sponsored Listing.

Location

Category

Website

Address


Dessie