09/08/2026
በጠለምት ወረዳ በተከሰተ ድርቅ ከ3,000 በላይ ነዋሪዎች መፈናቀላቸው ተነገረ
በድርቁ 14 ሺህ የቁም እንስሳት ሞተዋል ተብሏል
«ጉዳቱን የሚያጠና ግብረ ኃይል አቋቁመን ወደ አካባቢው ልከናል» የሰሜን ጎንደር ዞን አስተዳደር
በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ጠለምት ወረዳ በሚገኙ አስር ቀበሌዎች በተከሰተ ድርቅ 3,386 ነዋሪዎች ወደ አጎራባች ወረዳዎች መፈናቀላቸውን የጠለምጥ ወረዳ አስታወቀ።
ከሚያዝያ ወር 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በወረዳው በሚገኙ 24 ቀበሌዎች ውስጥ በአስሩ ዝናብ ባለመምጣቱ 3,386 ነዋሪዎች ቀያቸውን ለቀው መሰደዳቸውንና 14,089 የቁም እንስሳት መሞታቸውን፤ የጠለምጥ ወረዳ ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳነ እሸቴ ለሪፖርተር ተናግረዋል።
እርን፣ በተል፣ በስቅያ፣ መረው ብላ፣ መረው ገብርኤል፣ አገጣ፣ ደረባ፣ ከረዋ፣ ነጋዴ መሸገሪያና አተባ የተባሉ ቀበሌዎች፤ እስካሁን ምንም ዝናብ ያላገኙ መሆናቸውን የጠቀሱት አቶ አዳነ፤ ሌሎች ስድስት ቀበሌዎች ደግሞ ከሐምሌ 19 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ዝቅተኛ የዝናብ መጠን እያገኙ መሆናቸውንና ቀሪዎቹ ስምንት ወረዳዎች ዝናብ እያገኙ መሆናቸውን አስረድተዋል።
የሰሜን ጎንደር ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ክቡር አሰፋ በዞኑ የተለያዩ ወረዳዎች ከፍተኛ የዝናብ እጥረት መኖሩን ገልጸዋል።
በጠለምጥ ወረዳ ብቻ ሳይሆን በዞኑ የተለያዩ ወረዳዎች ድርቅ ያጋጠመ ቢሆንም፤ ከሐምሌ 19 ቀን 2018 ዓ.ም. በኋላ አንዳንድ ወረዳዎች ዝናብ መጣሉ መጀመሩን አቶ ክቡር አክለዋል።
በድርቁ ምክንያት በጠለምት ወረዳ ደረሰ የተባለውን ጉዳት አጣርቶ መረጃ የሚያቀርብ ግብረ ኃይል ተዋቅሮ ወደ ወረዳው መላኩን የገለጹት አቶ ክቡር፤ እስካሁን በወረዳው ስለሞቱ እንስሳትም ሆነ ስለተፈናቀሉ ሰዎች የደረሳቸው መረጃ እንደሌለና የተጠና ነገር ባለመኖሩም የጉዳቱን መጠን ከመናገር ተቆጥበዋል።
በሰዎችና በእንስሳት ላይ የደረሰ ጉዳት መኖሩ በጥናት ከተረጋገጠ፤ መረጃውን መሠረት በማድረግ ከመንግሥትና ከበጎ አድራጎት ድርጅቶች እርዳታ ሊጠየቅ እንደሚችል አስታውቀዋል።
የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ ይህንን ይበሉ እንጂ፤ የወረዳው ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳነ ግን፤ በአካባቢው ለረጅም ጊዜ አጥጋቢ ዝናብ ባለመምጣቱ በየወቅቱ የእንስሳት ሞትና የነዋሪዎች ስደት እንደሚያጋጥም ተናግረዋል።
አሁንም በርካታ እንስሳት በሞት አፋፍ ላይ እንደሚገኙ የተናገሩት አቶ አዳነ፤ ከወረዳው በተገኘ የሁለት ሚሊዮን ብር የእንስሳት መድኃኒት መገዛቱን ጠቅሰዋል። በአካባቢው ማሽላና ጤፍ በብዛት እንደሚመረት የተናገሩት አቶ አዳነ፤ አርሶ አደሮች በሚያዝያ ወር የተለያዩ ሰብሎችን ዘርተው እንደነበር አስታውሰው፤ ነገር ግን ዝናቡ ወቅቱን ጠብቆ ባለመምጣቱ 9,088 ሄክታር መሬት ሰብል ማብቀል ሳይችል በመቅረቱ ለከሰራ መዳረጋቸውን ጠቅሰዋል።
በአሁኑ ወቅት ወረዳው ዜጎችን ከድርቅ ለመታደግ አስፈላጊውን ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸው፤ ነገር ግን ከመንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ሰብአዊ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ አቶ አዳነ ጥሪ አቅርበዋል።