ኢስላማዊ እውቀቶች - Islamic Knowledge

ኢስላማዊ እውቀቶች - Islamic Knowledge

Share

Islamic Knowledge - ኢስላማዊ እውቀቶች

07/01/2024

ብጣሿ ወረቀት

ለንደን ከተማ ውስጥ ጥሩ ኑሮ የሚኖሩና አላህን እጅግ ፈሪ የሚባሉ እናትና ልጅ ነበሩ፤ ልጁ በመንግስታዊ ድርጅት ውስጥ የሚሰራ ሲሆን፤ እናቱም አብራው ትኖራለች፤ በዲኑ ላይም እጅግ ጠንካራና መስጂዶችም ውስጥ በጀመዓ ሰላት በስፋት የሚታወቅ ልጅ ነው።

አጋጣሚ ሆኖ ከሚሰራበት መስሪያ ቤት ለአንድ ዓመት ያህል ወደ ሌላ ሃገር ነፃ የትምህርት እድል ( scholarship ) ደረሰው። ልጁም ለጉዞ የሚያስፈልገውን ቁሳቁስ ካዘጋጀ በኋላ ለእናቱ ለወር ወጪ የሚሆን ያህል ገንዘብ አስቀመጠላትና ተሳፈረ።

ቀናትና ሳምንታት ተፈራርቀው ወር ደረሰ፤ እናትም የተቀመጠላትን ገንዘብ ለወጪ እየተጠቀመች ቢሆንም ገንዘቡ በመገባደድ ላይ ነው፤ ቀናትና ወራት እየተቆጠሩ በሄዱ ቁጥር እናት ችግሯና ረሃቧ ከምትቋቋመው በላይ እጅግ እየበረታባት መጣ። ልጁ ከተሳፈረ ስምንት ወር ሞላው፤ እናትም ማንነቷን ለመለየት በሚከብድ ያህል ተጎሳቆለች።

ይህቺ ሚስኪን እናት ችግሯ ቢጠናባት አንዲት ብጣሽ ጨርቅ መስጂድ በር አንጥፋ ከመስጂድ ከሚወጡ ሰዎች መለመን ጀመረች። ከመስጂድ ለሚወጣውም ጀመዓ ይህቺ እናት ፈፅሞ አዲስ አልሆነችባቸውም። የሆነ ቦታ እንደሚያውቋት ተረድተዋል፤ ነገር ግን ማን ናት? የሁሉም ጥያቄ ነበር። የተጎሳቆለው ሰውነቷ ማንነቷን ቀይሮታል። ነገር ግን እሷ ከመስጂድ ዘውትር የማይጠፋው የአኺራ ወንድማቸው እናት ነበረች።

ከመስጅዱ መጨረሻ የወጡት ኢማሙ ሆኑና እንዳዩዋት የዚያ ሙዕሚን ልጅ እናት መሆኗን አወቁ፤ ግራ በመጋባትም ጠጋ ብለው ምን እንደገጠማት ጠየቋት፤ እሷም የልጁን ወደ ሌላ ሃገር መጓዝና የስምንት ወር ችግርና ስቃይዋን ነገረቻቸው።

ኢማሙም እጅግ በመገረም " ልጅሽ ከሄደ በኋላ ለወጪሽ የሚሆን ገንዘብ አይልክልሽም? " ብለው ጠየቋት። እናትም " ምንም አይነት ገንዘብ ልኮልኝ አያውቅም፤ ነገር ግን በየወሩ አንዲት ብጣሽ ወረቀት በፖስታ ቤት በኩል ይልክልኛል፤ እኔም ከልጄ የተላከልኝ ወረቀት እንደደረሰኝ መልዕክቱን ሳላነብ " የውዱ ልጄ ደብዳቤ " እያልኩ እየሳምኩ መሳብያ ውስጥ አስቀምጣለሁ፤ ምክንያቱም እንግሊዝኛ ማንበብ አልችልም " ብላ ለኢማሙ መለሰች።

ኢማሙም ወደ ቤቷ ይዘዋት ሄደው ለስምንት ወራት የተላከላትን ደብዳቤ እንድታመጣ ጠየቋት። እናትም ካስቀመጠችበት መሳብያ አውጥታ ሰጠቻቸው። ኢማሙ እጅግ ተገረሙ፤ ወደሷ ዞረውም " አንቺ እናት ሆይ፦ ይህ ልጅሽ በየወሩ የሚልክልሽ ብጣሽ ወረቀት እያንዳንዱ እኮ የአንድ ሺህ ዩሮ ቼክ ነው፤ ይህ ወረቀት ማለት ባንክ ቤት ሄደሽ በገንዘብ የምትቀይሪው ነው " በማለት ገንዘቡን ከባንክ እንዴት እንደምትቀበል አስረድተው ካለችበት ችግር አወጧት።

ይህቺ እናት ስለ ቼክ ባለማወቋና ማንበብ ባለመቻሏ፤ እንዲሁም ከቼኩ ጋር ባለመግባባቷ ምክንያት ወራትን በችግርና እንግልት አሳለፈች።

አላህም ተባረከ ወተዓላ የዱንያ ሃያታችንን ሊያሳምርልን የሚችልና፤ በአኺራም ድልን ሊያጎናፅፈን የሚችል ቼክ ለእያንዳንዳችን ሰጥቶናል። የቼኩን አጠቃቀም ነቢ አለይሂ ሰላም አበብራርተው ነግረውናል።

ነገር ግን እንደዚያች እናት ከቼኩ ጋር ባለመግባባታችን ምክንያት ቼኩን ቤት አስቀምጠን ችግርና ያልተረጋጋ ህይወት እየተፈራረቀብን ነው። ይህም ከአላህ ዘንድ የተሰጠንና፥ ሃያታችንን ሊያሳምርልን የሚችለውና ሳንግባባው ቀርተን ቤት ያስቀመጥነውም ቼክ ቁርዓን ነው።

አላህ ያግባባን።
Haji Ahmedin

02/01/2024

ነቢ ሰዐወ አሉ፦
የአደም ልጅ ሞት በቀረበው ግዜ አላህ 5 መላዕክትን ይልክበታል።

ነፍሱ በመውጣት ላይ ሳለች የመጀመርያው መልዓክ ይቀርበው'ና‹‹የአደም ልጅ ሆይ! ያ ፈርጣማ ጡንቻህ የት ገባ? ዛሬ ምን አደከመው? ያ ርቱዕ አንደበትህ የት ግባ፤ ዛሬ ስለምን ተለጎመ? ዘመድ አዝማዶች አልነበሩህ! ስለምን ጭርታ ሰፈነብህ?›› ሲል ይጣራል።

የአደም ልጅ ነፍሱ ወጥታ በተከፈነ ግዜም ሁለተኛው መልዓክ ይመጣ'ና፦‹‹የአደም ልጅ ሆይ! ከሀብትህ ለድህነቴ እለት ብለህ ያጠራቀምከው የት ገባ? ለመጠለያ ብለህ የገነባኸው ህንፃህ የት ሄደ? ከወዳጅ አዝማድ የያዝካቸው ጓደኞችህ የት ጠፉ?›› ሲል ይጣራው'ና ትቶት ይሄዳል።

የአደምን ልጅ ጀናዛ ሰዎች ተሸክመው ወደ ቀብሩ ሲሄዱ ሶስተኛው መልዐክ ይመጣ'ና ይጣራል፦‹‹የአደም ልጅ ሆይ! ዛሬ... ተጉዘህ የማታውቀውን አይነት ሩቅ ጉዙ ትጓዛለህ፤ ዛሬ...ጎብኝተህ እማታውቃቸውን አይነት ሰዎች ትጎበኛቸዋለህ፤ ዛሬ... ገብተህ በማታውቀው ጠባብ መግቢያ ውስጥ ትገባለህ። የአላህ ውዴታ ከተሳካልህ ምንኛ ታደልክ፤ በአላህ ጥላቻ ከተመለስክ ዋ! መጥፋትህ!››

ሟች ከቀብሩ ገብቶ በተጋደመ ግዜ አራተኛው መልዓክ ይመጣ'ና፦‹‹የአደም ልጅ ሆይ! ትናንት ከምድር በላይ ሆነህ ስትራመድ ነበር፤ ዛሬ ከስሯ ገብተህ ተኝተኻል። ትናንት ከላይዋ ሆነህ ስትስቅ ነበር፤ ዛሬ ከስሯ ሁነህ ታለቅሳለህ። ትናንት ከላይዋ ሆነህ ስታምፅ ነበር፤ ዛሬ ከስሯ ሆነህ ትፀፀታለህ።›› ሲል ይጣራል።

ቀባሪ ቀብሮ ሲመለስ የመጨረሻው መልዓክ ይመጣ'ና፦‹‹የአደም ልጅ ሆይ! ቀበሩህ እኮ፤ ትተውህም ሄዱ። አብረውህ ቢቀመጡም አይጠቅሙህም። ንብረት ሰበሰብክ፤ ግና ለሌላ ሰው ትተኸው ሄድክ። ዛሬማ! ወይ ከላዕላይቷ ጀነት ትከትማለህ፤ አልያም ከነዲዷ ጀሀነም ትነጉዳለህ›› ሲል ተጣርቶ ይሰናበተዋል።

በ Sheik Ahmedin ተጻፈ

01/01/2024

አላህ 💚 ألله 💚 አልሏህ
=== ⨳ === ⨳ === ⨳ ===
*
أحمد محمد سيراج ✍️

በዓረብኛ ቋንቋ ድምጽ ያላቸው ተነባቢ ፊደላት "sound letters" ሃያ ስምንት(28) ሲሆኑ አጫዋች ፊደል "stretch letter" አንድ (1) ሲሆን እርሱም أ (አሊፍ) ነው።

በመካከል ስናነባቸው የሚቀጥኑ ፊደሎች አስራ ዘጠኝ(19) ሲሆኑ "ተርቂቅ" ይባላሉ፣ የሚወፍሩ ፊደሎች ደግሞ ሰባት (7) ሲሆኑ "ተፍሂም" ይባላሉ። ነገር ግን ተርቂቅ እና ተፍሂም የሆኑ ሁለት ፊደሎች አሉ
እነሱም:- ر "ራ" እና ل "ላም" ናቸው።

"ራ" ر በፈትሃና በደማ ይወፍራል በከስራ
ይቀጥናል፣ ل "ላም" ደግሞ በለፍዙል ጀላላ ማለትም የአላህ ስምን ለማንበብ የل "ላም" ፊደል ትወፍራለች። ስለዚህም "አላህ" የሚለው ቃል ልክ የዓረብኛውን የአነባብ ዘዮ ተከትለን እናንብበው ካልን፦
"አልሏህ" ( ٱللَّه ) ይሆናል።

አላህ (ٱللهَّ)የሚለው ቃል በቅዱስ ቁርኣን ላይ ሁለት ሺህ ስድስት መቶ ዘጠና ዘጠኝ (2699) ጊዜ የተጠቀሰ ሲሆን ትርጉሙም የሚመለክ ወይም አምልኮ የሚገባው ማለት ነው።

አላህ ኢስሙል ዛት (የህላዌው ስም) ሲሆን "ዛት" (ذات ) ማለት “ምንነት” ሲሆን አላህ በምንነቱ የሚመለክ ነው።

ይህ ስም በ"ኢዕራብ"إعراب (ሙያ) "case" እንዲህ ተቀምጧል:-"ፈትሐ" فَتْحَة ፣ "ከስራ" كَسْرَة ፣ "ደማ" ضَمَّة በሚባሉ አጭር አናባቢ ፊደሎች ላይ ያገለግላሉ።

"መንሱብ"المنصوب (ተሳቢ ሙያ) "accusative case"፦ በፈትሐ የሚያገለግለውን(ሙያ) ስንጠቀም አላህ የሚለው ቃል "አልሏَህ" (ٱللهَّ)ይሆናል።

"መጅሩር"المجرور (አገናዛቢ ሙያ)"genitive case"፦ በከስራ የሚያገለግለውን (ሙያ)ስንጠቀም
"ሊልሏሂ"( اللَّهِ) ይሆናል።

"መርፉዕ"المرفوع (ባለቤት ሙያ)"nominative case"፦ በደማ የሚያገለግለውን (ሙያ) ስንጠቀም ደግሞ "አልሏሁ"( اللَّهُ) ይሆናል።
ለምሳሌ፦ "አሏሁ-ማ"( ٱللَّهُمَّ )ማለት
"ያ-አልሏህ"( ياالله) ማለት ነው።

"አልሏህ"(ٱللهَّ) የሚለው ቃል የትኛውም መስራች ፊደል ከላዩ ላይ ቢቀነስ ትርጉም ይሰጣል።

"አልሏህ"( ٱللهَّ) በሚለው መነሻ የመጀመሪያውን አንድ ፊደል ስንቀንስ “ሊልሏህ” (لله)የሚል ይሆናል፡፡ ትርጉሙም “ለአላህ” ማለት ነው።

"አልሏህ"(ٱللهَّ ) ከሚለው የመጀመሪያዎቹን ሁለት ፊደሎች ስንቀንስ ደግሞ ውጤቱ "ለሁ"( لَهُ ) የሚል ይሆናል፡፡ ትርጉሙም "የእርሱ"ማለት ነው፡፡

"አልሏህ"(ٱللهَّ ) በሚለው የመጀመሪያዎቹን ሶስት ፊደሎችን ስንቀንስ ደግሞ ውጤቱ "ሁ"( هُ ) የሚል ሲሆን፥ ትርጉሙም "እርሱ" ማለት ነው፡፡

"አልሏህ"(ٱللهَّ ) ከሚለው ውቅር ቃል መሀል ከሁለቱ የ"ላም"(ل) ፊደሎች አንዱን ስንቀንስ "ኢሏህ"( إِلَٰه ) የሚለው ይሆናል፤ ትርጉሙም "አምላክ" ማለት ሲሆን “ኢሏህ” የሚለው ቃል መቶ አርባ ሰባት (147) ጊዜ በቅዱስ ቁርኣን የተጠቀሰ ሲሆን ተባታይ ነው፤ አንስታይ ሲሆን ደግሞ "ኢሏሃህ" (إلاهة) ነው፤ የ"ኢላህ" ብዙ ቁጥር ደግሞ "አሊሀህ" ( آلِهَةٌ ) ነው። "ኢላሃህ" (إلاهة )በተለያየ አገናዛቢ ተውላጠ ስም ላይ ሲመጣ፦ "ኢላሂ" ( إِلَٰهي ) "አምላኬ"
"ኢላሁና"( إِلَٰهُنَا ) "አምላካችን"
"ኢላሀከ"( إِلَٰهَكَ ) "አምላክህ"
"ኢላሀኩም" (إِلَٰهُكُم)ْ "አምላካችሁ"
"ኢላሀሁ"( إِلَٰهَهُ ) "አምላኩ"
"ኢላሀሁም"( إِلَٰهَهُمْ ) "አምላካቸው"

"ኢላሃህ"(إلاهة) "አምላክ" ብሎ በመተርጉም (መጠቀም) ችግር ባይኖረውም ነገር ግን "አልላህ"(ٱللهَّ) የተፀውዖ ስም ስለሆነ ይህን መጠቀም እጅጉን የተሻለ ነው፦

{"ከአላህ" ጋር ሌላን "አምላክ" አታድርግ፤ የተወቀስክ ረዳት የሌለህ ትሆናለህና።}(17:22)

{لَّا تَجْعَلْ مَعَ ٱللَّهِ إِلَٰهًا ءَاخَرَ فَتَقْعُدَ مَذْمُومًۭا
مَّخْذُولًۭا }

{"ከአላህም" ጋር ሌላን "አምላክ" አትጥራ......}28:88

{ وَلَا تَدْعُ مَعَ ٱللَّهِ إِلَٰهًا ءَاخَرَ ۘ .......}

{"ከአላህም" ጋር ሌላን "አምላክ" አትጥራ፤ ከሚቀጡት ትኾናለህና።}26:213

{فَلَا تَدْعُ مَعَ ٱللَّهِ إِلَٰهًا ءَاخَرَ فَتَكُونَ مِنَ ٱلْمُعَذَّبِينَ}

# ከአህመድ ሙሐመድ ሲራጅ

30/01/2023

ስጋ ለባሽ ሰው እንደመሆኔ መጠን፣ አንዳንድ ጊዜ የጤና እክል አጋጥሞኝ አልጋ ላይ በምውልበት ሰዐታት ወዲያው ትዝ የሚለኝ የሞት ነገር ነው፡፡

..ስታመም የምሞት የምሞት ይመስለኝና ስጋት መጥቶ ሽው ይልብኛል፡፡

ሞት ከኀያሉ አላህ በቀር ለየትኛውም ፍጥረት የማይቀር ዕዳ መሆኑ እየታወቀም፣ መምጣቱ ላይቀር አጥብቀን እንፈራዋለን፡፡

ስታመም ስለ ሞት በስፋት፣ በጥልቀትና በምልአት ማሰላሰል እጀምራለሁ፡፡

በተለይ ነፍሴ ከሥጋዬ ተነጥላ ከተለየችበት ቅጽበት ጀምሮ መቃብር ውስጥ እስከምጣል ድረስ ያለው አጭር ሰዐታት ይበልጥ የሚያስፈራ መስሎ ይታየኛል፡፡

.ለምሳሌ እንበልና ..

ማምሻውን መግሪብ ላይ ብሞት ቀብር ተወስጄ የምጥጣለው በበነጋው ዕኩለ ቀን ዙሁር ሰዐት ወቅት ነው ማለት ነው፡፡

ከማምሻው እስከ በነጋታው ዙሁር ድረስ ያለው አጭር ሰዐታት ከሌላው ሁሉ ይበልጥ የሚያስፈራ መስሎ ይታየኛል፡፡

ማታ ነው...ወዲያው መሞቴ ከተረጋገጠ በኀላ ሰዎች ገለል ያለ ቦታ ወስደው ጋቢ አልብሰው ሲያስተኙኝ፣ አስክሬን የማጠብ ልምድ ያላቸው የማላውቃቸው ሰዎች ተፈልገው መጥተው፣ እሳሳለት የነበረውን ገላዬን፣ እሸሽገው የነበረው ኀፍረቴን እያገላበጡ በቀዝቃዛ ውሃ ሲያጥቡኝ ይታየኛል፡፡

ከዚያም ከፈን አምጥተው ይጠቀልሉኛል፡፡

እንደነገሩ ጠረኑን የምወደው ሆነ የማልወደው ሽቶ አርከፍክፈውብኝ (ብዙ ጊዜ አስክሬን ላይ የሚርከፈከው ሽቶ አይጥመኝም፡፡ ሽታው ቋቅ ይለኛል፡፡) ቃሬዛ ላይ ጥለውኝ የሆነ ምንጣፍ ነገር ሲያከናንቡኝ ይታየኛል፡፡

ከዚያማ በኀላ ወደ ቀብር የመጥጣያ ሰዐቴን መጠባበቅ ነው፡፡

. ዒሻእ፣ ..ሱብሒ ከሩቁ አዛን ሲል ይሰማኛል፡፡

ቃሬዛ ላይ ተጋድሜያለሁ፡፡ መተንፈስ የለ፣ መናገር የለ፣ መንቀሳቀስ የለ...አስፈሪ ነው፡፡

.........

ለመሆኑ ሰው ሲሞት ስጋው ምን ይሆናል?...

..ሳይንስ እንዳረጋገጠው ከሆነ፣ ሰው ልክ ሲሞት ወዲያው የልብ ምቱ ቀጥ ይላል፡፡

ከሁለት ሴኮንድ በኀላ እክሲጅን ሰውነቱ ውስጥ መሰራጨት ያቆማል፡፡ ከዐሥር ሴኮንድ በኀላ የሰውነት ሙቀት መቀዝቀዝ ይጀምራል፡፡

ከሁለት ደቂቃዎች በኀላ የሰውነት ቅዝቃዜ በኀይል እየጨመረ ይሄዳል፡፡ ከሠላሳ ደቂቃ በኀላ በሰውነታችን ውስጥ ያለው ደም መርጋት ይጀምራል፡፡

ከሁለት ሰዐታት በኀላ ጡንቻዎች መሰነጣጠቅ ይጀምራሉ፡፡ ከዐሥራ ኹለት ሰዐታት በኀላ ሴሎቻችን በሙሉ ይሞታሉ፡፡

ከሁለት ቀናት በኀላ ሆዳችን እንደ ፊኛ ውጥርጥር ይላል፡፡ የቆዳ ቀለማችን እየተለወጠ ይመጣል፡፡ የተለያዩ ነፍሳት ሰውነታችን ላይ እንቁላላቸውን መጣል ይጀምራሉ፡፡

ከሦስት ቀናት በኀላ ነፍሳቱ የጣሏቸው እንቁላሎቹ ወደ ትላትልነት ይለወጣሉ፡፡

ከአራት ቀናት በኀላ ቆዳችን መሰንጠቅ፣ ጥፍሮቻችን መርገፍ፣ ፀጉራችን መነቃቀል፣ አፍንጫችን ደም ማመንጨት ይጀምራል፡፡

.እጅግ የሚከረፋ..

ከአምስት ቀናት በኀላ ሰውነታችን እጅግ ዘግናኝ የሆነ ግማትና ክርፋት ማመንጨትና ማትነን ይጀምራል፡፡

. ስፍርና ቁጥር የሌላቸው ኁልቆመሳፍርት ትላትሎች ከሰውነታችን ፈልቀው ወጥተው ገላችን ላይ መርመስመስ ይጀምራሉ፡፡

ከስድስት ቀናት በኀላ ቆዳችን ከሰል መስሎ ይጠቁራል፡፡

ከስምንት ቀናት በኀላ ጡንቻዎቻችን እንደ ጨው መሟሟት ይጀምራሉ፡፡

ከዘጠኝ ቀናት በኀላ ከእያንዳንዱ የሰውነታችን ቀዳዳ ደም ማዠት ይጀምራል፡፡

ከዐሥራ አንድ ቀን በኀላ የውስጥ የሰውነት ብልቶቻችን በሙሉ ፍርስርሳቸው ይወጣል፡፡ ይፈርሳሉ፡፡

ወደ ፈርስነት ይለወጣሉ፡፡

ከዐሥራ ኹለት ቀን በኀላ አጥንቶቻችን መሰነጣጠቅ ይጀምራሉ፡፡

ከዐሥራ አራት ቀን በኀላ ከሰውነታችን የፈለቁት ስፍርና ቁጥር የሌላቸው ኁልቆመሳፍርት ትላትሎች የገማና የከረፋው ሥጋችንን ሙጥጥ አድርገው መብላት ይጀምራሉ፡፡

ከአንድ ዓመት በኀላ ሙሉ ለሙሉ ፍርከስክሳችን ወጥቶ ወደ አፅምነት እንለወጣለን፡፡
.....

ቃሬዛ ላይ ተጋድሜ ይታኛል፡፡ መተንፈስ የለ፣ መናገር የለ፣ መንቀሳቀስ የለ...አስፈሪ ነው፡፡

ነጋ፡፡

ረፋድ ሆነ፡፡ ሰዐቱ ይጣደፋል፡፡

የሰዎች የለቅሶ ድምፅ ይሰማኛል፡፡ ብዙዎቹ ሴቶች መሰሉኝ፡፡ ሰዎች እየተንጋጉ መጥተው የተኛሁበትን ቃሬዛ ተሸክመው እያካለቡ አወጡኝ፡፡ መኪና ላይ ተጫንኩ ፡፡ ሰዐቱ ይጣደፋል፡፡

መስጊድ ተወሰድኩ፡፡ ተሰገደብኝ፡፡ ሰዎች ግርር ብለው መጥተው የተኛሁበትን ቃሬዛ ተሸክመው እያካለቡ ከመስጊዱ አስወጡኝና ወደ መቃብሩ ጉድጓድ ይዘውኝ ተጣደፉ፡፡

ሰዐቱ ይጣደፋል፡፡ ሰዎቹ ይጣደፋሉ፡፡ ጥድፊያ ነው፡፡ ያከናነቡኝን ምንጣፍ ገለጥ አድርገው ከቃሬዛው ላይ ጎትተው በማውረድ ጉድጓድ ውስጥ አጣድፈው ጣሉኝ፡፡ ተዘጋብኝ፡፡ በዚሁ ተፈጸመ፡፡

ድቅድቅ ጨለማ!!!

..ብንን አልኩ.. ....
© Abubeker Alemu

11/01/2023

‹‹ጉዞ ላይ ነኝ። የበረሀው ንዳድ በአፌ ውስጥ ያለውን ምራቅ ሳይቀር አድርቆ በውሃ ጥም ልሞት አፋፍ ላይ ደረስኩ።›› ይላሉ ጀይላኒይ።

በዚህ ሁኔታ ላይ ሳለሁ ድንገት ጥቁር ደመና ከበላዬ አጠለለችኝ። ከደመናዋ ውስጥ የሚነፍሰው ቀዝቃዛ ነፋስ አፌን በምራቅ ሞላው።

‹‹አብዱል ቃዲር ሆይ! እኔ ጌታህ ነኝ›› የሚል ድምፅ ከደመናዋ ውስጥ ተስተጋባ።
‹‹እውን ያ ከእርሱ ሌላ አምላክ የሌለ የሆነከው ጌታ ነህን?›› ብዬ በድንጋጤ ጠየቅኩኝ።

‹‹አብዱል ቃዲር ሆይ! አዎን እኔ ጌታህ ነኝ። እነሆ እርም የተባሉ ነገራትን ሁላ ላንተ ፍቁድ አድርጌልኃለሁ›› የሚል ድምፅ ከደመናዋ ውስጥ ተሰማኝ።

‹‹ዋሸህ። አንተ የአላህ ጠላት ሸይጣን ነህ›› አልኩት። ይህን ግዜ ያች ያጠለለችኝ ደመና ተበታትና ተነነች። ከዝያም እንዲህ የሚል ድምፅ ከኋላዬ ተሰማኝ፦‹‹ዐብዱል ቃዲር ሆይ! ዐሊም በመሆንህ ዛሬ ተርፈኃል። ካንተ በፊት ተመሳሳይ ፈተና የፈተንኳቸው 70 ሰዎች ከዲን ወጥተዋል።››

ይህን ክስተት ያዳመጡ ሰዎች፦‹‹እንዴት ሸይጣን መሆኑን አወቅክበት›› ብለው ጀይላኒን ጠየቋቸው።
ጀይላኒም፦‹‹"እርምን ፍቁድ አድርጌልኃለሁ" ሲለኝ አወቅኩት፤ ምክንያቱም ከነቢ ሰዐወ በኋላ ማንም ህግጋትን ሊቀይር አይችልም›› ብለው መለሱላቸው።

ቀደሰሏሁ ሲረሁ!

© Sefwan Sheik Ahmedin

ምንጭ፦
مدارج السالكين

11/01/2023

ልምከርህ!

ይህ ፈተና በበዛበት ዘመን በማንም ፍቅር አትዋልል። ከሰዎች ጋር ያለህን ውዴታ ፈር አስይዘው፤ ስትወድም ድንበር አትለፍ ስትጠላም እንደዝያው። ሚዛንህንም ጠብቅ።

ዛሬ ያለ ገደብ የወደድኸው ነገ ዋና ጠላትህ፤ ዛሬ ያለ ገደብ የጠላኸው ነገ ዋና ወዳጅህ ሊሆን ይችላል'ና ገደብ ይኑርህ።

የትኛውንም አካል በገዛ የልብህ ዙፈን ላይ ተቆጣጣሪ አድርገህ ለፍቅር አትሹመው፤ አላህ እና ነቢ ሰዐወ ሲቀሩ። ከዘመድም ይሁን ከወዳጅህ ፈፅሞ መልካምን ውለታ ብቻ አትጠብቅ። መሬቶች ናቸው'ና የዘራህባቸውን ነው እሚያበቅሉልህ።

‹‹ከአላህ ወልዮች አንዱ ነህ›› ብለው ቢያወድሱህ ወይም ‹‹የመናፍቃን ቁንጮ ነህ ›› ብለው ቢዘልፉህ ለውዳሴውም ለዝልፍያውም ግድ እንዳይኖርህ። ትክክለኛውን አንተነትህን ስለማይቀይሩት!

‹‹ከሰው እማይጨመር ተኮፋሽ ነህ›› ብለው ቢያብጠለጥሉህ እንኳ ከፈተናው ዘመን ወጀብ ለመሸሽ የመረጥከውን የብቸኝነት ጀልባ ውደደው። ከወጀቡም ያሻህን መርጠህ ከጀልባህ አኑረው ግና ድንበር ይኑርህ።

በዙርያህ ከሚያንዣብቡ የፍጡራን ሰላቢዎች ተላቀቅ፤ ሰላቢውንም ተሰላቢውንም በፅሞና እያስተነተንክ ተመልከታቸው። የጌታንም የማስተናበር ጥበብ እዝያ ውስጥ እየው።

ገፅታዎች አይሸውዱህ። ልትይዝ የሻኸውን ሁሉ ገልፀህ ተመልከተው፤ ገፅታ ሸዋጅ ነው'ና!
ስንቱ ዘንጦ ውስጡ የበከለ አለ። ስንቱ ልብስ ነትቦ ውስጡ የነፃ አለ!

ልቦች የሚስጥራት መክተምያ ናቸው፤ ሚስጥራት በመላ አላህ እጅ ውስጥ ናቸው። በገፅታ እንዳትሸወድ።

በአንተነትህ አላህ አቻ የሌለህ ልዩ አድርጎ ፈጥሮኻል። አንተም አላህን ያለ አቻ አምልከው።

© Sefwan Sheik Ahmedin

11/01/2023

ዑመር ኢብኑል ከጣብ በሒምስ የሚኖሩ ድሆችን ለመደጎም ፈልጎ የድሆችን ስም ዝርዝር መዝግበው እንዲያመጡለት ባዘዘው መሰረት ተመዝግቦ ተሰጠው።

የስም ዝርዝሮችን ሲመለከት ከመሀል የሒምስን ግዛት የሚያስተዳድረው ገዥ ሰዒድ ኢብኑ ዓሚር ስም ተፅፎ አገኘ።(የአንድ ግዛት አስተዳዳሪ ከድሆች ተርታ)

ዑመር ትክዝ አለ...፤ ወደ ሰዎቹም ዞር ብሎ፦ «የአንድ ትልቅ ግዛት አስተዳዳሪ ሁኖ እንዴት ከድሆች ተርታ ተሰለፈ?»

«ሙሉ ደመወዙን ለድሆች ያከፋፍል'ና ተው ስንለው " ታድያ ምን ላድርግ አላህ ፊት ስለነሱ ስጠየቅ መልስ የለኝም" ይላል። » በማለት ሁኔታውን ለዑመር አስረዱት።

«እሱ ላይ የምታቀርቡት ስሞታ አለ?» በማለት ጠየቃቸው።

ሰዎቹም፦ «ሶስት ስሞታዎችን ብቻ እናቀርባለን።
1፦ረፋድ ላይ ነው ከቤቱ ሚወጣው
2፦በማታም ጭራሽ ይሰወርብናል
3፦በሳምንት አንድ ሙሉ ቀን ይሰወርብናል»

ዑመር የሒምሱን አስታዳዳሪ ጠየቀው፦ «የቀረበብህ ስሞታ ትክክል ነው?»

አስተዳዳሪ፦ «ትክክል ነው ያ አሚረል ሙእሚኒን!
1፦ረፋድ ላይ ነው ከቤቱ ሚወጣው' ላሉት እኔ ከቤት አርፍጄ የምወጣው ሚስቴ በሽተኛ ናት፤ አገልጋይ ስለሌለኝ ስራ ስሰራ ነው ማረፍደው።

2፦በማታም ጭራሽ ይሰወርብናል' ላሉትም እኔ ቀኑን ህዝብ ሳገለግል እውላለሁ፤ ማታውን ግን ጌታዬን አመልክበታለሁ።

3፦በሳምንት አንድ ሙሉ ቀን ይሰወርብናል' ላሉትም እኔ አንዲት ልብስ ብቻ ናት ያለችኝ፤ እሷን በሳምንት አንድ ቀን አጥባት'ና እስክትደርቅ ምለብሰው ስለሌለኝ ቤቴ ቁጭ እላለሁ።»

ኮስታራው ዑመር ይህን ሲሰማ ፂሙ በእንባው መርጠብ ጀመረ።

ይህ አስተዳዳሪ ከረሱላችን ሰዐወ ዩኒቨርስቲ የወጣ ምሩቅ ነው። ሰዒድ ኢብኑ ዓሚር
©Sefwan Sheh Ahmedin

11/01/2023

ስለራሳችን ሲባል መንቃት ያስፈልጋል!



በነገራችን ላይ እኛ ኮትኩተን የምናሳድገው እስልምና የለም። እኛም የምናከስመው እስልምና የለም። በስሙም ማደግና መበልጸግም ራስን እንጂ እምነቱን ፈቀቅ አያደርገውም።

እናስ .... ካልከኝ!

እኛ በስሙ (በእምነቱ) የምር (በኢኽላስ) ጥቂት ጥረት ካደረግን ሁሉም ነገር ወደ ልኩ መመለሱ አይቀሬ ነው። በምድር ላይ ያለው ፍጥረት ኹሉ ለርሱ ተገዢና እርሱን የሚያወድስ ነውና። ብዙዎች (ሌሎች የሚፈልጉን) በሚድያ ሲመለከቱን እንደኛ "ጥንካሬና ብርታት" ያለው ያለም አይመስላቸውም። ግና መልእክተኛው (ሰዐወ) እንደገለጹት እንደ ባሕር ላይ ዐረፋ (ምንም ኃይል የለሽ) የተባልነው ዘመን ይህ ይሆን እንዴ እላለሁ። ኃይል ሲባል አዕምሮ ሮጦ የሚሄደው (ተቋም፣ገንዘብ፣ሐብት ...) አስፈላጊነቱ የማይካድ ቢኾንም ሐሳቤ ግን የመንፈስ ከፍታና ሐብት ማለቴ ነው። የማይሰራው ተዓምር የለምና!

ከሳምንት በፊት ወደ ተፈጥሮ እምነታቸው የተመለሱ ሰዎች የተሰባሰቡበት መድረክ ላይ ተገኝቼ ጥቂት ልባሞችን ሳደምጥ በጣም ነው ራሴን የታዘብሁት። ያለማንም ሰበካና ሰበብ በአላህ ሒዳያን የተጎናጸፉ ሰዎች የሚያወሩትን እንዴት እንደተመለሱም ሲያወሩ ስሰማ የራሴን ዋስትና ተጠራጠርሁት። (ዋ ነፍሴ)

አንዳንድ ጊዜ የምንመስለው እኮ ሁሉ ነገሩ እንደተረጋገጠለት ያህል ነው። መንፈስ (ኢማን) ሲደክም ከሚያመጣው ነገሮች መካከል ድርቀት አንዱ ነው። መደንደን ከባድ ነው። መስጂዶቻችን ስለ ተቋምና ስለአስተዳደር በብዛት የሚወራባቸውን ያህል ስለ ትውልዱ ዕጣፈንታ (ኢማን) ተጨንቆ ስለኢማን የሚለፋ ማግኘት እየከበደ ነው። (የሚያስፈራ ግን እውነት) ጥረቶች ቢኖሩም በተለያየ ምክንያት እንዲኮላሽ ይደረጋል። (ውስጣዊ ላይሆን ይችላል ማጤን ነው።)

በተለያዩ ቦታዎች ላይ ሙስሊሞች ከእምነታቸው እንዲያዘነብሉ ይሰበካሉ። እንደምንሰማው ከሆነ አንዳንድ ቦታዎች ደግሞ ጨርሶ አላህን ለምን ተገዛችሁ በሚል መልክ ጭቆናን ያስተናግዳሉ። (የምድር ሱና ቢኾንም)

መስጂዶቻችን መንፈሳዊነት ርቋቸዋል፣ ወጣቶች በየአከባቢው መድረሳ ተገኝተው የተለያዩ ዕውቀቶች ላይ ከመቆየት ይልቅ ሚድያ ላይ ተጠምደናል። እኛ ላይ ብዙ የሚጠነስሱ ኃይሎች መንደር ላይ ጨርሰው ወደ ውጭ ሲያንጸባርቁ የእኛ ትርምስምስ ደግሞ ከሚድያ ጫጫታ ወደ መሬት ለመውረድ እናስባለን። ሁሉ ነገራችን ሜዳ ተዘርግፏል። በየቦታው ሸሐዳ የናፈቃቸው በርካቶች እያሉ ዛሬም ከኢማን የመነጨ እንቅስቃሴ ከማድረግ ይልቅ ነፍሲያ እየተጫወተብን እንገኛለን።

እስልምናን የሚኸድም ሰው በቅድሚያ ታግሎ መርታት ያለበት የራሱን ሸሕዋት (ዝንባሌዎች) ነው። ከዚያ ቀጥሎ ለአላህ ዲን የሚበጀውን ኹሉ መጠበቅና መንከባከብ አለበት። በምንም መመዘኛ ሁሌም መቅደም ያለበት ኢማን ነው። ኢማን ነው በፍጥነት መሰራጨት የሚችለውና በተለይም በዘመናችን ቁስና የተለያዩ መለኪያዎች ምን ያህል እንደሚያስከፍሉ ነጋሪ አያስፈልጋቸውም።

ቅድሚያ ለኢማን ሲባል ?

ዘወትር በምናደርጋቸው ማንኛውም እንቅስቃሴዎች ላይ ኢማን የማናገኝባቸው ከሆነ ኢማን ወደ ምናገኝባቸው መንገዶች ለመሄድ እንጣር። እስልምናን የምንኸድመው በዚህ መልኩ ነው። ራሳችን የማንጠቀምበት ኢስላም ሌሎችን መጥቀም አይችልም። በጥበብ ሥራ ሆነ በበጎ አድራጎት፣ በዳዕዋና ማስተማር ሆነ በማንኛውም ዘርፍ እኛ በኢማን የማናድግበት ሥራ ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናልና ከነፍስያ ጣጣዎች የምንጠበቅበትን መንገድ እንምረጥ እላለሁ።

ያስረዳን እርሱ ♥
© Best Kerim

11/01/2023


#ሰባሕ

ብዙ ጊዜ የምንሰራቸውን ስህተቶች የተለያየ አመክኖ በመስጠት ማመን አንፈልግም። ከዚያም በላይ ለማስተባበልና የሰራነውን ወንጀል መልካም እንደሆነ ለማሰብም ይዳዳናል። በወንጀላችን ሰበብም በግልጽ የሚደርሱብንም ቅጣቶች ማስተዋል ያቅተናል። ነፍሳችን የለመደው ኸይር ድንገት ሲቋረጥ፣ ከአላህ ጋር ያለ ግንኙነት ሲሳሳ፣ አንዳች የመረበሽና የድብርት ጠባይ እኛ ላይ ሲመጣ፣ አላህ በሰጠን ነገሮች አለመርካት ከተደጋገመ ግድየለም እነዚህንና ሌሎች የደረሱብንን ነገሮች የመጡብን በወንጀሎቻችን ሰበብ ይሆናሉና መለስ ብለን ወደራሳችን እንመልከት።

አላህ (ሱወ) እንዲህ ይላል፦

[ሌሎችም በኃጢአቶቻቸው የተናዘዙ መልካም ሥራንና ሌላን መጥፎ ሥራ የቀላቀሉ አልሉ፡፡ አላህ ከእነሱ ጸጸታቸውን ሊቀበል ይከጀላል፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡] አልተውባህ፤102

ኃጢአት መናዘዝ ሲሉ የተተረጎመው ቁርአኑ "ኢዕተረፉ" የሚለውን ሲኾን ወንጀላቸውን አምነው ለርሱ በመተናነስ ዝቅ ብለው የተለማመጡትን ነው። ከመልካም ሥራዎቻችን መካከል ስለተቀላቀሉ ጥፋቶች ዘወትር ከእርሱ ደጃፍ እርሱን መለመንና ለጥፋት ይቅርታን መለመን የኸይር በራፍን ይከፍታል።

የለሊት አምልኮዎች በትክክለኛ ዓላማቸው ለመጎናጸፍ ይህ ወሳኙ መንገድ ነው። በግልጽ ሆነ በስውር የምናጠፋቸው ብዙ ወንጀሎች ይኖራሉና ሁሌም ከመለመን፣ ሁሌም ከመተናነስ ደጃፍ አንራቅ!

አላህ ያስረዳና ♥
©Best Kerim

10/01/2023

ለ ባ ለ ህ ሊ ና ኢራቃዊው መምህር መኪናውን በማሽከርከር ላይ እንዳለ የትራፊክ ፖሊስ አስቆመው።የፖሊስ መኮንኑ አስፈላጊ የመረጃ ሰነዶችን ተቀብሎ የፀሐይ መነፅሩን እንዳደረገ ማንበብና መፈተሽ ቀጠለ።መኮንኑ ከአሽከርካሪው ባለ ጉዳይ ጋር ያሳየው መስተጋብር ፍፁም ጨዋነት የተሞላበት ነበር።ዝርዝር ሁኔታውን ባለ ጉዳዩ መምህር እንደሚከተለው ይገልፀዋል፦
ቀበቶ አላሰርክም አለኝ። አዎ አላሰርኩም በጣም አዝናለሁ ይቅርታ አልኩት።ህገወጥ ነው አለኝ ። እኔም አዎ አምናለሁ ደንብ በመተላለፌ ቅጣት ይገባኛል አልኩት።መኮንኑ የቅጣት ማዘዣ ወረቀቱን መፃፍ ቀጠለ።በመካከሉ ፦ አንተ የስነ ትምህርት ( ኢጁኬሽን) መምህር ነህ አይደል? አለኝ።መሆኔን አረጋገጥኩለት።አንድ ተማሪ በፈተና ቢያጭበረብር ይቅርታ ታደርግለታለህ? አለኝ። እንደማላደርግለት ነገርኩት።ምን ታደርገዋለህ? ሲለኝ በህጉ መሠረት እቀጠዋለሁ አልኩት።የፃፈውን የቅጣት ወረቀት እየሰጠኝ ፦ አንዴ ከመኪናህ መውጣት ትችላለህ?አለኝ።ግራ በመጋባትና በማመንታት ወጣሁለት።ሳላስበው በድንገት እቅፍ አድርጎ ግንባሬን ሲስመኝ የምለውንና የምሆነውን አጣሁ።ከዚያም፦ ጋሼ እኔኮ ያንተ ተማሪ ነበርኩ ብሎ ስሙን ጠቀሰልኝ።ቀጥሎም፦ ካንተ ልጅ የፈተና መልስ ስቀበል ደርሰህብን ወዳውኑ እርምጃ ወሰድክ።የፈተና ወረቀታችንን ነጥቀህ ዜሮ በመስጠት እኔንም ልጅህንም ቀጣኸን።ህጉን ሁለታችንም ላይ ሳታዳላ ተገበርከው።ከዚያች ዕለት ጀምሮ ህግ የሚወጣው ማንንም ከማንም ሳይለይ (በራስ ልጅ ላይ እንኩዋ ቢሆን) ሊተገበር መሆኑን ተገነዘብኩ።በዚያች ዕለት በኔና በልጅህ ላይ በወሰድከው ፍትሀዊ እርምጃ፣ስላንተ ባደረብኝ የአክብሮት ስሜትና በፈፀምኩት ጥፋት በመፀፀት አልቅሻለሁ።
እናም ጋሽዬ ዛሬም በአንተ ላይ ያለ ምንም አድሎ ህግን አስከብራለሁ።በልጄም ላይ ቢሆን እንኩዋ ። ብሎ ንግግሩን አሳረገ።
እኔ እንባዬን መቆጣጠር አቃተኝ።ይህ የፖሊስ መኮንን ከቀድሞ ተማሪዎቼ አንዱ መሆኑና ህግ ማስከበር ወይም መተግበር ምን ማለት እንደሆነ በመገንዘቡ እጅግ በጣም አስደሰተኝ።እሱም በበኩሉ ስሜቱ በመነካቱ እንባ ቢተናነቀውም፣ከለበሰው ወታደራዊ ዩኒፎርም ጋር እንባ ማፍሰስ ስለማያምርበት በግድ ተቆጣጠረው።
ከሁዋላ ኪሱ የተወሰነ ገንዘብ አውጥቶ፦ ጋሼ ይህንን ስጦታዬን እንድትቀበለኝ በመሀላ እማፀንሃለሁ አለኝ።እኔ እምቢ አልኩት ። እሱም እምቢ አለኝ።እኔ በአንተ ላይ ህጉን አስከብሬያለሁ የመቀጮውን ገንዘብ ግን እኔ እሸፍናለሁ አለኝ።አንተ መምህሬ፣አባቴ፣አርአያዬ ነህ።የራስ ዘውዳችን ስለሆንክ አላህ እድሜና ጤና ሰጥቶ ያኑርህ በማለት መልካም ምኞቱን ገለፀልኝ።ከኔ እምቢታ የሱ እምቢታ በረታ።ሁኔታውን በተመስጦ ሲያስተውል የነበረው የስራ ባልደረባው በግፊቱ(በጫናው) ተባበረው።
ውስጤ በአስደናቂ ስክነትና አጥለቅላቂ ደስታ ተሞልቶ ፣በስራውና በአገሩ ላይ ክህደት የማይፈፅም ትውልድ ከተማሪዎች መገኘቱ ያሳደረብኝን ልዩ የእርካታና የክብር ስሜት የገለፅኩበትን እንባዬን እያፈሰስኩ ተለየሁዋቸው....
(بغداد اليوم/A H H)
© Awwal Hamza Hamza

10/01/2023



መውላና ሸይኽ ረመዳን ቡጢይ (ረሒመሁላህ) ተጠየቁ

ፍቅር ማለት ወደ አላህ መቅረብ፣ በእርሱ መደሰትና መርካት ከሆነ ታዲያ አላህን መፍራት ቦታው የት ነው? አላህን የሚወድ ሰው እርሱን አለመፍራት ይሆንለታል?

ሸይኽ በተለመደው ኢንኪሳራቸው (ዝግ ያለ ትህትናቸው) እየተናነቃቸው የመለሱት መልስ ልብ ይንጣል ....

ለአንድ ሙሒብ (የአላህ ወዳጅ) የሚወደውን ነገር እንደማጣት፣ በሚወደው ፈጣሪ እንደመተው፣ ከበራፉ እንደመባረር ወይም ከደምሥሩ የቀረበውን አብሮነት እንደመነፈግ ያለ ግዙፍ ፍራቻ አይኖረውም።

ሱብሐነላህ!

የአላህን ውዴታ በውስጣችን አለመሰማት፣ ከእርሱ እዝነትና በረከት መነፈግ አብሮነቱን ለውስጥ ባዳ መሆን ለዓሪፎቹ በጣም አስፈሪ ነው። በፍቅሩ እየኖሩ፣ በስሙ ብዙ ተጀሊያት ውስጥ እየዋኙ ሁሌ ስጋት፣ ሁሌ ለቅሶ ላይ ናቸው።

ዋ ነፍሴን ላሳበጥኳት ... በ " እኔ" እብሪት ውስጥ ለነከርኳት፤ በአውቃለሁ፣ እበልጣለኹ፣ እመራለኹ ባሕር ውስጥ ላስገባኋት ...

ነፍስ ከአላህ ጋር የምትገናኘው ስትሰበር ነው። ችግርና መከራን አትጥሉ፣ እንግልትና ፈተናዎችን በጸጋ ተቀበሉ ይላሉ ዓሪፎቹ ምክንያቱም ከአላህ ጋር መቃረቢያ ከአላህ ጋር ተናንሶ ለማውጋት መንገድ ናቸውና!

አላህ ያስረዳና ♥
© Best kerim

09/01/2023

ማከማቸትን ስለ መውደድ!

#ጥሞና

መሰብሰብ፣ ማከማቸት፣ ማጠራቀም፣ መስገብገብ ስለምንወድ በረካ አናገኝም። ከመሰብሰብና ከማከማቸት ባለን መጠቃቀም፤ ዝም ብሎ ከማጠራቀም ባለው ነገር ወደ ተግባር መቀየር መልመድ አስፈላጊ ነው። ይህ ለየትኛውም ነገር የሚሰራ ነው። ወደ ነፍስ ስናመጣው አንድ ምሳሌ እናምጣ።

በስልካችን ላይ ልንመለከታቸው ወይም ልናነባቸው ያዘጋጀናቸው ስንት ሰነዶች አልሉ? ቁጥር የለውም አይደል? የላፕቶፓችን ስክሪኖች በቤታችን ያሉ ያልተጠቀምንባቸው ነገሮች ምን ያህል ናቸው? ያልለበስናቸው አልባሳትና ጫማዎች፣ ያልተጠቀምናቸው ቁሳቁሶችስ? ምን ያልሰበሰብነው ነገር አልለ?

የሰው ልጅ መሰብሰብ ይወዳል። ከሁሉም በላይ ገንዘብ ላይ ያለውን ልቅ ያለፈ ውዴታ አስመልክቶ አላህ በአልፈጅር ቁጥር 20 ላይ እንዲህ ይላል፦

وَتُحِبُّونَ ٱلۡمَالَ حُبّٗا جَمّٗا
[ገንዘብንም ብዙን መውደድ ትወዳላችሁ፡፡]

ከገንዘብ ሰደቃና ዘካ እንኳን የመጣው ይህን ሰዎች የመሰብሰብና የማከማቸት ባሕሪያቸውን እንዲተዉና ከስግብግብነት እንዲጠበቁነት ነው። አለማከማቸት፣ ያለጥቅም ላይ ነገሮችን አለማከማቸትን የሚለማመዱ ሰዎች ባሕሪያቸውም እንዲሁ ነው።

አንዳንድ መጥፎ ባሕሪያትንም ማከማቸት እንወዳለን። መለወጥ እንወዳለን መንገዱ ላይ መልፋትን እንጠላለን። ይህ ነገሮችን ማግበስበስ "ነገ" ማለትን ያመጣል። የሆነ ነገር አነባለሁ ያልህ ጊዜ አሁን አንብበው፣ ለመስጠት፣ ለመክፈል፣ ለመሔድ፣ ለመወሰን ሐሳብህን አታከማች። ገንዘብ ለሥራና ለመረዳዳት እንዲሁም ለመጠቃቀም ሲሆን በውስጡ በረከት አለው ሲከማች ዘካ እንደሚያገኘው ኹሉ ያለጥቅም የሰበሰብነው ዕውቀት፣ መሥራት እየቻልን ሳንሰራ ያጋበስናቸው ዐቅሞቻችን ኹሉ "ዘካ" ይፈልጋሉ።

በዚሕ መነጽር እኛ የዛሬ ነንና ከማከማቸት እሳቤ እንውጣ ለነገ (አኺራ) የምናስቀድመውም ብዙ ነገሮች ይኑረን። ለዛሬ የቤተሰብ ምቾት የምንጨነቀውን ያህል ለመጪው ትውልድና ለአኺራም የምናወርሰውን ኢማን እናጢን ትላንት የሐገራችን መሻኢኾች ለአባቶቻችን ኢማንን አወረሱ፤ አባቶቻችን የነበራቸው ዕውቀት ታላቁ ኢማን ስለነበር ዛሬ መድረስ ቻለ። ዛሬ የቁስ ዕድገት ብቻ ለትውልድ መሻገር አይችልም መንፈሳዊነትና ኢማንን ለማሻገር ዛሬ እንትጋ መጪው ትውልድ የአባቶቻቸው ነጸብራቅ ናቸውና!

አላህ ይርዳና ♥
© Best Kerim

Want your school to be the top-listed School/college in Addis Ababa?

Click here to claim your Sponsored Listing.

Location

Telephone

Website

Address


Megnagna
Addis Ababa