ይሖዋ ይርኤ፡ የሚያዘጋጅ አምላክ ዘፍጥረት 22፡14
"ይሖዋ ይርኤ" የሚለው ስም በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ከምንገነዘባቸው የእግዚአብሔር ስሞች ሁሉ እጅግ ጥልቅ፣ ልብን የሚነካና የተወደደ ስም ነው። ይህ ስም የተገኘው ከምሁራን ምርምር ወይም ከሥነ-መለኮት ትምህርት ቤት አይደለም፤ ይልቁንም አንድ አባት ብቸኛና ተወዳጅ ልጁን መሥዋዕት ለማድረግ ተራራ በወጣበት፣ እጅግ ከባድ ከሆነው የእምነት ፈተና ማዕከል ውስጥ የፈለቀ ነው። በዚያ ሁሉን ነገር ለእግዚአብሔር አሳልፎ በሰጠበት የፍጹም መታዘዝ ቅጽበት፣ እግዚአብሔር በዘመናት ሁሉ ሲያስተጋባ የሚኖር ማንነቱን ገለጠ፤ እርሱ የሚያይ፣ አስቀድሞ የሚያዘጋጅ፣ እና በጊዜው የሚያቀርብ ታማኝ አምላክ ነው!
ስለዚህ "ይሖዋ ይርኤ" የሚለው ስም ዝም ብሎ በዕውቀት የምንረዳው ጽንሰ-ሐሳብ ብቻ ሳይሆን፣ ወደ እምነት የተጠራንበት መለኮታዊ ግብዣ ነው። ይህ ግብዣ፣ የመታመንን ተራራ እንድንወጣ፣ ከእርሱ ይልቅ አጥብቀን የያዝነውን ማንኛውንም ነገር ከእጃችን እንድንለቅ፣ እና ሙሉ በሙሉ ለእርሱ እጅ በምንሰጥበት ስፍራ አምላካችንን እንድናገኝ የሚጠራን ነው።
አብርሃም በእምነት አይኖቹ ወደ ፊት ተመልክቶ በከፊል የተገለጠለትን ዝግጅት አየ። እኛ ግን ዛሬ ወደ ኋላ መለስ ብለን፣ መለኮታዊው ዝግጅት ሁሉ ፍጻሜውን ባገኘበት በክርስቶስ ኢየሱስ ላይ ዐይኖቻችንን ተክለን በምስጋና እንሞላለን። የእግዚአብሔር በግ የሆነው ኢየሱስ፣ "ይሖዋ ይርኤ" በሚለው ስም ውስጥ ያለውን የተስፋ ቃል ሁሉ በራሱ ፈጽሞታል። ከዚህም አልፎ፣ እያንዳንዱ ጥማታችንና ናፍቆታችን በዘላቂነት በሚረካበት አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፣ የእግዚአብሔር ህልውና የሁሉ ነገር ሙላት ወደሚሆንበት ወደዚያ ታላቅ የክብር ቀን በተስፋ ወደ ፊት እንመለከታለን።
"እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል... እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም... የቀድሞው ሥርዓት አልፎአልና።"
ራእይ 21፡3-4
የህይወት ቃል ህብረት
Our staffs at
ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ጥልቅ የሆነ ግንኙነት ለመፍጠር ለሚወዱ እና ሁሉምን አማኞች ለማገናኘት የተዘጋጀ መንፈሳዊ ድህረ ገጽ ነው። ይህ ህብረት የእግዚአብሔርን ሕያው ቃል በጥልቀት ለማየትና እና በእምነት ለመመላለስ የሚያስችል መንፈሳዊ መድረክ ነው። ዋና ዓላማችን የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት በመካከላችን በመፈለግ በመንፈሳዊ ህይወታችን እንድናድግ መርዳት ነው
የሲና ተራራ እና የጽዮን ተራራ
የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ፣ የድነትን ታሪክ ጫፍ በሚያሳይበት በ12፥18-29 ባለው ክፍል፣ እጅግ አስገራሚ የሆኑ ሁለት ተራራዎችን ያነጻጽራል። አንደኛው፣ እስራኤላውያን በሙሴ ዘመን የቆሙበት የሲና ተራራ ነው (ዘጸ. 19፥16-25)። ይህ ተራራ በእሳት የሚነድ፣ በጥቅጥቅ ጨለማና በዐውሎ ነፋስ የተዋጠ፣ የእግዚአብሔር ድምፅ በነጐድጓድ ሲሰማ ሕዝቡን በሽብር ያንቀጠቀጠ ተራራ ነበር። እኛ ግን የደረስነው እዚያ አይደለም። በአዲስ ኪዳን ጸጋ ወደተገለጠው የክብር ተራራ ነው የደረስነው፡ "ወደ ሰማያዊቱ ኢየሩሳሌም፣ በደስታም ወደ ተሰበሰቡት ወደ አእላፋት መላእክት፣ በሰማያትም ወደ ተጻፉት ወደ በኵሮች ማኅበር፣ የሁሉም ዳኛ ወደሚሆን ወደ እግዚአብሔር... የአዲስም ኪዳን መካከለኛ ወደሚሆን ወደ ኢየሱስ፣ ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገር ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል" (12፥22-24)።
ይህ ንጽጽር ጂኦግራፊያዊ ሳይሆን፣ ሁለት ኪዳናትን የሚያሳይ ታላቅ መንፈሳዊ ሥዕል ነው። "ሲና" አሮጌውን የሕግ ሥርዓት ይወክላል፡ በሚያስፈራና በሚያሸብር መለኮታዊ መገለጥ፣ ርቀትንና መገፋትን የሚያሳይ ነው። "ጽዮን" ግን አዲሱን የጸጋ ሥርዓት ይወክላል፡ የአቤል ደም "ፍረድ፣ ተበቀልልኝ" ብሎ ሲጮኽ፣ የክርስቶስ የኪዳን ደም ግን "ምሕረት፣ ይቅርታ፣ ዕረቅ" እያለ ይናገራል። ወደዚህ የደስታና የጸጋ ጉባኤ በክርስቶስ በኩል በቀጥታ ገብተናል! ሆኖም ይህ ታላቅ ጸጋ የራሱ የሆነ የከበደ ማስጠንቀቂያ አለው (12፥25-29)። ይህችን ዓለምና ሥርዓቷን የሚያናውጥ የፍርድ ቀን ይመጣል፤ በዚያን ጊዜ የሚጸናው በእምነት የተቀበልናትና ማንም የማያናውጣት የእግዚአብሔር መንግሥት ብቻ ናት። ለዚህ ታላቅ ጸጋ የሚገባው ምላሻችን፣ በማመስገን፣ በአክብሮትና በፍቅር እግዚአብሔርን በሕይወታችን ማምለክ ነው (12፥28-29)።
"ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም ነውና፤ ለእርሱ ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን።" ሮሜ 11፥36
የሕይወታችን፣ የመዳናችን፣ የትንፋሻችንና የጸጋችን ሁሉ ብቸኛ ምንጭ እግዚአብሔር ነው። ይህ እውነት ማንኛውንም ዓይነት "በገዛ ጥረቴ እድናለሁ" የሚል አድካሚ የሰውኛ ትምክህትና ራስን የማጽደቅ ሙከራ ከንቱ ያደርገዋል። እኛ የጸጋው ተቀባዮች እንጂ የጽድቅ ፈጣሪዎች አይደለንም። ፍቅር የጀመረው ከእኛ ሳይሆን ከእርሱ ነው፤ ድነታችን የፈለቀው ከልቡ አሳብ ነው። ዛሬ ላለንበት ማንነትና ለመንፈሳዊ ሕይወታችን፣ ብቸኛው የውሃ ልካችን የእርሱ ጸጋ ብቻ ነው!
ሕይወት ሁልጊዜ አልጋ በአልጋ አይደለችም። ዛሬ እያለፍንበት ያለው ግራ የሚያጋባ፣ ምናልባትም አሳማሚ የሆነ የሕይወት ምዕራፍ ሊኖር ይችላል። ነገር ግን ይህ ቃል አንድ ጽኑ ተስፋ ይሰጠናል። ማዕበሉን የሚገስጽ፣ ታሪካችንን የሚመራ፣ ፍጥረትን በስልጣኑ ቃል ደግፎ የያዘ ሉዓላዊ አምላክ አለን! ነገሮች ሁሉ በዘፈቀደ አይሆኑም፤ ሁሉም ነገር በእርሱ ጥበብና መግቦት ስር የሚያልፍ ነው። በመከራችንም ሆነ በደስታችን ውስጥ እርሱ ፈጽሞ ዙፋኑን አልለቀቀም፤ ሁሉ በእርሱ እጅ የተያዘ ነው!
የነገሮች ሁሉ ማጠቃለያ፣ የፍጥረትና የቤዛነት ታላቁ ግብ፣ የዘመናት ሁሉ ፍጻሜ ማረፊያ፣ የእግዚአብሔር ስም መክበር ነው። ይህ ማለት፣ ታሪካችን፣ ልፋታችንም ሆነ አገልግሎታችን ወደ አንድ ታላቅና ክቡር መዳረሻ እየተጓዘ ነው። ራሳችንን የምናስደስትበት ወይም የራሳችንን ስም የምናገንበት "ሰውን ማዕከል ያደረገ" ክርስትና የለንም። በመጨረሻው የዘመን ጫፍ፣ የፍጥረታት ሁሉ ጉልበት የሚንበረከከው፣ ምላስም ሁሉ የሚመሰክረው ለአንድ አላማ ነው፤ ለእርሱ ክብር!
የሰው ልጅ አእምሮ በመለኮታዊ ጥበብ ጥልቀት ውስጥ እስከ መጨረሻው አቅሙ ሲለጠጥ፣ አመክንዮአዊ ክርክር መለኮታዊ ምሥጢርን የመፍታት አቅሙን ሲያሟጥጥ፣ በዚያን ጊዜ የሚቀረውና ፍጹም በቂ የሆነው ብቸኛ ድርጊት- አምልኮ ነው!
-ጌታ ሆይ፣ አንተ የሁሉ ነገር ጀማሪ፣ የሁሉ ነገር ደጋፊ፣ የሁሉ ነገር ፈጻሚ ነህ። አእምሮዬ መንገዶችህን ሁሉ ተረድቶ ላይጨርስ ይችላል፤ ነገር ግን ልቤ አንተን በማምለክ ያርፋል። የሕይወቴ ታሪክ ከእርሱ ተነስቶ በእርሱ አልፎ ለእርሱ እንደሚሆን አምናለሁ። ለእርሱ እስከ ዘላለም ድረስ ክብር ይሁን! አሜን!-
የቤተ ክርስቲያን መሠረት
የቤተ ክርስቲያን መጀመሪያና መሠረት በሰው ልጅ ድንገተኛ የፈጠራ ችሎታ፣ በማኅበራዊ ስምምነት ወይም በታሪካዊ አጋጣሚ ላይ የተመሠረተ ምድራዊ ክስተት አይደለም። ይልቁንም ቤተ ክርስቲያን ከዘላለም ዓለም በማይናወጥ መለኮታዊ ተነሳሽነትና ምክር የታቀደች የቃል ኪዳን አካል ናት።
ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በራሱ በኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን፤ እርሱም የዘላለም ወልድ እንደመሆኑ፣ በአብ ፈቃድና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የእግዚአብሔርን ቤዛዊ ዓላማዎች በታሪክ ውስጥ ለመፈጸም ይህንን የተቀደሰ ማኅበረሰብ በምድር ላይ ተክሏል። በማቴዎስ 16፥18 ላይ “ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ” የሚለው የክርስቶስ ግልጽና ኃይለኛ ቃል፣ የምሥረታዋ ምስጢር በሰዎች ዕቅድ ላይ የተመካ ሳይሆን፣ ከእርሱ ሉዓላዊ የፈጠራ ሥራ የመነጨ ነው።
ክርስቶስ የቤተ ክርስቲያን ብቸኛ መሐንዲስ፣ ሕጋዊ ባለቤትና የማይሻር ጌታ ነው ። በምሥረታዋም ሆነ በአስተዳደሯ፣ በሕይወቷም ሆነ በተልእኮዋ ላይ ፍጹም የበላይ ሥልጣን ያለው እርሱ ብቻ ነው። ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ደም የተገዛችና በእርሱ ቃል የምትመራ በመሆኗ፣ ምንጩም መድረሻውም እርሱ የሆነ ሰማያዊ ተቋም ናት።
"እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚህም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሏትም።" (ማቴ. 16:18)
"ቸር ነውና፥ ምሕረቱ ለዘላለም ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ" መዝሙር 107
መዝሙር 107 "አመስግኑት" በሚል ጥሪ ተጀምሮ፣ "ያስተውላል" እና "ይጠብቃል" በሚል ጥሪ ያበቃል። በእነዚህ ሁለት ዋልታዎች፣ ይኸውም በምስጋናና በማስተዋል መካከል፣ ሙሉው መንፈሳዊ ሕይወት ይገኛል።
የዚህ መዝሙር እጅግ ዘላቂ ስጦታ አዝማቹ ነው። ጩኸት፣ እርስ በርስ የሚፎካከሩ ትረካዎችና የማያቋርጥ ትኩረት የሚሰርቁ ነገሮች በሞሉባት ዓለም ውስጥ፣ መዝሙረኛው አራት ጊዜ ወደዚያው ወደ አንድ የማይናወጥ እውነት ይመልሰናል፦ ምሕረቱ (ጽኑ ፍቅሩ) ለዘላለም ነውና፤ ድንቅ ሥራዎቹም ለሰው ልጆች ናቸው።
እነዚህ ተራ የሃይማኖት አባባሎች አይደሉም። ከምድረ በዳ፣ ከእስር ቤት፣ ከሕመም አልጋና ከማዕበል ተጋድሎ የወጡ ሕያው ምስክርነቶች ናቸው። በሕይወታቸው እጅግ አስከፊ በሆኑት ጊዜያት፣ እግዚአብሔር ልክ ቃሉ እንደሚለው መልካም እና ቸር መሆኑን በተግባር ያዩ ሰዎች የእምነት ቃላት ናቸው።
በእግዚአብሔር የተዋጁት "ይናገሩ" (ቁ. 2) ተብለው ተጠርተዋል። በዝምታ ወይም በድብቅ ሳይሆን፣ በአደባባይ፣ በምስክርነት፣ በእግዚአብሔርና በሚመለከተው ዓለም ፊት እንዲህ እንዲሉ ተጠርተዋል፦ አዳነኝ፤ ፈወሰኝ፤ ማዕበሌን ጸጥ አደረገ፤ ወደ ቤቴም መራኝ።
መዝሙሩ እግዚአብሔር ለምን አንዳንዴ እነዚህን ማዕበሎች እንደሚያዝዝ ማብራሪያ አይሰጥም። የሚሰጠን ዋስትና ይህንን ነው፦ ማዕበሉን የሚያዘው አምላክ፣ ጸጥታውንም ያዛል።
ዐውሎ ነፋሱን ጸጥ አደረገ" (ቁ. 29)። ይህን ሲያደርግም፣ ሕዝቡን "ወደ ፈለጉት ወደብ" ይመራቸዋል:። ዝም ብሎ ወዳ ማንኛውም ወደብ ሳይሆን ወደ ፈለጉት ወደብ፤ ልባቸው በዚያ ሁሉ አስፈሪ ጉዞ ውስጥ ሲመኘው ወደነበረው ወደብ።
በማዕበሉ ውስጥ ታመነው። በማዕበሉ ውስጥ ጩኽ። እርሱ አልተለየህም። እርሱ የማዕበሉ ጸሐፊም ጸጥ አድራጊውም ነው።
ከአቴና እስከ አዲስ አበባ፡ የ21ኛው ክፍለ ዘመን ዲጂታል ጣዖታት
የሐዋርያው ጳውሎስ መንፈስ በአቴና ጎዳናዎች ላይ ሲመላለስ በጣዖት ብዛት እንደተበሳጨ ሁሉ (ሐዋ 17፡16)፣ ዛሬም በኢትዮጵያ ወጣቶች የዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ የሚታዩት "ዘመናዊ መሠዊያዎች" መንፈሳዊ ቅንዓትን የሚቀሰቅሱ ናቸው። በጥንቷ አቴና ሰዎች አዲስ ነገር ለመስማትና ለመናገር "አጎራ" (የገበያና የሕዝብ መሰብሰቢያ ስፍራ) ይሄዱ ነበር። ዛሬ ያ ስፍራ በስማርት ስልኮቻችን ውስጥ በሚገኙት TikTok, youtube, FB እና Instagram ተተክቷል።
የsocial media ስልተ-ቀመር (Algorithm)፣ እንደ ጥንቶቹ አቴናውያን ሁልጊዜ "አዲስ ነገር" እንድንፈልግ (ሐዋ 17፡21) አእምሯችንን አደንዝዞታል። ወጣቱ ትርጉም ባለው ሕይወት ፋንታ በ"Views"፣ "Likes" እና "Viral" በመሆን አባዜ ተጠምዷል። Filter የተደረገ ሕይወትን በማሳየት፣ ወጣቱ የራሱን ማንነት እንዲጠላና በሰው ሕይወት እንዲቀና የሚያደርግ የዘመናችን "የውበትና የዝና ጣዖት" ሆኗል።
የኤፊቆሬዎሳውያን እና የኢስጦኢካውያን ተጽዕኖ በኢትዮጵያ
ጳውሎስን የተከራከሩት እነዚያ ሁለት ፍልስፍናዎች ዛሬም በሀገራችን ወጣቶች መካከል በሰፊው ይንጸባረቃሉ፦
1- ዘመናዊ ኤፊቆሬዎሳውያን የምንላችው የሥጋ ደስታ ፈላጊዎች ናችው። "ዛሬን ብላ፣ ጠጣ፣ ተዝናና፤ ነገ እንሞታለንና" የሚለው አስተሳሰብ በሱስ፣ በዝሙትና በጭፈራ ቤቶች ባሕል ውስጥ ሰርጎ ገብቷል። "Enjoy" ማድረግ ብቸኛው የሕይወት ግብ ሆኗል።
2- ዘመናዊ ኢስጦኢካውያን የምንላችው ተስፋ ቢሶች ፣ ተስፋ የቆረጡትን ነው። በሀገራችን ባለው የኢኮኖሚ ቀውስ፣ የሥራ አጥነት ጫና እና የፖለቲካ አለመረጋጋት ምክንያት ብዙ ወጣቶች "ምንም አይመጣም፣ ዕድላችን ነው" በሚል ተስፋ መቁረጥ ውስጥ ወድቀዋል። ይህም ራስን ለጨለማና ለሰይጣን ፈንታ አሳልፎ የመስጠት መንፈስ ነው።
ብዙ ወጣቶች ከቤተክርስቲያን እየራቁ "መንፈሳዊ ነኝ ግን ሃይማኖተኛ አይደለሁም" ወደሚል አደገኛ ቀጠና እየገቡ ነው። እውነተኛውን አምላክ በቃልና በሥርዓት ከመፈለግ ይልቅ፣ በYouTube ፖድካስቶች፣ በ"Self-help" መጻሕፍትና በሥነ-ልቦና ምክሮች ውስጥ የነፍስ እረፍትን ይፈልጋሉ።
ለኢትዮጵያ ክርስቲያን ወጣቶች የቀረበ ጥሪ
የጳውሎስ ምላሽ ከአቴና መሸሽ አልነበረም፤ ይልቁንም ወደ አርዮስፋጎስ መሃል በመግባት ወንጌልን በድፍረት መናገር ነበር። ዛሬም ለኢትዮጵያ ወጣቶች የቀረበው ጥሪ፦
1- ከስማርት-ፎን መቅደሶች ውጡ፤ ሕይወት በስክሪን ላይ በሚታይ "Scroller" የሚለካ ሳይሆን በእግዚአብሔር ፊት በሚኖር ቅድስና የሚመዘን መሆኑን አስተውሉ።
2- በጣዖት ፊት አትስገዱ፦ ለታዋቂ ሰዎች (Celebrities)፣ ለሀብትና ለዝና የሚሰጠው አምልኮአዊ ክብር ተገቢው ለእግዚአብሔር ብቻ ነው።
3- ባሕልን ገምግሙ፦ ክርስቲያን ወጣት ማለት ዓለም የሚግተውን ሁሉ የሚውጥ ሳይሆን፣ በቃሉ መነጽር ባሕልን፣ ፖለቲካንና ቴክኖሎጂን የሚመዝን መሆን አለበት።
ጳውሎስ በአቴና የቆመው ለተረት ወይም ለፍልስፍና ሳይሆን፣ ለሞተውና ለተነሣው ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ለመሆን ነበር። እኛም በዚህ በTikTok እና Instagram ዘመን፣ "በእርሱ ሕያዋን ነንና እንንቀሳቀሳለን እንኖርማለን።" (ሐዋ 17፡28) የሚለውን እውነት ለትውልዱ በተግባር ማሳየት ይጠበቅብናል።
ተባረኩ!
የመስቀል ሞት አሰቃቂነት
ጆን ስቶት "የክርስቶስ መስቀል" በሚለው መጽሐፋቸው ላይ፣ የሮማውያን ስቅለት ምን ያህል ዘግናኝ እንደነበር በታሪክ ያስረዳሉ። ሮማዊው ፈላስፋ ሲሴሮ ስቅለትን "እጅግ ዘግናኝ እና አሳፋሪ የቅጣት ዓይነት" ብሎ የጠራው ሲሆን፣ "መስቀል" የሚለው ቃል ራሱ በጨዋ ማኅበረሰብ ዘንድ የማይነሳ ጸያፍ ቃል ነበር። መስቀል ለሮማውያን ዜጎች የማይሰጥ፣ ለባሮች፣ ለአማፂያንና ለከባድ ወንጀለኞች ብቻ የተመደበ ከፍተኛ የውርደት ሞት ነበር።
ይህ እውነታ የእግዚአብሔር ልጅ የሰውን ልጅ ኃጢአት ለመሸከም ሲል፣ በዘመኑ ከነበሩት የሞት ዓይነቶች ሁሉ እጅግ አዋራጅ፣ ረጅም ስቃይ ያለበትና እርቃንን የሚያስቀር ሞት መምረጡ፤ ክርስቶስ እኛን ለማዳን እስከዚህ የውርደትና የሕመም ጥልቀት ወረደ፤ ይህ የፍቅሩን ወደር-የለሽነት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል።
የእግዚአብሔር ስም
የእግዚአብሔር ስም የእርሱን ባሕርይና መገኘት የሚወክል በመሆኑ፣ በተፈጥሮው ቅዱስ ነው። ሦስተኛው ትእዛዝ "የእግዚአብሔርን የአምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ" (ዘጸ. 20፥7) በማለት ከመለኮታዊው ስም ጋር የተያያዘውን መንፈሳዊ ክብደት ያሳያል።
ይህ ትእዛዝ የእግዚአብሔርን ስም ለራስ ሐሰተኛ ምስክርነት በመጠቀም በሐሰት መማልን፣ መለኮታዊውን ሥልጣን ለግል ጥቅም፣ ለጥንቆላም ሆነ ለሟርት መሣሪያነት በማዋል ስሙን ማቃለልን፣ እንዲሁም ያለ አምልኮ መንፈስና ያለ ተገቢው ጥንቃቄ ስሙን በመጥራት አምላክን እንደ ተራ ፍጡር መቁጠርን በጥብቅ ይከለክላል።
አለመለወጥ
የእግዚአብሔር አለመለወጥ ማለት እርሱ በባሕርይው፣ በፍጹምነቱ፣ በቃል ኪዳኑም ሆነ በዘላለማዊ ዓላማው ፈጽሞ የማይለወጥ መሆኑን የሚያረጋግጥ መለኮታዊ እውነት ነው። ነቢዩ ሚልክያስ "እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም" (ሚልክያስ 3፡6) በማለት የገለጠው ቃል፣ እግዚአብሔር በሁኔታዎች የማይናወጥ የጽናት መሠረት ነው።
በአዲስ ኪዳንም ሐዋርያው ያዕቆብ "በእርሱ ዘንድ መለወጥ በመዞርም የተደረገ ጥላ የለም" (ያዕቆብ 1፡17) በማለት፣ እግዚአብሔር እንደ ፍጥረት ዓለም የሚለዋወጥ ሳይሆን፣ ዘላቂና የማይለወጥ ብርሃን መሆኑን ያረጋግጣል። ይህ መለኮታዊ አለመለወጥ በዘፈቀደ የሚሆን ሳይሆን፣ ከእግዚአብሔር ፍጹምነት የሚመነጭ ነው፤ ምክንያቱም አንድ አካል ሊለወጥ የሚችለው ካለው ወደተሻለ ለማደግ ወይም ካለው ወደ ተባላሸ ለመውረድ ነው፤ እግዚአብሔር ግን ፍጹም በመሆኑ የሚጎድለው ነገር የለምና ሊያድግ አይችልም፣ የፍጹምነት ጥግ በመሆኑም ሊቀንስ አይችልም። ይህ ባሕርይ እግዚአብሔርን ከጊዜና ከቦታ ውሱንነት በላይ ያደርገዋል።
በጊዜ ውስጥ ያለ ነገር ሁሉ ይለወጣል፣ ያረጃል፣ ይሻሻላል ወይም ይጠፋል፤ እግዚአብሔር ግን ከጊዜ ውጭ በመሆኑ ትናንት፣ ዛሬ፣ ለዘላለምም ያው ነው (ዕብራውያን 13፡8)። ይህ መለኮታዊ ጽናት ለሰው ልጆች ትልቅ ዋስትና ነው። ለምሳሌ፦ አንድ ሰው የገባውን ቃል ኪዳን ሊለውጥ የሚችለው ሐሳቡን ስለቀየረ ወይም ቃሉን ለመፈጸም አቅም ስለሌለው ነው፤ እግዚአብሔር ግን ሁሉን አዋቂ በመሆኑ ሐሳቡን አይቀይርም፣ ሁሉን ቻይ በመሆኑም አቅም አያጣም። የእግዚአብሔር አለመለወጥ ማለት እርሱ ዝም ያለና የማይሰማ አምላክ ነው ማለት ሳይሆን፣ በባሕርይውና ለፍጥረቱ ባለው ፍቅር ላይ የማይናወጥ ታማኝ ጌታ መሆኑን የሚያረጋግጥ የሕይወት መሠረት ነው።
መንፈሳዊ ስጦታዎች እና ሹመቶች
መንፈሳዊ ስጦታዎች ለጋራ ጥቅም እና ለአገልግሎት ሥራ ለእያንዳንዱ አማኝ የሚሰጡ የጸጋ ችሎታዎች ናቸው (1 ቆሮ 12፡7፣ 11፤ ሮሜ 12፡6-8፤ 1 ጴጥ 4፡10)። የቤተክርስቲያን ሹመቶች ግን፣ ግልጽ የሆነውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ መስፈርት ለሚያሟሉና በምእመናኑ ዘንድ ተቀባይነት ላላቸው ብቻ የሚሰጡ፣ በይፋ የታወቁ የኃላፊነትና የሥልጣን ቦታዎች ናቸው። ስጦታዎች ለሁሉም አማኞች ታድለዋል። ጳውሎስ “ነገር ግን መንፈስ ቅዱስን መግለጥ ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል።” በማለት ይናገራል(1 ቆሮ 12፡7፤ ኤፌ 4፡7)።
ስጦታ ያልተሰጠው አማኝ የለም፤ ክርስቶስን ከሙታን ያስነሳው ያው መንፈስ “እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርጋል።” (1 ቆሮ 12፡11)። እነዚህ ስጦታዎች፣ ማስተማር፣ ምሕረት፣ ማስተዳደር፣ መምከር ወይም ትንቢት መሠረታቸው አገልግሎት ነው፤ የተሰጡትም በአካል ውስጥ ለማገልገል እንጂ ለግል ዝና ወይም ለግል ፍላጎት አይደለም። አማኞች ሁሉ ቤተክርስቲያንን በማነጽ ሥራ ላይ በንቃት እንዲሳተፉ ኃይል ይሰጣቸዋል (1 ጴጥ 2፡9፤ ራእ 1፡6)።
በዘመናችን ባለው የወንጌላውያን ክርስትና ውስጥ እጅግ አወዛጋቢ ከሆኑ ጉዳዮች አንዱ፣ በአዲስ ኪዳን የተገለጹት ተአምራዊ የጸጋ ስጦታዎች (ትንቢት፣ ልሳን፣ ልሳንን መተርጎም፣ ፈውስ፣ ተአምራት፣ የእውቀትና የጥበብ ቃል) ዛሬም ይቀጥላሉ፣ በከፊል? ወይስ በመጨረሻው ሐዋርያ ሞት ወይም በመጽሐፍ ቅዱስ ቀኖና መዘጋት አብቅተዋል? የሚለው ጥያቄ ነው።
በመላው አዲስ ኪዳን ውስጥ፣ የክርስቶስ ዳግም ምጽአት ከመሆኑ በፊት የጸጋ ስጦታዎች እንደሚያቆሙ የሚናገር አንድም ጥቅስ የለም። የብሉይ ኪዳን መስዋዕት እና ክህነት መሻር በዕብራውያን መልእክት በግልጽ እንደተቀመጠው ሁሉ (ዕብ. 8፡13)፣ የመንፈስ ስጦታዎችም እንዲያቆሙ ቢታዘዝ ኖሮ በግልጽ ይቀመጥ ነበር። ነገር ግን ጳውሎስ የጸጋ ስጦታዎችን “የመንፈስ መገለጥ” እና “ለጥቅም የሚሰጥ” (1 ቆሮ. 12፡7) በማለት ይገልጻቸዋል።
በ1 ቆሮንቶስ 12፡1፣ ጳውሎስ pneumatikōn የሚለውን ቃል በመጠቀም "ስለ መንፈሳዊ ነገሮች" ወይም "ስለ መንፈስ ስጦታዎች" ይናገራል። ይህ ቃል ከ pneuma (መንፈስ) የተገኘ ሲሆን፣ ሁኔታቸውን በከፍተኛ እና ከተፈጥሮ በላይ በሆኑ መግለጫዎች ለማረጋገጥ የሚፈልጉ የቆሮንቶስ አማኞች ተመራጭ ቃል ነበር። ይሁን እንጂ ጳውሎስ በቁጥር 4 ላይ charismata የሚለውን ቃል በመጠቀም ወዲያውኑ ያርማቸዋል። ይህ ቃል ከ charis (ጸጋ) የተገኘ ሲሆን፣ እነዚህ ችሎታዎች የ"መንፈሳዊነት" ወይም የብቃት ምልክቶች ሳይሆኑ፣ በእግዚአብሔር በነጻ የተሰጡ "ጸጋ" ወይም "የጸጋ ስጦታዎች" ናቸው።
ስጦታዎቹ የተሰጡት ለቤተክርስቲያን ማነጽና ለአገልግሎት ብቃት ነው። ቤተክርስቲያን ደግሞ ዛሬም ማነጽ ያስፈልጋታል። ስጦታዎች ከሌሉ ቤተክርስቲያን ወደ ደረቅ ሃይማኖተኝነት ትቀየራለች።
Click here to claim your Sponsored Listing.
Location
Category
Website
Address
AA
Addis Ababa