Rebuni ረቡኒ

Rebuni ረቡኒ

Share

doctrinal, and theological teachings of the Ethiopian Orthodox Church.

ረቡኒ ቃሉ የእብራይስጥ ሲሆን ትርጉሙም መምህር ማለት፡፡ በዚህም ፔጅ ላይ ምእመኑን ሊያስተምሩ የሚችሉ ሀይሞኖታዊ እና ማህበራዊ ጉዳዮችን ያነሳል … ከምእመናን የሚነሱለትን ጥያቄዎች የቤተ-ክርስቲያን መምህራንን በማናገር መጻህፍትን በማገላበጥ ምላሽ ይሰጣል … እባካችሁ ቤተ-ክርስቲያን ምላሽ የማትሰጥበት ጥያቄ የለምና ተገቢውን አካል እንጠይቅ እንማማር ለበለጠ መገጃ www.rebuni.com በመጎብኘት ይሳተፉ፡፡ ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን የእመቤታችን የቅዱሳን ምልጃ አይለየን፡፡

Photos from Rebuni ረቡኒ's post 19/05/2026

#ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ተሰውሯል እንጂ ሞትን አላየም

#ቅዱስ ያሬድ በሰማያት የሰማውን የመላዕክት ዝማሬ በምድር ለሰው ልጆች አስተማረ፡፡ በግዕዝ በእዝልና በአራራይ ዜማዎች አጥንትን የሚያለመልም ልዩ ዝማሬን ቀመረ፣ በወቅቶች ከፍሎና ሥርዓት ሠርቶ አበረከተልን፡፡

#ቅዱስ ያሬድ በታላቁ ንጉሥ በአፄ ገብረ መስቀል ፊት በግእዝ፣ በዕዝል በዓራራይ ዜማ በዝማሜ ሲያመሰግን ንጉሡ በዜማው ተመስጠው ዓይን ዓይኑን እያዩ ሳያዉቁት እግሩን በያዙት የብረት ዘንግ ወጉት፡፡

#ሁለቱም በተመስጦ ስለነበሩ የሆነውን ነገር አላስተዋሉትም ነበር፡፡ ዜማው አብቅቶ ሁለቱም ከተመስጧቸው ሲነቁ ዘንጋቸው በቅዱስ ያሬድ እግር ላይ ተሰክቶ ብዙ ደም ፈሶት ነበር፡፡

#ንጉሡም ደንግጠው እጅግም አዝነው “ደምህን አፍስሻለሁና የምትፈልገውን ማንኛውንም ነገር ጠይቀኝ እሰጥሃለሁ” አሉት፡፡ እርሱም “እስካሁን እግዚአብሔር በፈቀደ በዚህ ታላቅና ቅዱስ ስፍራ ቆይቻለሁ፤ ብዙ ደቀ መዛሙርትንም ተክቻለሁ፡፡

#ከእንግዲህ የቀረኝን ዘመን በጸሎትና በብሕትውና ራቅ ወዳለ ቦታ ሔጄ እየኖርኩ ፈጣሪዬን ማገልገል እፈልጋለሁ አላቸው፡፡ አፄ ገብረ መስቀልም የቅዱስ ያሬድን ቃል ሰምተው ቢዚያኑም በገቡለት ቃል መሠረት ፈቀዱለት፡፡

#ጉዞውንም ወደ ደቡብ አቅጣጫ ወደ ሰሜን ተራሮች አደረገ፡፡ በዚያም ደብረ ሐዊ በተባለው ተራራ ላይ አሁን በስሙ የታነጸው ቤተ ክርስቲያን ባለበት ቦታ በምናኔ ተወስኖ ፈጣሪውን በብሕትዉና እያገለገለ ኖረ፡፡

#በምናኔ ብዙ ዓመታትን ካሳለፈ በኋላም በጸለምት ዋሻ በአንዱ ግንቦት 11 ቀን በ571 ዓ.ም ተሠውሯል፡፡

#አምስት መጻሕፍትን የደረሰ ሲሆን የመጀመሪያው ድጓ ሲሆን የዓመቱን በዓላትና የሳምንታት መዝሙራት ተሰብሰበውና ይገኙበታል፡፡

#ድጓ ከብሉይ፣ ከሐዲስና ከአዋልድ መጻሕፍት ስለሚጠቅስ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን፣ የእመቤታችን ድንግል ማርያምን፣ የመላእክትን፣ የነቢያትንና ሐዋርያትን፣ የጻድቃን የሰማዕታትን ክብር ይናገራልና፡፡

#ጾመ ድጓ በዐቢይ ጾም ወቅት በማለዳ፣ በሦስት ሰዓት፣ በቀትር፣ በሠርክና በሌሊት የሚዘመሩ መዝሙራትን ይዟል፡፡ ነገረ እግዚአብሔርን፣ ነገረ ማርያምን፣ ነገረ ቅዱሳንን፣ ነገረ መላእክት፣ ነገረ ቤተ ክርስቲያን የሚዘከር፤ የጾምን፣ የጸሎትንና የምጽዋትን ጠቃሚነት የሚስተምር ነው፡፡

#ምዕራፍ የተሰኘው መጽሐፍ የዘወትርና የጾም ምዕራፍ ተብሎ በሁለት ክፍል የተከፈለ ሲሆን የዘወትር ምዕራፍ ዓመቱ ሳይጠብቅ በዓመቱ ውስጥ ባሉት ሳምንታትና በዓላት ወቅቱን እየጠበቀ የሚያገለግል ሲሆን የጾም ምዕራፍ ደግሞ በዐቢይ ጾመና በምሕላ ቀኖች የሚዘመር ነው፡፡

#ዝማሬ የተባለው መጽሐፍ አገልግሎት በቅዳሴ ጊዜ ከድርገት በኋላ የሚቃኝ፣ የሚዜም፣ የሚዘመር፣ የጸሎተ ቅዳሴውን ዓላማ ተከትሎ የሚሄድ የአገልግሎት መጽሐፍ ነው፡፡

#መዋሥዕት፡ አውሥአ ወይም መለሰ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጓሜውም ምልልስ፣ ማለት ነው፡፡ በፍትሐት ጊዜ ነፍስን ለማሳረግ የሚደርስ ነው፡፡ ለሙት ድርሰት ደርሶ ማዘንን ከማን አግኝቶታል ቢሉ መልሱ ከዳዊት የሚል መልስ ይሰጣል፡፡

#ከዚህም ሌላ አስሩን የዜማ ምልክቶች ሰርቶ ማንኛውም ምልክቶቹን የተማረ ሰው በቀላሉ ዜማውን እንዲረዳ አድርጎ ሰርቶልናል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በታላቅ ክብር ቅድስናውን ታከብራለች፡፡

#የቅዱስ ያሬድ ረድኤትና በረከት ይደርብን፡፡

Photos from Rebuni ረቡኒ's post 18/05/2026

#ራስን መገሰጽ የጥበብ መጀመሪያ እንደሆነ አሳይቶናል

#ማይኪራህ ወደምትባል ቦታ ሄዶ ሲደበቅ የአጎቱ ጌዲዮን ዱላ አሰልችቶት ነበር፡፡ ለሰባት ዓመታት ፊደል ተምሮ አንዲት ነቁጥ መያዝ ያልቻለ ተማሪ ቢሆንም እጅግ በመገረፉ አዘነ፡፡

#ሚያዝያ 5 ቀን በ505 ዓ.ም በአክሱም ከተማ ከአባቱ ከይስሐቅ እና ከእናቱ ከታውክልያ የተወለደው ቅዱስ ያሬድ በ7 ዓመቱ አባቱ ስለሞተ እናቱ ለአጎቱ ለጌዴዎን እንዲያሳድገውና እንዲያስተምረው አደራ ሰጠችው፡፡

#ያሬድ ከአጎቱ ዘንድ መዝሙረ ዳዊት በሚማርበት ጊዜ ስለሚቆጣውና ስለሚገርፈው መታገሥ ተስኖት ማይኪራህ ሲደርስ በአንዲት ዛፍ ሥር አርፎ ሳለ አንድ ትል ዛፉ ላይ ለመውጣት ስድስት ጊዜ ሲወድቅ ሲነሣ ከቆየ በኋላ በሰባተኛው ከዛፉ ላይ ወጥቶ የዛፉን ፍሬ ሲበላ ተመለከተ፡፡

#ቅዱስ ያሬድ የትሉን ተስፋ አለመቁረጥና ያልተቋረጠ ትጋቱን፣ ሲመለከት ራሱን ከገሠጸ በኋላ ወደ መምህሩ ተመልሶ ይቅርታ በመጠየቅ ትምህርቱን ዳግም ቀጠለ፡፡

#ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ በአጥቢያው በምትገኘው የአክሱም ጽዮን ቤተክርቲያን ዘወትር እየሄደ “ዕውቀትና ጥበብ የሚገልጽ የጌታዬ እናቱ እመቤቴ ሆይ! ዓይነ ልቦናዬን ያበራልኝ ዘንድ ለምኝልኝ” እያለ ይጸልይ ነበር፡፡

#እግዚአብሔርም የዕውቀትን መንገድ ገልጾሎት በአንድ ቀን 150ውን መዝሙረ ዳዊት፣ መኃልየ ነቢያት፣ መኃልየ ሰሎሞንና ሌሎችን ትርጓሜ መጻሕፍት የብሉያትና ሐዲሳትን ትርጓሜ መጻሕፍትን ዐወቀ፡፡

#እግዚአብሔርም በምድራውያን ሰዎች፣ በሰማያዊ ዜማ ሊመሰገን በወደደ ጊዜ ሦስት አዕዋፍ ለቅዱስ ያሬድ ግእዝ፣ ዕዝልና አራራይ የሚባሉ የዜማ ስልቶችን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት አስተምረውታል፡፡

#በመንፈስ ቅዱስ በመነጠቅም ወደ ሰማይ አርጎ ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን በልዩ ጣዕመ ዜማ ሲያመሰግኑት ሰምቶ ወደ ምድር ተመለሰ፡፡

#ከዚያም በአክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ከታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ አምላኩን እግዚአብሔርን “ዋይ ዜማ ዘሰማኩ በሰማይ ዘመላእክት ግናይ፣/ በሰማያት የሰማሁት የመላእክት ምስጋና ምን ይደንቅ! ምን ይረቅ!” በማለት በዜማው አመስግኗል፡፡

#ቅዱስ ያሬድ ሰማያዊ ዜማ በሚያዜምበት ጊዜ ካህናቱ፣ ንጉሡና ምእመናን አዲስ ነገር ሆኖባቸው፣ ምልክት ሳያገኙ እንዴት እንደሚቀበሉት ሲያስቡ ንጉሡ አምላካችን ይግልጽልን ብለው ከታኅሣሥ 1 ሰኞ እሑድ ታሕሣሥ 7 ሕዝቡ ሱባዔ እንዲይዝ አወጁ፡፡

#በየቀኑም የአክሱም ጽዮን ማርያምን ቤተ ክርስቲያን እየዞሩ ዐራት መቶ እግዚኦታና ዐርባ አንድ በእንተ ማርያም እያደረሱ ምሕላውን አካሔዱ፡፡ በሰባተኛው ቀን እሑድ ምሕላውን ጨርሰው ሲያሳርጉ ጌታ በዕለተ ዐርብ እንደተሰቀለ ሆኖ በአክሱም ጽዮን ማርያም ጉልላት ላይ ተገለጸ፡፡

#ከዚህም አያይዞ ቅዱስ ያሬድ “ዘበመስቀሉ ተቀነወ ወበነቢያት ተሰብከ መላእክት ወሊቃነ መላእክት ሰብሕዎ ኪያሁ ንሰብክ መድኅነ” ብሎ ነገረ መስቀሉን በማውሳት የወልድ ምሳሌ በሆነው በዕዝል ዜማ ዘመረ፡፡

#ትርጓሜውም ‹‹በነቢያት ትንቢት የተነገረለትና በመስቀሉ ላይ የተቸነከረው ጌታ መላእክትና የመላእክት አለቆች አመሰገኑት፤ እኛም እርሱ መድኃኒት እንደሆነ እንናገራለን›› ማለት ነው፡፡

#በዚህ በተገለጸው ምስክርነት መሠረት ዜማው ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠ መሆኑ ታምኖ ከዚያን ዕለት ጀምሮ የቅዱስ ያሬድ ዜማ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መደበኛ መገልገያ ሆነ፡፡

#የቅዱስ ያሬድ ረድኤትና በረከት ይደርብን።

17/05/2026

#የአህዮቹ ጭንቅላት ተቅያይሮ ቢገጠምም ዳግም ሕይወት ዘሩ

#ቅዱስ ቶማስ ዘመራስ የትውልድ ሀገሩ መራስ ናትና በዚያው ይጠራል፡፡ ዲዮቅልጥያኖስና መክስሚያኖስ በክርስቲያኖች ላይ መከራ ባጸኑበት ዘመን ለ22 ዓመታት ተጋድሏል።

#ይህ ድንቅ ሰማዕትና ሐዋርያ ገና በወጣትነቱ መንኖ ገዳም የኖረ፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በሰጊድ፣ ቀንና ሌሊትም በመትጋት ለድኆችና ለምስኪኖችም በመራራት ተጠምዶ የኖረ ነበር፡፡

#በጨካኞቹ ነገስታት ዘመንም ለጣኦት እንዲሰግድ የደረሰበትን መከራ ታግሶ በክርስቶስ ፍቅር በመጽናቱ ለ22 ዓመታት ባደረገው ተጋድሎ ጨለማ ውስጥ ተጥሏል።

#አካሉን እየቆራረጡ ለጣዖታቸው ያጥኑ ስለነበር 2 እግሮቹ፣ 2 እጆቹ፣ 2 ጀሮዎቹ፣ አፍንጫውና ፪ ዐይኖቹ አልነበሩም፡፡ የተጣለበትን ስፍራ የምታውቅ አንዲት ሴትም በስውር እየገባች ትመግበው ነበር፡፡

#እኛ በዘመናችን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍቅር የትኛውን አካላችን እንድንሰዋ አልጠተየቅንም፤ ወይም በረሀብ አልተቀጣንም፡፡

#ይልቁንም በነጻነት የምናመልክበት እድል እነዚህ ቅዱሳን አባቶቻችን መከራውን ታግሰው ባቆዩልን እምነት መጽናትና ቤተ ክርስቲያናችንን በተሰጠን ስጋዊና መንፈሳዊ ሃብት ማገዝ ብቻ ነው የሚጠበቅብን፡፡

#የቤተክርስቲያን የመከራ ዘመን አልፎ ንጉስ ቆስጠንጢኖስ ስልጣን ከተረከበ በኋላ በኒቂያ ጉባኤ አርዮስን ለማውገዝ ከተሰበሰቡት 318 ሊቃውንት አንዱ ቅዱስ ቶማስ ዘመራስ ነበር፡፡

#ደቀ መዛሙርቱ ስጋዊ አካሉ የጎደለውን ቅዱስ ሰማዕት በቅርጫት አድርገው በአሕዮች ጭነው ለቀናት ተጉዘው ነበር ወደ ኒቂያ የወሰዱት፡፡

#በመንገድ ላይ ሳሉም ካደሩበት ቦታ የአርዮስ ተከታዮች የአሕዮቹን ራስ ቆርጠው ገድለዋቸው ሔዱ፡፡

#ምንም እንኳን ሁለት አይኖቹ ቢጠፉም መንፈሳዊ ምጥቀቱ ከፍ ያለ ነበርና በሌሊት ገስግሰው ሊጓዙ ሲነሱ የአሕዮቹን ጭንቅላት ከአካላቸው ጋር እንዲገጥሙት አዘዛቸው፡፡

#ከዚያም ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክት አሕዮቹ እደገና ነፍስ ዘርተው ተነስተው መንገዳቸውን ቀጥለዋል፡፡

#አስገራሚው ነገር በጨለማው ምክንያት አንዱን ከአንዱ መለየት ስላልቻሉ የነጩን አሕያ ጭንቅላት ለጥቁሩ፣ የጥቁሩንም ለነጩ እንደገጠሙላቸው ጠዋት በብርሃን አዩት፡፡

#ቅዱስ ቶማስ ዘመራስም አርዮስን አውግዞ ወደ ሀገሩ ስብከቱ ተመልሶ ጸሎተ ሃይማኖት የተባለውን ጸሎት ለሕዝቡ አስተምሯል፡፡ በተጨማሪም ለ40 ዓመታት በጵጵስና አገልግሎ አልፏል፡፡

#የቅዱስ ቶማስ ዘመራስ ረድኤትና በረከት ይደርብን።

17/05/2026

ሕዝቡ እንዲሰጥ አይደለም....

Photos from Rebuni ረቡኒ's post 16/05/2026

#ደሙ ሲፈናጠቅበት የጠፋው ዐይኑ በራለት

#ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ስፍራ ቀራንዮ-ጎልጎታ አባታችን አዳም የተቀበረበት እንደሆነ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና በርካታ ዓለም አቀፍ የታሪክ ጸሐፍያን ይገልጻሉ።

#ጲላጦስ አይሁድ እንዲሰቅሉት አሳልፎ የሰጣቸው ጠዋት 3:00 ላይ ነው። በፍርድ ሒደቱ ላይ ተጽእኖ ለማሳረፍ አይሁድ ሕዝቡን ሁሉ ሲያስተባብሩ፣ የሀሰት ምስክርም አቁመው ነበር።

#መስቀል አሽክምው እየገረፉ ወስደው በእርጥብ እንጨት ሰቀሉት። ሰውን ሊያድን ሰው የሆነው ጌታ፣ በሰው ልጅ ይሙት በቃ ተፈረደበት።

#በዚህ ሁሉ ክፋታቸው ወስጥ ያልተስማሙ፣ ኢየሱስ ንጹህና ጻድቅ ሲሆን በግፍ እንደተገደለ የሚያምኑ ድርጊቱንም ያልደገፉ የራሳቸው የአይሁድ ወገኖች ነበሩ።

#በበጎ ምግባር መሳተፍና ከክፉ ምግባር መራቅ የየትኛውም ቅን ልብ ያለው ሰው መገለጫ ነው።

ከእነዚህ አንዱ ለንጊኖስ የተባለው አንድ ዐይና ወታደር ነው።

#ይህ ፈረሰኛ በዚያች ዕለተ አርብ በጌታ ላይ የሚፈጸመውን ግፍ ላለማየት ከከተማ ወጥቶ በጫካ ውስጥ ዋለ።

#ነገሮች አብቅተዋል ብሎ አመሻሹ ላይ ወደ ከተማ ሲግባ፣ የአይሁድ አለቆች ከቀራንዮ ሲመለሱ ከመንገድ አገኘቱ፤ ስለምን ከመሢሑ ሞት አልተባበርክም አሉት? እርሱም ምንም ስላላገኘሁበት አላቸው፡፡

#ከዚያም በኋላ እንደሕጋቸው እንደሚቀጡት ቢነግሩት እየሮጠ ሔዶ የጌታችንን ጎን ሲወጋው ደሙ በዐይኑ ላይ ሲፈናጠቅ ወዲያው ዐይኑ በራለት።

#ከጌታችን ጎንም ትኩስ ደምና ውሃ ፈሰሰ፣ መላእክትም ደሙን በጽዋ ቀድተው በዓለም ላይ ረጩት፤ ውሃውም ለጥምቀታችን ሆነ። ይህ መሠረት ሆኖ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታነጸው የጌታችን ደም የነጠበበት ነው፡፡

#ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ "አሁንም በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ" ያለው (ሐዋ 20÷28)፡፡

#ለንጊኖስ የልቡናው ቅንነት ነው የታየለት፤ ጎኑን መውጋቱ ዓይኑን ሲያበራለት ለኛ ደግሞ ለጥምቀታችን የሚሆነንን ማየ ገቦና በዓለም የተረጨ ደሙን አስገኘልን።

#በኋላም ለንጊኖስ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት ሰብኮ በሰማዕትነት አርፏል። በረከቱ ትደርብን።

Photos from Rebuni ረቡኒ's post 16/05/2026

#በርካቶች በስማቸው የሚጠሩባቸው ጻድቅ "ኪሮስ"

#በሀገረ ሮም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የተገኘው ወጣቱ በቀድሞ ስሙ "ዲላሶር" ይባል ነበር። ከነገስታት ወገን ቢወለድም ወላጆቹ ሲሞቱ ከወንድሙ ጋር የተካፈለውን ሃብት ለነዳያን መጽውቶ ለምናኔ ውጣ።

#ከአንዲት በዓት የራስ ፀጉሩ እስከ እግሩ የሚደርስ፣ አባ በብኑዳ የሚባል ግርማው የሚያስፈራ ገዳማዊ ወጥቶ “ኪሮስ መነኲሴ ለመሆን ወደዚህ መጣህን? አለው፡፡

#ኪሮስም ቀርቦ ተባረከና ሦስት ቀን ከቆየ በኋላ ደግሞ ጠየቀው፡፡ እርሱም “አዎ በጣም እፈልጋለሁ” አለው፡፡ አባ በብኑዳም ትንሽ ደመናን ጠርቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም በመሄድ የምንኲስናን ልብስ አምጥቶ አለበሰው፡፡

#ከአባ በበኑዳ ጋር ሰማያዊ ህብስት እየተመገቡ የኖሩት አቡነ ኪሮስ መምህራቸው ካረፉ በኋላ ለአርባ ዓመታት መሬት ላይ ተኘተው ጸልየዋል።

#ጌታችንም በአካል መጥቶ ታላቅ ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል። ከእነዚህ ቃል ኪዳኖች ዋነኛው ፈታሔ ማህጸንነታቸው ነው። በስማቸው ተማጽኖ ልጅ የሚያጣ የለም።

#ልጅ ያጡ እናቶች የጻድቁ አቡነ ኪሮስን ገድል አዝለው ቤተ ክርስቲያናቸውን በዞሩ በዓመቱ ልጃቸውን አዝለው ይዞራሉ። ታዲያ ሴትም ብትወለድ፣ ወንድም ቢወለድ ስማቸው ኪሮስ ነው የሚሆነው።

#በተለይ በትግራይ በተደጋጋሚ ለአቡነ ኪሮስ ተስለው ስለሚወልዱ በአንድ ቤት ሁለት አንዳንዴም ሦስት ልጆች ስማቸው ኪሮስ ሊባል ይችላል። በዚያ ቤትም በረከት ይሞላል።

#የጻድቁ አቡነ ኪሮስ ረድኤትና በረከት ይደርብን።

15/05/2026
Photos from Rebuni ረቡኒ's post 15/05/2026

#በእጅ የማይዳሰስ፣ በቦታ የማይወሰን፣ በሁሉም ምሉዕ ነው

#ቅድስት ሥላሴ ቅድምናቸው ዘመኑን ቢወስነው እንጂ ዘመኑ ቅድምናቸውን አይወስነውምና፡፡ ስማቸው ከአካላቸው፣ አካላቸው ከስማቸው ሳይቀድም ከዓለም በፊት የነበረ ስም ነው እንጂ ኋላ የተገኘ አይደለም፡፡

#የእግዚአብሔርን አንድነት በባህርይ፣ በህልውና፣ በፈቃድ፣ በሥልጣን፣ በመፍጠር በመሳሰሉት ነው፡፡ የሰው ነፍስ የቅድስት ሥላሴ ምሳሌ ናት፡፡

#ይኸውም አብ በልብ፣ ወልድ በቃል፣ መንፈስ ቅዱስ በእስትፋስ ይመሰላሉ፡፡ በእግዚአብሔርነቱ፤ ልብ፣ ቃል፣ ሕይወት አለ።

#ነፍስ ሶስት ባህርያት ቢኖሯትም አንድ እንደምትባል እግዚአብሔርም ሶስት ስም፤ ሶስት ግብር፤ ሶስት አካል፤ ቢኖረውም አንድ አምላክ እንጅ ሶስት አማልክት አይባልም፡፡

#ሥላሴ የሚለው ስም የአንድነትና የሶስትነት ስም ነው፡፡ በስም፣ በግብርና በአካል ሶስት እንላለን፡፡

ለአብ፣ ለወልድ፣ ለመንፈሰ ቅዱስ ለየራሳቸው ፍፁም ገጽ፣ ፍፁም መልክ፣ ፍፁም አካል፣ አላቸው።

#አካል በአጠቃላይ ሙሉው የሰውነታችን ክፍል ነው። የፍጡራን አካል የሚታይ፣ የሚዳሰስ፣ የሚመጠን፤ የሚወሰን፣ ሲሆን የሥላሴ አካል ግን፤ የማይታይ ፣ በእጅ የማይዳሰስ፣ በቦታ የማይወሰን፣ በሁሉም ምሉዕ ነው።

#በመዝሙር 138÷7 እንደተጻፈው በሁሉ የመላ ነውና፡፡ “ከመንፈስህ ወዴት እሔዳለሁ፤ ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ ወደ ሰማይ ብወጣ አንተ በዚያ አለህ፤ ወደ ውቅያኖስም ጥልቅ ብወርድም በዚያ ትገኛለህ።

#እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ ከአጽናፍ አጽናፍ ብበርም እጅህ በዚያ ትመራኛለች ቀኝህም ትይዘኛለች” ይላል፡፡

#የቅድስት ሥላሴ ምሕረትና ቸርነት አይለየን።

Photos from Rebuni ረቡኒ's post 14/05/2026

#ብርቱውን ጦረኛ ከመሬት ፈጠፈጠችው

#በዲዮቅልጥያኖስ ስር ከነበረው ንጉሥ ድርጣድስ መገኛ ከሮሜ ሸሽታ በሔደችባት አብረዋት ከነበሩ ገዳማውያን ደናግል ጋራ ካሠራቸው በኋላ እናታችን ቅድስት አርሴማን ሚስቱ እንድትሆን በብዙ ሊያታልላት ሞከረ።

#የፊቷ መልክ እጅግ ልዩ፣ ደምግባቷ ያማረ የነበረችው እናታችን ቅድስት አርሴማ ግን በመንፈሳዊ ሕይወቷ ፍጹም የበረታችና ራሷንም ለቸሩ አምላካችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ለሰማያዊ ሙሽርነት ያጨች ሆነች።

#በኋላም እመ ምኔቷን እንድታባብላት ላካት፤ እመ ምኔቷ ግን “አይዞሽ! እንዲህ ላለው ምድራዊ ኃላፊ ነገር እንዳትታለይ፤ ሰማያዊ ሙሽርነትሽንና ንጽሕናሽን አጽኚ” ብላ ይበልጥ አጸናቻት።

#ንጉሡም በግድ በኃይል መንፈስ ቅዱስ ፍጹም ኃይል ስላሳደረባት ያንን በጥንታዊ ውትድርና የጎለመሰውን ብርቱ ጦረኛ ከመሬት ፈጠፈጠችው። በሰው ፊት በመዋረዱ ያፈረው ንጉሥም እጅግ ተቆጥቶ ቅድስት አርሴማን አሠራትና ደናግሉን በፊቷ አንድ በአንድ አንገታቸውን ቀላቸው።

#እርሷ ግን በቃለ እግዚአብሔር ታጽናናቸው ነበር። ንጉሱ ባደረገው ነገር ከመሳቀቅ ይልቅ ቅዱሳኑ ሰማያዊ አክሊልን ሲቀበሉ ትመለከት ነበር።

#የእርሷንም ሁለቱን ጡቶቿን ቆረጠ፤ ቀጥሎም ሁለቱን ዐይኖቿን አወጣቸው፤ በብዙ መከራም እጅግ አሠቃያት። ንጽሕት ድንግል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልዩ የብርሃን ዐይኖችን ሰጠቻት።

#በመጨረሻም ከቀሩት ከሰባ አምስት ወንዶችና ከሃያ ሰባት ደናግል ሴቶች ጋራ መስከረም ሃያ ዘጠኝ ቀን አንገቷን ሰየፋቸውና የሰማዕትነትን የድል አክሊል ተቀዳጁ።

#ቅድስት አርሴማ በሰማዕትነት ስታርፍ ጌታችን ነፍሷን በታላቅ ክብር በመላዕክት ዝማሬ ተቀበላት፤ ራሷን ለእርሱ በሙሽርነት አሳልፋ ሰጥታለችና ብዙ ቃል ኪዳንም ሰጣት፡፡

#የቅድስት አርሴማ ረድኤትና በረከት አይለየን፡፡

Photos from Rebuni ረቡኒ's post 13/05/2026

#በሳውዲ በማያውቁት ቋንቋና ሕግ የሞት ፍርድ የተፈረደባቸውን እንታደግ

#ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርከችን

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

‹‹ተዘከሩ መቁሓነ ዘከመ ተሞቃሕክሙ ምስሌሆሙ ወእለ ተሣቀዩ ከመ ዘሀለውክሙ በሥጋክሙ፡-
ከእነርሱ ጋር አብራችኋቸው እንደታሰራችሁ ሆናችሁ እስረኞችን ዐስቡ፤ መከራ የጸናባቸውንም በሥጋችሁ ከእነርሱ ጋር እንዳላችሁ ሆናችሁ ዐስቡ››
(ዕብ. 13፡3)

እውነተኛ እምነትም ሆነ ጤናማ አመለካከት የሚመዘነው መከራ ስለሚቀበሉ ሰዎች ሰምቶና አይቶ በዝምታ ባለማለፍ፤ ይልቁንም በእነርሱ ሕመም ውስጥ ራስን በማስገባት በሚሰማው ጥልቅ ኀዘን እና በሚደረገው ድጋፍ ነው፡፡ ይልቁንም በዚች ዓለም የምንኖር ለችግርና ለመከራ ቅርብ እንደመሆናችን የታሰሩትን መጎብኘት፣ የተገፉትን ማጽናናት፣ በስደት ምድር ላይ ሆነው በሞት ፍርድ የሚጨነቁትን ወገኖች ስቃይም እንደራሳችን ስቃይ በመቁጠር ስለእነርሱ ድምፅ መሆንና ማዘን ስንችል በሰማያዊው መንግሥት የማይጠፋ የጽድቅ ዋጋን እናከማቻለን፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን!

እረኛ በበረት ውስጥ ያለችው አንዲት በግ ስትጠፋ ወይም ለአደጋ ስትጋለጥ ዝም ብሎ እንደማያይ ሁሉ፣ በሳዑዲ ዓረቢያ ምድር በሞት ጥላ ሥር ሆነው ‹‹የፍትሕ ያለህ›› እያሉ የሚጮኹ፤ በጭንቀት ቀናትን የሚቆጥሩና ድምፅ የሌላቸው ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን የተሻለ ኑሮ እናገኛለን ብለው በተሰደዱበት ሀገር ሕይወታቸው በጅምላ ሊቀጠፍ እንደሆነ መረጃውን ከልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን የተገነዘብን በመሆኑ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ጠቀሜታው የሰው ልጆችን ሕይወት ለመጠበቅ ነውና የኢትዮጵያ መንግሥት በከፍተኛ ደረጃ ከሚገኙ ከሳዑዲ ባለሥልጣናት ጋር በመነጋገር በግፍ የተፈረደባቸው ልጆቻችን የሞት ፍርድ እንዲነሳላቸውና ወደ ሀገራቸው የሚመለሱበት መንገድ ይመቻች ዘንድ የተጀመሩ ሥራዎች ልዩ ትኩረት እንዲሰጥባቸው፤ ወገኖቻችንም በቋንቋ እጥረትና በሕግ አማካሪ እጦት ለሞት እንዳይዳረጉ ከአደራ ጭምር እናሳስባለን ፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ለሰው ልጅ የሰጠው ታላቅ ስጦታ ሕይወት ነው፤ "አትግደል" የሚለው ሕግም በማንኛውም ምድርና ቋንቋ የሚሠራ ሲሆን ፍርድ ያለ ምሕረት ከሆነ አምላካዊ ቁጣን ይጋብዛልና የሳዑዲ ባለሥልጣናት የሁለቱን ሀገራት የቆየ ታሪክና ወዳጅነት አስበው፣ በሞት ፍርድ ጥላ ሥር ላሉት ወገኖቻችን ምሕረትን እንዲያደርጉ፣ ቅጣቱንም ወደ እስራት እንዲቀይሩ በአባታዊ ርኅራኄ እንጠይቃለን ፡፡

ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችም በማያውቁት ቋንቋ እንዲሁም ባልተረዱት የሕግ ሂደት ሞት የተፈረደባቸውን ወገኖች ስቃይ ተመልክተው የፍትሕ መዛባትን እንዲቃወሙና የንጹሐንን ነፍስ እንዲታደጉ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

በመጨረሻም፣ ማንኛውም በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ሰው ሕይወቱ ሊጠፋ አይገባምና ኦርቶዶክሳውያን ልጆቻችን የክርስትናችን አንዱ መገለጫ የአንደኛው ወገን ሕመምን በጋራ መካፈል እንደሆነ ተረድታችሁ ወደ ፈጣሪያችን በጸሎት እንድትማጸኑ፤ መላው ኢትዮጵያውያንም ለመፍትሔው የበኩላችሁን ጥረት እንድታደርጉ ስንል አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
አሜን።

ምንጭ፡- ማህበረ ቅዱሳን

01/12/2024

አምላካችን ሆይ ምህረትህን ላክልን፣
እንደበደላችን ሳይሆን በቸርነትህ . . . !

Want your school to be the top-listed School/college in Addis Ababa?

Click here to claim your Sponsored Listing.

Location

Category

Website

Address


Addis Ababa