AY Bible Club የወጣቶች መጽሐፍ ቅዱስ ማሕበር

AY Bible Club የወጣቶች መጽሐፍ ቅዱስ ማሕበር

Share

Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from AY Bible Club የወጣቶች መጽሐፍ ቅዱስ ማሕበር, Religious school, Ras Desta Damtew Street, Addis Ababa.

27/04/2026

ሁሉ ከንቱ
============================

📖“ሰባኪው፦ ከንቱ፥ ከንቱ፥ የከንቱ ከንቱ፤ ሁሉ ከንቱ ነው ይላል።”

— መክብብ 1፥2

የሰው ልጅ ባህሪ ያስደንቀኛል። ለዘመናት ለማግኘት የናፈቅነውን ነገር ስናገኘው በቀደመው ግለት አንቀጥልም። ደስ ይለን ይሆናል። ነገር ግን ከተወሰነ ጊዜ በኃላ ዋጋው ቀሎ ይታየናል። እንደው ባስ ሲልም ሊሰለቸን ሁላ ይችላል።

እያንዳንዱ ሰው የሕይወት ግቡ ይለያያል። ለአንደኛው ስኬት የሆነው ነገር ለሌላኛው አካል ውሃ ላያነሳ ይችላል። ሊቅ፣ ባለጠጋ፣ ዝነኛ፣ ታዋቂ ወዘተ የብዙዎች ናፍቆት ነው። እነዚህን ነገሮች በራሱ መፈለግ ምንም ክፋትም ሆነ ኃጢአት የለውም። የተሰጠንን ነገር ተጠቅሞ አጉልቶ ማውጣት በመሆኑ።

ታዲያ ከጓጓንለት ነገር ላይ ስንደርስ፣ ህልማችን እውን ሆኖ በእጃችን ስንጨብጠው እንደዛ ዋጋ የከፈልንለት ነገር ዘላለም ልባችንን እያሞቀው አይዘልቅም። የሆነ ወቅት ላይ ገንዘብ ስላለን ብቻ ሁሉን መግዛት እንደማንችል ሲገባን፣ የምድር እውቀት ውስን መሆኑን ስንደርስበት፣ ዝና ነፃነታችንን ሲያሳጣን የተመኘነው ነገር ሁሉ ዋጋው ይቀልብናል። እንደ ተራ ነገርም መቁጠር እንጀምራለን።

ሰባኪው በሕይወቱ ብዙ ነገሮችን ካየ በኃላ እንደዚህ አለ፦ “ሰባኪው፦ ከንቱ፥ ከንቱ፥ የከንቱ ከንቱ፤ ሁሉ ከንቱ ነው ይላል። ከፀሐይ በታች በሚደክምበት ድካም ሁሉ የሰው ትርፉ ምንድር ነው? ትውልድ ይሄዳል፥ ትውልድም ይመጣል፤ ምድር ግን ለዘላለም ነው። ፀሐይ ትወጣለች፥ ፀሐይም ትገባለች፥ ወደምትወጣበትም ስፍራ ትቸኵላለች። ነፋስ ወደ ደቡብ ይሄዳል፥ ወደ ሰሜንም ይዞራል፤ ዘወትር በዙረቱ ይዞራል፥ ነፋስም በዙረቱ ደግሞ ይመለሳል። ፈሳሾች ሁሉ ወደ ባሕር ይሄዳሉ፥ ባሕሩ ግን አይሞላም፤ ፈሳሾች ወደሚሄዱበት ስፍራ እንደ ገና ወደዚያ ይመለሳሉ።” (መክ 1፥2-7)

ትላንት አዲስ የሆነብን ነገር ዛሬ አሮጌ ሆኖ ይታየናል። የምድር ጉሮ በአዙሪት የተሞላ ነው። ድግግሞሽን አድምቆ በጉያው ይዟል። ትላንት ዛሬ፣ ዛሬ ደግሞ ትላንት ይሆናል። በአሁንና በቅድም ውስጥ ያለው ልዩነት ጊዜ ብቻ ነው። በፈጠነ ምድር ላይ ዘግይቶ መራመድ ዋጋ ቢያስከፍልም፣ በጊዜው ፍጥነት ልክ ሮጠን የምናገኘው ነገር ዘላለማዊ አይደለም። ሁሌ ተወዶና ተናፍቆ የሚቆይ ሳይሆን የሚለመድ ይሆናል። ሁሉም ነገር ከንቱ ነው።

ግና ትልቁ ቁም ነገር በሚያልፈው ዓለም ላይ የማያልፈውን አምላክ ጨብጦ መያዝ ነው። ይህ ከቶ ከንቱ ሊሆን አይችልም። በየማለዳው ዘውትር አዲስ ነው። የእግዚአብሔር አስደናቂ ፍቅር፣ ፀጋ፣ ይቅርታ፣ በረከት፣ ምሕረትና ቸርነት ሁሌም የሚናፈቁና የሚወደዱ ናቸው። ከቶ ሊሰለቹም ሆነ ሊለመዱ አይችሉም።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ በሚለዋወጠው ዘመን ላይ አንተ ብቻህን ፀንተህ ትኖራለህ። ትላንት የጓጓሁለት ነገር ዛሬ ቀሎብኝ ራሴን አገኘዋለሁ። አቤቱ፣ ሁሉም ነገር የከንቱ ከንቱ እንደሆነ በመረዳት ክንውኖቼን በመጠን እንዳደርግ እርዳኝ። እንዲሁም ደግሞ ከንቱነት ከነገሰበት ዓለም በመራቅ ወደ አንተ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ መቅረብ እንድችል በፀጋህ እርዳኝ። አሜን።

24/04/2026

የሰባኪው ቃል
============================

📖“በኢየሩሳሌም የነገሠ የሰባኪው የዳዊት ልጅ ቃል።”

— መክብብ 1፥1

የተኖረ ሕይወት በራሱ ትልቅ ማስተማሪያ ነው። ከአንደበታችን አንዳች ቃል ሳናወጣ በድርጊታችን ብቻ ብዙዎች ጋር መድረስ እንችላለን። ቃል ተግባር ላይ ካልዋለ ከባዶ ጩኸት ተለይቶ ሊታይ አይችልም። በዘመናት ሂደት ውስጥ የተገነባ የሕይወት ልምድና ልምምድ ግን በዝምታ ውስጥ ከፍ ብሎ መደመጥ ይችላል።

አባቴ፣ የተግባር ሰው ነበር። ከትንሽ ስፍራ ላይ ተነስቶ እንዴት መተለቅ እንደ 'ሚቻል አስተምሮኛል። "ሕይወቱ ባህር ነው" ብል እንዲሁ ፁሁፍ ለማሳመር ከቶ አይደለም። በተለያዩ የስራ መስኮች ውስጥ አልፏል። ዝቅ ብሎ ሰርቷል። ከፍ ብሎም ትዕዛዝን ሰጥቷል። በሞት ሸለቆ ውስጥ አልፏል። ማግኘትንም፣ ማጣትንም ጠንቅቆ ያውቀዋል። እናም አስታውሳለሁ የሆነ ጊዜ ላይ (ከበዙ የሕይወት ልምዶቹ በመነሳት ይመስለኛል) መቼም ከአዕምሮዬ ሊጠፋ የማይችልን ነገር ተናገረኝ። "አባ" በማለት ለስለስ ባለና ፍቅር በታከለበት አጠራር ከጠራኝ በኃላ፣ "አቶ እንድትባል ከቶ አልፈልግም። በትምህርትህ ጠንክረህ፣ ሊቅ እንድትሆን እፈልጋለሁ" አለኝ። እርሱ መማር ፈልጎ በተለያዩ ምክንያቶች ያሰበበት ስፍራ ሳይደርስ ቀርቷል። እናም ቁጭቱን ከሕይወት ልምዱ በመነሳት በእኔ በልጁ ላይ ሊወጣ ተመኘ። ምንም እንኳን የእኔን መጨረሻ በሕይወት ኖሮ ማየት አለመቻሉ ዘውትር የእግር እሳት ሆኖ ቢያንገበግበኝም "አቶ" የማልባልበት ደረጃ ላይ እየደረስኩ እንደሆነ ሳስብ በጥቂቱም ቢሆን እንኳን ለመበርታት እሞክራለሁ።

መፅሐፈ መክብብ ከሕይወት ልምድ በተነሱ ሀሳቦችና ምክር አዘል መልዕክቶች የታጨቀ ነው። የዚህ መፅሐፍ ፀሐፊው በውል ባይታወቅም፣ ሌሎች የመፅሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ስናጣቅስ ግን "ሰሎሞን" ለመሆኑ ፍንጮችን እናገኛለን። “በኢየሩሳሌም የነገሠ የሰባኪው የዳዊት ልጅ ቃል።” (መክ 1፥1) የሚለው ጥቅስም ይህንን ሀሳብ ይደግፈዋል።

በሕይወት ብንኖርና የጌታ ፈቃድ ቢሆን፣ ለሚቀጥሉት ጥቂት ወራቶች "መፅሐፈ መክብብን" እንመረምራለን፤ እንመረመራለንም። ለዚህም የሕይወት ቃል ባለቤት የሆነው አምላክ ልባችንን እንዲከፍትና ከዚህ የመፅሐፍ ቅዱስ ክፍል ራሱ እንዲያስተምረን በመፀለይ ጥናታችንን "ሀ" ብለን እንጀምራለን።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ መቼም ቸር ነህ። ዛሬም ጎደሏችንን አውቀህ እነሆ በቃልህ ልትመግበን ስለወደድህ ተመስገን። አቤቱ፣ የመክብብን መፅሐፍ ስናጠና ሳለ መንፈስህ እንዲመራንና እንዲያስተምረን እየፀለይን ይሆናል። አሜን።

23/04/2026

ማስተዋልን የሰጠ
============================

📖“በውስጡስ ጥበብን ያኖረ፥ ለሰውስ ልብ ማስተዋልን የሰጠ ማን ነው?”

— ኢዮብ 38፥36

አባት ለልጁ ብዙ ነገርን ሊሰጥና ሊያወርስ ይችላል። ነገር ግን ጥበብን ከማስተማር የዘለለ እርሱ ሊሰጠው ከቶ አይችልም። ገንዘብ፣ ሀብት፣ ቤት ከቤተሰብ ይገኝ ይሆናል። እነዚህ በራሳቸው ግን ወደ ስኬት ጎዳና አያደርሱም። ጥበብ ያስፈልጋል።

የእውነተኛ ጥበብ ባለቤት እግዚአብሔር ነው። የእውቀት መገኛው እርሱ ነው። እግዚአብሔር የዚህ ነገር ምንጩ ስለሆነ ለሌሎች መስጠት ይችላል። ልብን በሀሴት የሚሞላው ነገር ደግሞ ሲሰጥ እንዲሁ ቁጥ ቁጥ እያደረገ ሳይሆን በሙላት ነው።

ያዕቆብ ይህን በመረዳት ነበር “ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል።” (ያዕ 1፥5) በማለት በዙሪያው የነበሩ ህዝቦችን ያደመው። እግዚአብሔር ጥበብ ሰጪ አምላክ ነው። ህይወታችን በተኳለ መንገድ ይሄድ ዘንድ የምንሻ ከሆነ ጥበብን እንለምን። እርሱም ሳይሰስት በልግስና ይሰጠናል። “በውስጡስ ጥበብን ያኖረ፥ ለሰውስ ልብ ማስተዋልን የሰጠ ማን ነው?” (ኢዮ 38፥36) ተብሎ እንደ ተፃፈ። ሰጪው እርሱ ብቻ ነውና።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ “እነሆ፥ እውነትን ወደድህ፤ የማይታይ ስውር ጥበብን አስታወቅኸኝ።” (መዝ 51፥6) ተመስገን። አሜን።

22/04/2026

ሁሉን ትችላለህን?
============================

📖“በውኑ የሰባቱን ከዋክብት ዘለላ ታስር ዘንድ፥ ወይስ ኦሪዮን የሚባለውን ኮከብ ትፈታ ዘንድ ትችላለህን?”

— ኢዮብ 38፥31

የጠፈር ሳይንስ ከፍተኛ የሆነ በጀት ተመድቦለት በተቋም መልክ ስራውን ይሰራል። ጥሩ ጭንቅላት አላቸው የሚባሉ ሰዎችን በውስጡ ይዟል። ኃያላን ሀገራትም የዓለምን ስልጣን ለመቆጣጠር ይህን ስፍራ በጉልህ ይፈልጉታል።

ጠፈርተኛ፣ ፈጣሪ የሰራውን ነገር አውቆ ለሌላው ከመግለጥ የዘለለ የሚያደርገው አንዳች ነገር የለም። የፀሃይን መጠን፣ የጨረቃን ልክ፣ የከዋክብትን ብዛት ለማወቅ ይጥራል። ልኩ ይሄ ነው። አለቀ! ሊፈጥረውም ሆነ ሊያሻሽለው የሚችለው ነገር የለም። በዚህ ምድር ላይ በኖርኩበት ዘመን አንድም ቀን፣ "እንትና ጨረቃን ፈጠረ፣ ከዋክብትን ፈጠረ" ሲባል ሰምቼም ሆነ አይቼ አላውቅም። ወደ ፊትም ላይ አልችልም።

“በውኑ የሰባቱን ከዋክብት ዘለላ ታስር ዘንድ፥ ወይስ ኦሪዮን የሚባለውን ኮከብ ትፈታ ዘንድ ትችላለህን?” (ኢዮ 38፥31) የሰው ልጅ ገደብ አለው። መስራት የሚችለው ነገር እንዳለ ሁሉ መስራት የማይችላቸው ነገሮች አሉ። እኛ ሰብዓዊያን፣ ሁሉን ማድረግ ከቶ አንችልም። በእውቀት፣ በጥበብ፣ በጊዜና በሀብት የተወሰንን ነን። ሁሉን ማድረግ የሚችለው "ኤልሻዳይ" የተባለው እግዚአብሔር ብቻ ነው።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ “በውኑ የሰባቱን ከዋክብት ዘለላ ታስር ዘንድ፥ ወይስ ኦሪዮን የሚባለውን ኮከብ ትፈታ ዘንድ ትችላለህን?” ብለህ ጠየከኝ፣ እኔ ሁሉን ማድረግ ከቶ አልችልም። አቤቱ፣ በሁሉ ላይ ስልጣን ያለህ አንተ ብቻ ነህና ወደ አንተ ወጣበቅ እንድችል በፀጋህ እርዳኝ። አሜን።

21/04/2026

ሁሉን ታውቃለህን?
============================

📖“ምድርንስ በስፋትዋ አስተውለሃታልን? ሁሉን አውቀህ እንደ ሆነ ተናገር።”

— ኢዮብ 38፥18

መምህር ትውልድን በመቅረፅ ረገድ አይነተኛ የሆነን ሚና ይጫወታል። በልጆች ላይ መልካም ዘርን በመዝራት እየኮተኮተ ለቁም ነገር ያበቃቸዋል። እርሱ የቀለም አባት ነውና ልጆቹም በቀለም ደምቀው እንዲያሸበርቁ ይሻል።

አንድ ሰው ስለ መምህር ያለውን ነገር ሰማሁ። "አንድ አስተማሪ ጎበዝ ነው የሚባለው ተማሪዎቹ ከእርሱ ሲበልጡ ነው" አለ። እርሱ ያልደረሰበትን የእውቀት ልክ እነርሱ መድረስ የቻሉ ለት ትምህርቱ ግቡን መቷል።

እየሱስ፣ ታላቁ መምህራችን። የህይወትን ትርጉም ያወቅንበት አንፃራችን። ጨለማን ትተን በብርሃን መድመቂያችን። ማንም ሊስተካከለውም ሆነ ሊበልጠው የማይችል ረቡኒ። እርሱ የእውቀት ጥግ ነው። ሁሉም ነገር በእርሱ፣ ከእርሱ፣ ለእርሱ ነው።

የሰው ልጅ ሁሉን አውቆ ሊጨርስ ከቶ አይችልም። የሚያውቀው ማወቅ ባለበት ልክ ብቻ ነው። ይህ ባይሆንማ ኖሮ በጭንቀት ማዕበል ተነድተን ከዓለቶች ጋር በተላተምን ነበር። “ምድርንስ በስፋትዋ አስተውለሃታልን? ሁሉን አውቀህ እንደ ሆነ ተናገር።” (ኢዮ 38፥18) እኛ ሁሉን በሚያውቅ አምላክ ተፈጠርን እንጂ ሁሉን አናውቅም። ጥበባችንና እውቀታችን እርሱን ያከበረ ይሆን ዘንድ እናፍቃለሁ።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ የእውቀት ልኬ፣ የጥበብ አንፃሬ ነህና አከብርሃለሁ። አሰብኩት እኮ፣ ሁሉን ማወቅ ብችል ጭንቅላቴ እንደ ቆዳ ተወጥሮ ለሞት በቀረብኩ ነበር። ለእኔ የሚያስፈልገኝን የተመጠነ እውቀት ስለሰጠኸኝ ደግሞ ተመስገን። ይህን ማስተዋል እንድችል በፀጋህ እርዳኝ። አሜን።

20/04/2026

ወዴት ነበርህ?
============================

📖“ምድርን በመሠረትሁ ጊዜ አንተ ወዴት ነበርህ? ታስተውል እንደ ሆንህ ተናገር።”

— ኢዮብ 38፥4

ውስን በሆነው አዕምሯችን እግዚአብሔርን ተረድተን ልንጨርሰው አንችልም። በጊዜ ውስጥ ተወስነን፣ የጊዜን ባለቤት ልንገዳደር እኛ ማን ነን። ፍጥረት ፈጣሪን ይከስ ዘንድ በእውነት ያቻለዋልን? ሸክላ ሰሪው በሸክላው ላይ ስልጣን አለው። እርሱ በወደደው መልኩ ገጣሚ ዕቃ አድርጎ ያበጀዋል። ሸክላው ያለ ሸክላ ሰሪው ምንም ነው።

ኢዮብ ውስጡ ቆስሏል። እንክትክት ብሎ ተሰብሯል። የቀኑ ብርሃን ውስጡ ያለውን ጨለማ ማብራት ተስኖታል። ዓላማ እንዳጣ ሰው ተቆራምቶ ተቀምጧል። በዚህ ሁኔታ፣ ነገ እንኳን በህይወት ስለመኖሩ እርግጠኛ አይደለም።

እግዚአብሔር የኢዮብን ብዥታ ያጠፋ ዘንድ ወደ እርሱ መጣ። በጥያቄ ራሱን ለኢዮብ ገለጠ። “እንግዲህ እንደ ሰው ወገብህን ታጠቅ እጠይቅሃለሁ፥ አንተም ተናገረኝ። ምድርን በመሠረትሁ ጊዜ አንተ ወዴት ነበርህ? ታስተውል እንደ ሆንህ ተናገር። ብታውቅስ መሠፈሪያዋን የወሰነ፥ በላይዋስ የመለኪያ ገመድ የዘረጋ ማን ነው? አጥቢያ ኮከቦች በአንድነት ሲዘምሩ፥ የእግዚአብሔርም ልጆች ሁሉ እልል ሲሉ፥ መሠረቶችዋ በምን ላይ ተተክለው ነበር? የማዕዘንዋንስ ድንጋይ ያቆመ ማን ነው?” (ኢዮብ 38፥3-7)

እነዚህን ቁጥሮች ስንመለከት እንዲሁ ዝም ብሎ የጥያቄ ጋጋታ ሊመስለን ይችላል። ነገር ግን ጠጋ ብለን ያየናቸው እንደሆን፣ የእግዚአብሔርን ሉዓላዊነት ፍንትው አድርገው ይናገራሉ። እርሱ አደራረጉ ቢገባን፣ ባይገባን፣ ያለው ቢመቸን ባይመቸን፣ በከበረው ዙፋኑ ላይ አለ። ጥያቄዎቹ በራሳቸው መልስ ሆነው ተቀምጠዋል።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ አንተ ትልቅ ነህ። አዕምሮዬ ከሚያስበው በላይ እጅግ ኃያል ነህ። አንዳንዴ ነገሮች ሲደራረቡብኝ እስታለሁና ታላቅነትን በማስተዋል እበረታ ዘንድ በፀጋህ እርዳኝ። አሜን።

17/04/2026

ለኢዮብ መለሰ
============================

📖“እግዚአብሔርም በዐውሎ ነፋስ ውስጥ ሆኖ ለኢዮብ መለሰ...”

— ኢዮብ 38፥1

ኢዮብ የደረሰበትን መከራ "ዱብ ዕዳ" ብለን መግለጥ እንችላለን። ዓይኑን ጨፍኖ በገለጠበት በሚያስብል መልኩ ነገሮች ሁሉ በፍጥነት ነበር የሆኑት። በሰውኛ መነፅር ሲታይ ቅፅበታቸው ያስደነግጣል። በዚህን ጊዜ ነበር ኢዮብ በእሮሮና በሲቃ የተሞላው። ሁኔታዎች ሁሉ ከኢዮብ ቁጥጥር ውጪ በመሆናቸው ዛለ። ልቡ ፍስስ አለ። አዕምሮው ማብቂያ በሌላቸው ጥያቄዎች ተሞላ።

በምዕራፍ ሰላሳ ስምንት ኢዮብ ለጊዜው "ዝም" ብሎ እግዚአብሔር ሲናገር እንመለከታለን። ይህንም ሰፊ ዳሰሳ፣ ምዕራፉ መዝግቦልን እናነባለን። “እግዚአብሔርም በዐውሎ ነፋስ ውስጥ ሆኖ ለኢዮብ መለሰ እንዲህም አለ፦” (ኢዮ 38፥1)

ቁጥር ስምንትን ሳነብ፣ ውስጤ በታላቅ ተስፋ ይሞላል። ኢዮብ፣ በተሰበረና እታች መሬት ላይ በተፈጠፈጠ ጊዜ እግዚአብሔር ከቶ አልተወውም። የኢዮብ የዝቅታ ህይወት የተለያዩ ሰዎችን ከእርሱ ያራቀ ቢሆንም እግዚአብሔር ግን ከእርሱ አልተለየም ነበር። በመከራ ማቆ አዕምሮው በትክክል ማሰብ ተስኖት ቢዘባርቅም እግዚአብሔር "በዐውሎ ነፋስ ውስጥ ሆኖ ለኢዮብ መለሰ።"

ዛሬም እኛ ህይወታችን በመዶሻ ተቀጥቅጦ ደቀን ያለንበት ሁኔታ ላይ ልንሆን እንችላለን። የከፍታን በትረ መንግስት እንዳልጨበጥን፣ አሁን ላይ ለእኛ እስኪያስገርመን ድረስ ታች ተገኝተን ይሆናል። ባስ ሲልም የመከራው ማየል ጤናችንን እያናጋው ሊሆን ይችላል። ኢዮብ በዚህ መስመር አልፏል።

ነገር ግን አንድ እርግጠኛ ሆኜ ልናገር የምችለው ጉዳይ አለ። እርሱም “እግዚአብሔር በዐውሎ ነፋስ ውስጥ ሆኖ” ያናግረናል። ለስላሳ በሆነው ድምፁ "ልጄ፣ አልተውኩህም/አልተውኩሽም" ይለናል። ወገኖቼ፣ መከራው ያልፋል። ለጥቂት ጊዜ ነው። ለቅሶ ማታ ቢሆን እንኳን ጠዋት ግን ደስታ ይሆናል። ማንም ሳያየን በድብቅ ያነባንባቸው ሌሊቶች፣ በማለዳ በሳቅ ይቀየራሉ። አንብተን፣ አዝነን፣ ዝለን፣ ወድቀን፣ ደቀን፣ ተሰብረን ከቶ አንቀርም። ሀሌሉያ!

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ ከእስትንፋሴ ይልቅ ለእኔ የቀረብከኝ አባቴ፣ ያለቀልኝ በመሰለኝ ሰዓት እንኳን ስላልተውከኝ አመሰግንሃለሁ። ካለሁበት ሁኔታ የተነሳ የተለያዩ ነገሮችን እያነሳሁ ስዘባርቅ፣ በቁጣ ሳይሆን በፍቅር ልትገናኘኝ ስለመጣህ ከፍ ከፍ በል። ይህን ታላቅ እውነት በመረዳት ደግሞ በአንተ ላይ ዘውትር መደገፍ እንድችል በፀጋህ እርዳኝ። አሜን።

16/04/2026

ክፍል አስር፣ ትመሰገናለች
============================

📖“መልካም ያደረጉ ብዙ ሴቶች አሉ፥ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ።”

— ምሳሌ 31፥29

በከበረ ትዳር መባረክ በእውነት መታደል ነው። ብዙ ነገሮችን አግኝተን፣ ተሳክቶልን ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ገጣሚ የሆነን ሰው ማግኘት እኩያ የለውም። ቤት በሰላም፣ በፍቅርና በደስታ ደምቆ እንደ ማየት ምን የሚያስደስት ነገር ይኖራል። ልጆች የሚዋደዱና የሚከባበሩ ወላጆችን እያዩ ማደጋቸው በሕይወታቸው ላይ የሚፈጥረው ተፅዕኖ ቀላል የሚባል አይደለም።

ቤት ሰላም ከሆነ፣ አከባቢ ሰላም ይሆናል። አከባቢ በመልካም ጠረን ከተሞላ ሀገር ከክፋት ተፋታ ተዘልላ ትኖራለች። የሁሉም ነገር ምንጭ ያለው ቤት ነው። ጠላት ይህንን ስለሚያውቅ ነው ቤተሰብን ለመናድ ያለ የሌለ ኃይሉን የሚጠቀመው። በመልካም ቤተሰብ ያላደግ ልጅ ወይም ከትዳር ውጪ የተወለደ ልጅ ሲያድግ ወደ ተለያዩ ሱሶች የመግባትም ሆነ ወደ ወንጀል የመሳቡ ሁኔታ በመልካም እንክብካቤ ካደጉት ልጆች አንፃር ሲታይ ከፍተኛ ነው። ከስር መሰረቱ ቤተሰብ ላይ ካልተሰራ፣ ነገን የሚረከብ ትውልድ ተፈልጎ ላይገኝ ይችላል።

በክርስትናው ዓለምም የሚንፀባረቀው እውነታ ይሄ ነው። ልጆች በቤተሰብ ፍቅር ተኮትኩተውና እግዚአብሔርን አውቀው ካላደጉ፣ በጉብዝናቸው ወራት ከቤቱ መራቃቸው አይቀሬ ነው። ወጣትነታቸውን ለክብር ከመጠቀም ይልቅ ጠላት ቅርጥፍ አድርጎ እንዲበላው ይፈቅዱለታል።

ታዲያ ሚስት የመልካም ቤተሰብ ዋልታና ማገር ናት። ቤቷን ቀጥ አድርጋ መያዝም ሆነ ልጆቿን በተገቢው ሁኔታ ማሳደግን ታውቅበታለች። የሙሴ እናት፣ ሙሴ ላይ ያሳደረችውን ተፅዕኖ ልብ ይሏል።

እናማ፣ ልባም ሴትን ያገኘ ሰው እንዴት ዝም ማለት ይቻለዋል። ይልቁን የቤቱን ምሰሶ አፅንታ ላቆመችው ንግስቱ የምስጋናን ቃል ያፈልቅላታል እንጂ። ይህቺ ልባም ሴት ይህ ሁሉ ይገባታል። ልጇቿም ሆኑ ባሏ ከልባቸው ያመሰግኗታል። እንዲህም ይሏታል፦ “ልጆችዋ ይነሣሉ፥ ምስጋናዋንም ይናገራሉ፤ ባልዋ ደግሞ እንዲህ ብሎ ያመሰግናታል፦ መልካም ያደረጉ ብዙ ሴቶች አሉ፥ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ። ውበት ሐሰት ነው፥ ደም ግባትም ከንቱ ነው፤ እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት ግን እርስዋ ትመሰገናለች። ከእጅዋ ፍሬ ስጡአት፥ ሥራዎችዋም በሸንጎ ያመስግኑአት።” (ምሳ 31፥28-31)

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ የሁሉም ነገር ምንጭና ባለቤት አንተ ነህ። ከአንተ የሆነው ነገር ሁሉ እጅግ መልካምና ያማረ ነው። አቤቱ፣ ስትሰጥ መቼ ሰስተህ ታውቅና። እጆችህ የልጆችህን ፍላጎት ለሟሟላት ዘውትር የተዘረጉ ናቸው። ወደ አንተ የሚመጡትን ወደ ውጪ አውጥተህ ከቶ የማትጥለው ቸር አባት ሆይ፣ አሁን ላይ ደግሞ ትዳር የምፈልግበት ወቅት ነውና እነሆ ወደ አንተ መጥቻለሁ። ቤቴን፣ ሕይወቴን፣ ዘመኔን በልባም ሴት ትባርክልኝ ዘንድ እማፀንሃለሁ። ጌታዬ ሆይ፣ እኔም እንደ ሴት የከበረን ትዳር እሻለሁና "ልባም ሴት" አድርገኝ። አሜን።

15/04/2026

ክፍል ዘጠኝ፣ ጠቢብ
============================

📖“አፍዋን በጥበብ ትከፍታለች፤ የርኅራኄም ሕግ በምላስዋ አለ።”

— ምሳሌ 31፥26

"ምላስ አጥንት የላትም፤ ነገር ግን አጥንትን ትሰብራለች" የሚልን አባባል የሆነ ጊዜ ላይ እንደ ሰማሁ አስታውሳለሁ። አንደበት ዋጋዋ የላቀ ነው። ላወቀበትና ለተጠቀመበት ቤትን ትሰራለች፣ ለሌላኛው ደግሞ የቆመን ቤት ታፈርሳለች።

ልባም ሴት፣ አንደበቷ የተገራ ነው። ምን ሰዓት ላይ፣ ምን ማውራት እንዳለባት ጠንቅቃ ታውቃለች። በምላሷ ክፉ የሆነውን መርዝ አትረጭም። አፍዋን እንዲሁ በምናምንቴ አትከፍትም። በጨዋታ መካከል እንኳን አንተን የሚያስከፋ ነገር አትናገርም። ንግግሯ በፀጋ የተቀመመ በመሆኑ ከአንደበቷ የሚወጡት እያንዳንዷ ቃላቶች ፈዋሽ መድኃኒቶች ናቸው። “ያማረ ቃል የማር ወለላ ነው፤ ለነፍስ ጣፋጭ ለአጥንትም ጤና ነው።” (ምሳ 16፥24)

አዎ፣ ልባም ሴት በንግግሯ አትስትም። “አፍዋን በጥበብ ትከፍታለች፤ የርኅራኄም ሕግ በምላስዋ አለ።” (ምሳ 31፥26) በአንደበቷ ቀና ምክር አለና አቅጣጫን ጠቋሚ ናት። ለሕይወትህ ስኬት ታጥቃ ትነሳለች። ቤትህን በመልካም ጠረን ሞልታ ሰላምንህን ታበዛዋለች።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ ንግግሬን በፀጋ ቀምመህ ለባሌ ምቹ ረዳት አድርገኝ። አባት ሆይ፣ አፍዋን በጥበብ የምትከፍተዋን፣ ጣፋጭ አንደበት ያላትን ልባም ሴት ስጠኝ እልሃለሁ። አሜን።

14/04/2026

ክፍል ስምንት፣ ብርቱ
============================

📖“ብርታትና ከበሬታ ልብስዋ ነው፤ በኋላም ዘመን ላይ ትስቃለች።”

— ምሳሌ 31፥25

"የልባም ሴት" መገለጫ ባህሪያትን እያጠንና እንገኛለን። በዛሬው የሕይወት ስንቃችን ይህቺ ዕንቁ ሴት "ብርቱ" እንደሆነች እንመለከታለን።

ሕይወት በብዙ ቀለሞች የተሞላች ናት። የነጭ (ደስታ)፣ የጥቁር (ሀዘን)፣ የቀይ (ዋጋ መክፈል) እና መሰል ቀለሞች በሕይወት ውስጥ ተንፀባርቀው ይገኛሉ። ኑሮ በራሱ በሩጫ የተሞላ ነውና ከእርሱ ጋር በተመሳሳይ ፍጥነት የማንጓዝ ከሆነ ቀትሩ ይጨልምብናል።

ታዲያ በነገር ሁሉ ረዳት ሆና የምትገኝ መልካም ሴት ድቅድቁን ጨለማ የማብራት ታላቅ ኃይል አላት። ይህቺ ሴት ስንፍና ከቶ አያውቃትም። ለስራ ማልዳ ትነሳለች። የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ ቀድማ ታደርጋለች። ብርቱ ናት። “ብርታትና ከበሬታ ልብስዋ ነው፤ በኋላም ዘመን ላይ ትስቃለች።” (ምሳ 31፥25) በስራዋ የተመሰገነች፣ በባልደረቦቿ የተወደደች ናት። "ደከመኝ ሰለቸኝ" ሳትል ቤቷን ለማቅናት ሌት ተቀን ትሰራለች። በየ ቤቱ እየሄደች ወሬ አትለቃቅምም። ለዚህ የሚሆን ጊዜ የላትም።

ሴት ሁሉ ሚስት በማይሆንበት በዚህ ዘመን፣ ሚስትን መምረጥ ትልቅ ጥበብን ይጠይቃል። ታዲያ ወዳጄ፣ ብርቱ ሴትን ያገኘህ እንደሆን አስብበት። ምን አልባት መልኳ የተሸለመ ላይሆን ይችላል። ነገር ግን እመነኝ፣ የተሸለመን ሕይወት ትሰጥሃለች።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ ባሌ የማያፍርብኝ ብርቱ ሴት አድርገኝ። አባት ሆይ፣ ብርታትን እንደ ልብስ የደረበችውን ልባም ሴት ስጠኝ በማለት እፀልያለሁ። አሜን።

13/04/2026

ክፍል ሰባት፣ መከበሪያ
============================

📖“ባልዋ በአገር ሽማግሌዎች መካከል በሸንጎ በተቀመጠ ጊዜ በበር የታወቀ ይሆናል።”

— ምሳሌ 31፥23

ደርቦ የማይሞቀው፣ ደህና ለብሶ የማያምርበት ሰው አለ። ምንም እንኳን በከፍታ ላይ የተቀመጠ ቢሆንም ከሁሉ አንሶ ይታያል። ሞገስ የሌለው ሰው መገለጫው ይህ ነው።

ልባም ሴት ለቧሏ መከበሪያው ናት። እንደ እንቁ ገና ከሩቅ ሲታይ ደምቆ ያበራል። ሞገሱ እንደ አርሞዴም ጠል ከራስ ጠጉሩ እስከ እግር ጥፍሩ ድረስ ሞልቶ ይፈሳል። ግርማው እንደ ናርዶስ ሽቶ አከባቢውን ያውደዋል። እርሱ ከእርሷ ጋር ሲሆን ብቻውን ሆኖ እንኳን ብዙ ነው። በማህበረሰቡ ዘንድ ተሰሚነትን የሚያገኝ፣ ለውሳኔ የሚፈለግ፣ ለአባቢው ዋርካ የሚሆን አይነት ሰው ይሆናል።

“ባልዋ በአገር ሽማግሌዎች መካከል በሸንጎ በተቀመጠ ጊዜ በበር የታወቀ ይሆናል።” (ምሳ 31፥23) ይህቺ ልባም ሴት ለቧሏ የክብሩ መገለጫ ዘውዱ ናት። ወንድሜ፣ መከበሪያህ የሆነችዋን ልባም ሴት የራስህ ማድረግ ትፈልጋለህን? እንግዲያውስ አምላክህ ፊት ተንበርከክ። መሻትህን ንገረው። እርሱም የለመንከውን ሁሉ እንደ መልካም ፈቃዱ አንዳች ሳያጓድል ይሰጥሃል።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ ለባሌ መከበሪያው እንድሆን በፀጋህ እርዳኝ። አባት ሆይ፣ የምትወድደኝንና ሞገሴ የሆነችዋን ልባም ሴት ስጠኝ ስል እፀልያለሁ። አሜን።

10/04/2026

ክፍል ስድስት፣ አሳቢ
============================

📖“ለቤትዋ ሰዎች ከበረዶ ብርድ የተነሣ አትፈራም፥ የቤትዋ ሰዎች ሁሉ እጥፍ ድርብ የለበሱ ናቸውና።”

— ምሳሌ 31፥21

የፍቅር ምሰሶዎች ከሆኑት አንዱ መተሳሰብ ነው። በትዳር ውስጥ ይህ ከሌለ ቤቱን በአሸዋ ላይ የሰራን ሰው ይመስላልና ትንሽ ነፋስ በነፈሰ ጊዜ መሰረቱን ከስሩ ነቃቅሎ ያፈርሰዋል። "ኮሽ" ያለ ድምፅ ሁሉ ጆሮ ውስጥ ይገባል። ፍቅርም ደብዛው እየጠፋ ይሄዳል።

ልባም ሴት፣ ሲበዛ አሳቢ ናት። ለባሏ፣ እርሱ ለራሱ ከሚያስበው በላይ ታስብለታለች። ውዷን በዘመኗ ሁሉ ትጠነቀቅለታለች። በህይወት አጋጣሚ ዝቅ ያለ እንደሆን እንኳን እጁን ይዛ ወደ ከፍታው ታወጣዋለች። ሀዘኑ አጥንቷን ዘልቆ ያልፋል። ደስታው ያስቦርቃታል። ስኬቱ ስኬቷ፣ ውድቀቱ ደግሞ ውድቀቷ ይሆናል።

የሚያስገርመው ደግሞ ይህቺ ልባም ሴት አሳቢነቷ ለቧላ ብቻ አለመሆኑ ነው። በቤቷ ጣሪያ ላሉት ሰዎች ሁሉ ግድ ይላታል። እርሷ ሞቋትና ደልቷት፣ እነርሱ ግን በብርድ ሲቆራፈዱ እያየች እንዲሁ ዝም አትልም። የታረዘን አልባሽ ናትና። “ለቤትዋ ሰዎች ከበረዶ ብርድ የተነሣ አትፈራም፥ የቤትዋ ሰዎች ሁሉ እጥፍ ድርብ የለበሱ ናቸውና።” (ምሳ 31፥21)

ወዳጄ፣ እንደዚች አይነት ልባም ሴት ካገኘህ ጊዜ አታጥፋ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ በፀሎት ምሪት ውስጥ ፈትሸህ የቤትህ ንግስት አድርጋት።

🛐ፀሎት፡ አምላኬ ሆይ፣ ከራስ ወዳድነት ስሜት በመውጣት ለውዱ ባሌ የማስብ ልባም ሴት አድርገኝ። አባት ሆይ፣ የምትጠነቀቅልኝ፣ የምታስብልኝና ዋናዋ የሆንኩኝ ልባም ሴትን ስጠኝ። አሜን።

Want your school to be the top-listed School/college in Addis Ababa?

Click here to claim your Sponsored Listing.

Location

Category

Culinary Team

Attire

Telephone

Address


Ras Desta Damtew Street
Addis Ababa