09/06/2022
በAbiy Ahmed የመደመር ስሌት — የአንድ ኢትዮጵያዊ ነፍስ ስንት ያወጣል?
/በትዕግሥት የሚነበብ!/
አብይ አህመድ በ5ሺህ የክብር ዘብና በ50 ጠባቂ ጠረንገሎዎች ታጅቦ ይንጎማለላል፡፡ ሳዑዲ ተልከው የመኪና አክሮባት በሠለጠኑ ሹፌሮቹ ነው የሚንቀሳቀሰው፡፡ አለ የተባለ በመዓት ሺህ ዶላሮች ተከስክሶባቸው ወደ ሀገር ውስጥ የገቡ ዘመናዊ የጦር መሣሪያዎችንና ተሽከርካሪዎችን ታጥቀው አብይ ሲሮጥ ይሮጣሉ፣ ሲቆም ይቆማሉ፣ ሲተኛ ነቅተው ይጠብቃሉ፡፡
እንግዲህ ሰውየው የሚኖረው በጠላት ሀገር ላይ አይደለም፡፡ ሥራቸው አብይን ከራሱ ህዝብ መጠበቅ ነው፡፡ ለነፍሱ ጥበቃ የሚከሰክሰው የተጋነነ ወጪ መጠን የአብይ አህመድን ፈሪነት አይደለም የሚያመለክተው፡፡ ህዝቡን የፈራበትን መጠን ነው፡፡ የዚህ ሁሉ ሪፐብሊካን ጋርድ ወጪ የሚከፈለው እህ ብሎ አምጦ ወገቡን አጉብጦ ሲሠራ ከሚውለው ከእያንዳንዱ ጭቁን ኢትዮጵያዊ ጉሮሮ ተነጥቆ ነው፡፡
የደሃው ልጅስ? የደሃው ልጅ ደሞ ለጌቶች ነፍስ ጥበቃ ከጎበጠ ወገቡ የሚገፈግፈው አንሶ፣ እነ አብይ አህመድ እፍ ብለው በቆሰቆሱት የጦርነት እሳት እየተላከ፣ ኮቾሮ እየቆረጠመ፣ አፈር ልሶ፣ አፈር ለብሶ፣ አፈር መስሎ፣ በየጥሻው ሲንፏቀቅ፣ በጥይት አረር ሲጨረገድ፣ እና ከገዛ ወገኑ ጋር ደም ሲፋሰስ፣ ነፍስ ሲነጣጠቅ ይውላል!
በየዕለቱ የደሃን ልጅ ነፍስ እንደ ባህርዛፍ ቅጠል እያረገፈ፣ በሚሊየን ዶላሮች በተጌጠ የሲቹዌሽን ሩም ሳሎን ውስጥ ቁጭ ብሎ፣ በሚሊየኖች ብሮች ባስገነባቸው መናፈሻዎች ችግኞችን ሲተክልና፣ በማታ በቦቴ መኪና ችግኞቹን ውሃ ሲያጠጣ እየተከተለ የሚያነሳውን ፎቶግራፈር በሄደበት እያስከተለ የልጅ አምሮቱን ይወጣል፡፡ ድል ቁርሱ፣ ትንታጉ፣ ነበልባሉ፣ ሀገር-ወዳዱ እያለ በደሃው ደም ውስኪ ለሚረጫጩት፣ በደሃው አጥንት ላይ ለሚረማመዱት ድልብ ጄኔራሎች የዳቦ ስም ያወጣል!
አብይ አህመድ የምላስ ወለምታ አያውቅም፡፡ ንቀት፡፡ ከፍ ያለ ንቀት ነው ያለው ለህዝቡ፡፡ ህዝቡ ሜሞሪው አጭር ነው - ብሎ ተናግሮ ይቅርታ አትጠብቅ፡፡ በሚቀጥለው ጊዜ - የሕዝቡ የመዘንጋት ችግር እንዳለ ሆኖ.. ብሎ የፓርላማ ንግግሩን ይጀምራል፡፡ አብይ አህመድ የኢኮኖሚክስ ዶክተር ማለት የአንድ ሀብታምን ታሪክ የጻፈ ነው፣ የእናንተን፣ ለራሱ መኪና ያልገዛ ምሁር፣ ምሁር ነው ወይ? ያልተማረ ባለገንዘብ ይበልጠዋል የኛን ሀገር ፕሮፌሰር ሲል በተማሩት ይሳለቃል፡፡ ያው የፓርቲው ውርዴ መሆኑ ነው፡፡ ምሁር ጠልነት፡፡
ራሱ ስለምን ጽፎ ዶክትሬት እንዳገኘ በበኩሌ አላውቅም፡፡ ባንድ ወቅት የካርል ማርክስን ስም እጠራለሁ ብሎ ህዝብ በተሰበሰበበት አዳራሽ ‹‹ማርክ!›› እያለ እንደቆሎ ጓደኛው ሲቆነጽለው - ‹‹ሃይ ጋይስ›› እላለሁ ብሎ ‹‹ሄይ ጌይስ›› ያለው የጥንቱን ወዳጄን ያስታውሰኛል፡፡ ሳሞራ የኑስ ፕሮፌሰር በሆነባት ሀገር፣ ምን የማይቻል ነገር አለ?
አብይ አህመድ እኮ - ፕሮፌሰር መስፍን በአንድ ወቅት - በዓለም ላይ እንደእሱ ያለ ጭንቅላቱ የመጠቀ ሰው አይቼ አላውቅም - ብለው የመሰከሩለት ባለብሩህ አዕምሮ ሰው እኮ ነው፡፡ ከእሳቸው ጋር አንጋጠህ አትታገል እንግዲህ፡፡ መቀበል ነው ያለህ አማራጭ፡፡ ግን የሚገርመው እሳቸው በአንድ ወቅት በመጽሐፍ ሁሉ አትመው ‹ከደብተራም ያነሰ ድቁናውን የጣለ ደደብ› ብለው ያብጠለጠሉት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት እኮ ነው ንግግሩን እንኳ የሚጽፍለት!
ዓለም አስቂኝ ናት! ነብርን ፍየል ስትመራው ብታገኝ፣ ጂኒየሱን ደደቡ ንግግሩን ሲጽፍለት ብታገኝ አይግረምህ! ዓለም እንዲህ ነች! በበኩሌ ግን በብዙ ፈርጆች ቢመዘን ፕሮፌሰር ሳሞራ የኑስ ከዶክተር አብይ እጅግ የተሻለ የህይወት ልምድም ወታደራዊ እውቀትም ብስለትም ያካበተ ሰው እንደሆነ ይሰማኛል፡፡ ከአብይ አንጻር ነው ያልኩት፡፡ አብይ አህመድ አንዴ ብቻ ነጯን ሲናገር ስሰማው በፍቅር ገድሎኝ ነበር፡፡ ከአማካሪዎቹ ከእነ ዶክተር ብርሃኑ ጋር በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ችግሮች ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ሲያቀርብ - ‹‹እኔም እንደምሁር ተቆጥሬ ከናንተ ጋር በማቅረቤ አመሰግናለሁ›› ብሎ ነበር፡፡ ይህን ያህል ትሁት ከሆነ፣ የማብጠልጠል መብት አይኖርም፡፡ ይቅር ለእግዜር፡፡
በዚህች ጎረቤት ለጎረቤት እንጀራና ወጥ እየተበዳደረ በሚኖርባት ደሃ ሀገር ላይ - አብይ አህመድ የማርጋሬት ታቸርን እንደ ብረት የጠነከረ ነጭ ካፒታሊዝም አራምዳለሁ ብሎ ብዙ ጊዜ ሲናገርና ሲያስነግር ለሰማው ሰውየው በሕልም ዓለም እንደሚኖር ማንም አይጠራጠርም፡፡ ድንገት ይነሳና ሀብታሞችን የሚሊዮን ብር እራት ይጠራቸዋል፡፡
በግብዣው ላይ የሼሁ ስንተኛ ሚስት የሆነች አር-ቲስት ትነሳና በሼሁ ስም የሆኑ ሚሊየኖችን ለአብይ አህመድ ትለቅበታለች፡፡ ፓርላማ ሲጠይቀው - ይሄ ፓርላማ በጀት ቆርጦ ያልሰጠኝን፣ ለምኜ ያመጣሁትን ገንዘብ ሰባራ ሳንቲም ሊጠይቀኝ አይችልም! ብሎ በድፍረት የመለሰ ሰው ነው፡፡ ቄሮ ሆቴሉን አቃጥሎ አመድ ያደረገበት ኃይሌ ገብረስላሴ ይመጣና የሚሊዮን ብር ራት አብልቶ ፓርላማውን አትጠይቀኝ ላለው - እና የመለመን ፀጋ አለኝ ይሳካልኛል ብሎ - የእርዳታ አስተባባሪ ኮሚሽኑን ስምዖን መቻሌን ላስቀናው - ለአብይ አህመድ ባደባባይ አዲስ ከነዳጅ የነጻች መኪና ቁልፍ በሥጦታ ያበረክትለታል!
‹‹ሀብታም ለሀብታም ይጠቃቀሱ፣ ደሃ ለደሃ ይለቃቀሱ›› ይላሉ አበው - የእኛን ዓይነቱን አያዎ ህይወት ሲመለከቱ፡፡ በአብይና ጭፍሮቹ አመለካከት - ደሃው ሕዝብ (የኢኮኖሚክስ ዶክተርም ቢሆን መኪና ከሌለው!) በሀገሩ ላይ ሲኖር፣ ነፍሱ አስፈላጊ የሆነች፣ ቢሞት ቤተሰቡንና ሀገሩን የሚያጎድል፣ ቢኖር ራሱን፣ ዘመድአዝማዱን፣ ቤተሰቡን ሀገሩን የሚጠቅም ክቡር የሰው ልጅ ሆኖ ሳይሆን፣ ተራ አሃዝ፣ ተራ ቁጥር ሆኖ መኖር እንዳለበት ደምድመዋል፡፡
ከላይ እንዳልኩት በዚህች ሀገር ላይ - የአብይ አህመድ አንዲት ነጠላ ነፍስ በቢሊየን ብር ባጀት በሚመደብላቸውና በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ አስቂኝ ትርዒትና አጀብ በሚያደገድጉ፣ ከፍ ያለ ሥልጠናና ወጪ በሚወጣባቸው ሪፐብሊካን ጋርዶች ትጠበቃለች፡፡ የደሃው ልጅ ነፍስስ? በዚህች የህይወት ኢንሹራንስ ህዝቡን ባላዳረሰባት ምስኪን ሀገር የደሃውንስ ነፍስ ማን ይጠብቃት? ደሃውማ ምን ጠባቂ ያስፈልገዋል? ደሃ ጠባቂ ቢያስፈልገው በቡራዩ ላይ ያለጠባቂ አይጨፈጨፍም፡፡
ደሃ ጠባቂ እንደሚያስፈልገው አብይ አህመድ ቢያምን በዝዋይ፣ በሻሸመኔ፣ በወለጋ፣ በመተከል፣ በባሌ፣ በሐረርጌ፣ በሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች - ህዝብ - ያለ ጠባቂ፣ ያለህግ፣ ያለ ተከላካይ - በመቶ ሺኅዎች በግፍ አይገደልም፡፡ በግፍ በአደባባይ አይቃጠልም፡፡ በግፍ አይፈናቀልም፡፡ በግፍ የእርጉዝ ሆድ አይዘከዘክም፡፡ ሰው የራሱን አንዲት ነፍስ በቢሊዮን ብሮች ባጀት መድቦ በብርጌድ ሲያስጠብቅ፣ እንዴት የመቶ ሺህዎችና የሚሊዮን ዜጎችን ነፍስ እንደ በረሮ ነፍስ ቆጥሮ ሀገር ምድሩን የአራጅና የወንበዴ መፈንጫ ያደርገዋል?
ይሄ ይቅር! እነ አብይ አህመድ ይቅርና ከእነ አብይ አህመድ ጋር የተሞዳሞዱ ተቃዋሚዎች ሁሉ የነፍሳቸው ጠባቂ ጋርድና ታጣቂ ተመድቦላቸው ከዚህ ከደሃው ህዝብ ላይ ከሚሰበሰብ ታክስ ደመወዝ እየተቆረጠለት በየሄዱበት እንደጥላ እየተከተለ ለክብራቸው ሲያደገድግና ነፍሳቸውን ሲጠብቅ፣ ደሃው ኢትዮጵያዊ ግን ሠላሙም አርሮበት - በመቶ ሺኅዎች የሚቆጠር የደሃ ልጅ ከየጎጆው እየተጋዘ፣ ከሌላው ከፈረደበት ወገኑ ጋር፣ ባላገደደውና ባልፈተፈተው ጉዳይ፣ ባልጫረውና ባልቆሰቆሰው፣ በማያውቀው የጦርነት እሳት ውስጥ እንዲማገድ እየተደረገ… በዚህች በፈረደባት ‹‹እናት ሀገር›› ስም ከገዛ ወገኑ ጋር ሥጋ ለሥጋ፣ አጥንት ለአጥንት ሲሞሸላለቅ ይከርማል!
በዚህ መሐል የሞተ ተጎዳ፣ የተረፈ አንድዬ አተረፈው! ይኸው ነው! ዞር ብሎ የሚያየው የለም! ቢማረክም ባለቤት የለውም! ቢሞትም ሞቱ አይታመንለትም! የክብር ሜዳይ የለውም! ሀገርና ሕዝብ የተዋደቁላቸውን ጀግኖቻቸውን በስም አያውቁም! ስም የሌላቸው፣ ክብር የሌላቸው፣ ጠባቂ የሌላቸው፣ ግፋ ቢል በቁጥር 20 ሺህ ሰራዊት አለቀብን እየተባለ በጅምላ ቁጥራቸው የሚታመንላቸው፣ የደሃ ልጆች በሠላም ሀገር፣ የሠላም ኖቤል በተሸለመና በብርጌድ ነፍሱን በሚያስጠብቅ መሪ ዓይን ስር እንደ ቆሎ ይረግፋሉ!
ይህ ነው የዘመኑ የምስኪኑ የደሃው ኢትዮጵያዊ ልጅ የተፈረደበት አሳዛኝ የህይወትና የሞት እጣ ፈንታ! ይህንኑ ሸሽተው ለመሰደድ ስንቱ ባህር የሚበላቸው፣ ስንት አውሬ የሚጫወትባቸው፣ ወጥተው የቀሩ ኢትዮጵያውያን ሁሉ፣ በአስከፊ የሽሽት ሞታቸው የሥርዓቱን አስከፊነት የሚያጋልጡ ናቸውና የክብር ሽኝት አያገኙም፡፡ ስማቸው በሚዲያ አይነዛም፡፡ የሀዘን ባንዲራ አይወርድላቸውም፡፡ ዝም፡፡
ህዝባችን በዝምታ እያለቀ ነው፡፡ ወጣቶቻችን በዝምታ እያለቁ ነው፡፡ መሪው ደግሞ በቢሊየን ብሮች መሐል መስቀል አደባባይ ላይ አስፋልት እየቆፈረ የማሳመር ሥራ ይሰራና፣ በጓደኛው ያሬድ ሹመቴ ኤግዚቢሽን ማዕከል ሲኒማ ፊት ለፊት ቁጭ ብሎ ሲዝናና መከረኛውን ካሜራማን ጠርቶ ፎቶ ተነስቶ ኑሮው ላረረበት፣ ሕይወቱ ላረረበት ሕዝብ ይለቃል፡፡
‹ዘ ፓወር ኦፍ ፖዘቲቭ ቲንኪንግ!› ‹የብልጽግና ወንጌል!› ይህ መሆኑ ነው! ስለማሸነፍ ነው ማውራት ያለብህ! ስለብልጽግና ነው! ስለሥልጣን ብልግና አይወራም! ኢትዮጵያ አሸንፋለች! በቅርቡ ከዓለም ሁለት ኃያላን ሀገራት አንዷ ትሆናለች! (ይህን የሚለው ባለ ክቡሩ ባለራዕዩ መሪያችን ዶክተሩ አብይ አህመድ አሊ ነው! እግዚአብሔር በኃያላን ጦር ያስወጋህ! ማለት ያሰኛልኮ አንዳንዴ - ይህን ሕዝብ እንዴት እንደሚጫወትበት ሲታይ!)
ዛሬ ሀገራችን ወደ ትልቅ የሀዘን ቤት ድንኳንነት ተቀይራለች፡፡ ሀገር በጦር እሳት እየተንገበገበች ባለችበት በዚህ መራር ወቅት - እውነተኛው ሀገር-ወዳዱ - እና ያለችውን አንድዬ ነፍስ በሀገር ስም የሚነጠቀው ወጣት ኢትዮጵያዊ - ከኢትዮጵያዊም መሐል የፈረደበት የደሃው ልጅ - አጥንቱ በየሜዳው በሺህዎች እየተከሰከሰ ነው፡፡ ልጅ ያለው ልጆቹ ዘለዓለም ዓለማቸውን ያለአባት፣ ወላጆቹ ያለ ደጋፊ፣ እርሱ ያለ ስም፣ ቤተሰቡ ያለ ጧሪና ቀባሪ ያቺኑ የኮሰሰች ኑሮ ያለአጋር ሲገፏት ይኖራሉ!
ቅዱሷና ከዜጎች ሁሉ ነፍስ እጅግ የከበረችው የእነ አብይ አህመድ ነፍስ ደግሞ - አስር ቢሊዮን በጀት በየዓመቱ እየተመደበላት - በአምስት ሺህ የክብር ዘቦችና በሃምሳ ጠባቂ ጠረንገሎዎች - ባህረሰላጤውን ተሻግረው በሳዑዲ አረቢያ የመኪና አክሮባት በሠለጠኑ ሹፌሮች - እና በመዓት ደህንነቶች እየተጠበቀች ከቀን ወደቀን ደህንነቷ ተጠብቆ ትለመለልማለች፡፡
አብዮት ልጆቿን ትበላለች - የሚባለው የፈረንሳይ አብዮቶች ቃል ዳግመኛ በሀገራችን ምድር በቃል የደረሰው አሁን በአብዮት አህመድ የአገዛዝ ወቅት ላይ ነው፡፡ አብዮት - የራሱን ነፍስ በሺኅ ሪፐብሊካን ጋርዶች እያስጠበቀ - የሀገሪቱን ልጆች ነፍስ ቅርጥፍ አድርጎ እየበላውና እያስበላው ነው፡፡ እሱ በስም ላይ ስም፣ በዝና ላይ ዝና፣ በፉከራ ላይ ፉከራ እየደረበ የድል-ቁርሱዎችን ስም ለጋሻ-ጃግሬዎቹ እያደለ ሲንጎማለል ይኖራል! ደሃው ስም የለውም! ሙት ሲባል መሞት! ሂድ ሲባል መታዘዝ! ውጣ ሲባል ምስስ ብሎ ወደተዘጋጀለት መትረፊያ ካምፕ መግባት ብቻ!
የኢትዮጵያ ህዝብ ይህን የጌቶችና የባሮች ግንኙነት እንዴት አሜን ብሎ እንደሚቀበል ብዙዎችን የዓለም ሕዝቦችን ግራ ያጋባውን ያህል እኔንም ግራ ያጋባኛል፡፡ ፈጣሪ እኩል አድርጎ አይደል ወይ የፈጠረን በአንድ ሰማይ ሥር? የእነ ታዬ ደንደአና የእነ ሽመልስ አብዲሳ የእነ አባዱላና የእነ ደመቀ መኮንን ልጆች ከፍተኛ የሀገሪቱ ሀብት እየተንጠፈጠፈላቸው፣ በቦዲ ጋርዶች እየተጠበቁ፣ በሰላም ውለው ያድራሉ፡፡
የድሃው ኢትዮጵያዊ ልጆች ግን የአውሮፕላን ቦምብ የሚዘንብባቸው፣ ወይ ጥይት አዝናቢም፣ በጥይት ተጠዝጣዥም ሆነው - ቤተሰቦቻቸው እየተለዩ ሆነ ተብሎ በቁርሾና በሥልጣን መቧጨቅ በተመሳሳይ ሀሳብ ተጋሪ ሰዎች መሐል በተቀሰቀሰ ጦርነት የሚማገዱበት፣ እንጥፍጣፊ ተስፋቸው የሞት ጨለማ የሚደረገምባት - ይህን ዓይን ያወጣ፣ ሰው-በላና ዘረኛ ሥርዓት እንዴት - በዚህ በሰለጠነ ዘመን፣ እና ብዙ የዓለም መረጃ በፍጥነት በሚዘዋወርባት ዘመናይት ዓለም ላይ እየኖርን - የሚያመዛዝን የሰው ልጅ ህሊና እሺ ብሎ ይቀበለዋል?
ለመሆኑ እውነቱን እንነጋገር ከተባለ.. አብርሃ ሄዶ በመገርሳ ስለተተካ፣ ጎይቶም ተባሮ በዲማ ስለተለወጠ፣ ኩማ በሹመት ተዛውሩ በሱ እግር ደመላሽ ስለተተካበት፣ በንቲ ሄዶ ባቲ ስለመጣ፣… በቃ ለውጥ መጣልን ማለት ነው? የትኛው ለውጥ ነው ይህ ሁሉ የዜጎች ደም የሚገበርለት? የየትኛው ደሃ ኑሮ ነው የተሻሻለው? ከሶስት ዓመት በፊት ትግራይ ውስጥ ኮሽ የሚል የፀጥታ ችግር ነበር? አሁንስ? ከጥቂት ዓመታት በፊት ወለጋ ላይ ሰዎች በሰላም አይኖሩም ነበር? አሁንስ?
ድጋሚ ወደድሮው! እርስ በርስ ሚሳይል መተኳኮስ፣ ዲሽቃ መለካካት፣ በአውሮፕላን ሕዝብን በቦምብ መደብደብና አውሮፕላን መጣል! ድጋሚ ወዳለፍነው የእርስ በእርስ ጦርነት ለመግባት ነው የደሃው ልጅ ነፍስ ጭዳ የሚሆነው? ማን ነው በለውጡ ያተረፈው? ያለጥርጥር ብቸኛዎቹ የለውጡ አትራፊዎች በሪፐብሊካን ጋርድ የሚጠበቁት ብቻ ናቸው! ሌላ ማንም ለውጡ ጠቀመኝ ያለ አይገኝም! በመጫረስ ብቻ ነው ወይ ለውጥ የሚመጣው? ወይስ በደሃው ልጅ ኪሳራ የህዝብ ቁጥር ለመቀነስ ነው ዓላማችን?
ጥቂቶች ከሁሉም በልጠው፣ የጥቂቶች ነፍስ ከሁሉም ነፍስ ተለይታ እየለመለመች፣ የጥቂቶች ነፍስ በብዙ ሺህ ነፍሶች እየተጠበቀች - የአብዛኛው የሀገሪቱ ህዝብ ነፍስ የደምና የሞት እሳት እንዲነድበት የተፈረደበትን ኑሮ እንድንገፋ የጣፈን የትኛው ፈጣሪ ይሆን? ለግፍ ልክ የለውም ወይ? በየቀኑ በገዢዎቹ መቀላመድና ድንፋታ ወደ እሳት የሚማገደው የደሃው ልጅ መሪውን ‹‹በቃህ! የሚለው መቼ ነው?
‹‹በቃህ! እስቲ አንተ ደሞ እንደ እኔ ከሞቀ ቤትህ ውጣና እንደ ጀግና ተዋግተህ አሳየኝ! እስቲ አንተም እንደኛ ሙትና አሳየን! እስቲ አንተም ቁሰልና፣ አፈር ምሰልና አሳየኝ! ከዚያ እኔም፣ እኛም፣ ሁላችንም ፈለግህን እንከተልሃለን!›› ብሎ የሚያፋጥጥበት ወቅት መቼ ነው? ‹‹መሪ ነኝ›› ሲል ‹‹ናና መንገዱን አሳየን እስቲ!›› አይባልም ወይ ሰው? እሱ በሺህ ጠባቂዎች አንዲት ነፍሱን እያስጠበቀ፣ የደሃውን የመቶ ሺህ ኢትዮጵያውያንን ነፍስ እንደ ቀላል በወራት ዕድሜ ለሞት ሲማግድ? በቃን አይባልም ወይ?!!
ያንተስ ነፍስ፣ ያንቺስ ነፍስ፣ የእኛስ ነፍስ.. ነፍስ አይደለችም ወይ? አይበቃንም ወይ በሞታችን ለሌሎች ጥቂቶች የልጅነት ምኞት መሣካት ተቀጣጣይ ማገዶ መሆን? አይበቃንም ወይ ለንጉሦቻችንና ለመኳንንቶቻችን የቀን ቅዠት ሲባል አንዲቱን ጓዳችንን የምታጎድለውን ያለችንን ብቸኛ ተስፋ - አንድዬ ህይወታችንን - ለእርስ በእርስ መበላላት ዓላማ ተሰላፊ ሆነን ለውጥ ለሌለው ከንቱ የገዢዎች ምኞትና መቆራቆስ በከንቱ መማገድ?
‹‹ወርቃማው ህግ!›› የሚባለው እኮ ይኸው ነው! በሰው እግር ሆኖ ማየት! እንደ ሰው ሆኖ መቆርቆር! የሰው ህመም፣ የሰው ሞት፣ የሰው ልጅ ስቃይ፣ የሰው ልጅ ከወገኑ ጋር ሲወጋጋ መድማት! ያ ሲሰማህ ነው ወርቃማው ህግ የሚገባህ፡፡ በራስህ እንዲደረግ የማትፈልገውን ነገር፣ ለምን በሰው ላይ ታደርጋለህ? ለምን በሰው ላይ ታስደርጋለህ? ለራስህ የምታደርገውን ጥንቃቄና የነፍስ ጥበቃ፣ ስለምን ከሚሊየኖች ህዝቦች ላይ ትነሳለህ? ወርቃማውን ህግ ለምን አትፈልገውም?
ቆይ ቆይ ለምን ቦታ ተለዋውጠን አንሞክረውም? ለምን እኛ ብዙሃኑ የደሃው ልጆች - በሥልጣን ላበጡትና በጥጋብ ለሚገጫጩት ባለጊዜዎች ብለን ነፍሳችንን ከምንገብር - ለምን እኛ የነጻ ትኬት ተሰጥቶን - ተገጫጪዎቹ ራሳቸውን ችለው - እንደ ግላዲያተሮች - በፍስፍሱ መድረክ ላይ ይውጡልንና - ጥቂቶቹ አጅሬዎች እርስበርሳቸው ሲጠዛጠዙ - እኛ ብዙሃኖቹ ተመልካቾች በተዘጋጀልን የሚስማር ተራ ሲቹዌሽን ሩምም ቢሆን፣ አረፍ ብለን - ጠላም ብትሆን እየተቃመስን - ለምን አንመለከትም?
የጌም ኦፍ ትሮንሱ - አሪፍ ጌም እንዲሆንልን - ለምን ጨዋታውን ገልብጠን አንጫወተውም? ለምን ቦታ ተለዋውጠን የደሃው ልጅ በሪፐብሊካን ጋርድ እየተጠበቀ ሲቹዌሽን ሩም ውስጥ 24 ሰዓት እየዋለ እያደረ፣ እናንተ ገዢዎቻችን ደግሞ ጦርሜዳ ኮቾሮና አፈር እየቃማችሁ፣ እየቆሰላችሁና እየተቆሳሰላችሁ፣ እየሞታችሁ… ለምን ጌሙን አገላብጠን አንሞክረውም ጌቶችዬ?
የአንዱ ነፍስ አፈር እየጠጣች፣ አፈር እንድትገባ የተፈረደባት፣ የአብይ አህመድና ጭፍሮቹ ነፍስ ግን በአምስት ሺህ ቦዲጋርድ እየተጠበቀች፣ ጥይት በማይበሳው ልብስና መድፍ በማይዘልቀው መኪና እየተከለለች፣ በዚያ ላይ ክፉ እንዳይነካት የኢትዮጵያ እናቶች በእንባ ታጅበው እየፀለዩላት የምትቀጥል ከሆነ - እንግዲህ ባንድ ሀገር ሰማይ ስር - ሁለት ዓይነት ነፍሶች እያሉ - በእኔ ጉሮሮ ጥይት ይሰንቀር፣ በጌቶች ጉሮሮ ምቾት ይንቆርቆር - እየተባባልን - እንዴት እኩል ዜጋ ነኝ ልንል እንችላለን? የሆነ ልክ ያልሆነ ነገርማ አለ!
እውነት እንዲህ የራሳቸውን ነፍስ በቢሊየን ብሮች በጀት የሚያስጠብቁ ገዢዎቻችን፣ የራሳቸውን ነፍስ እንዲህ ከፍ አድርገው አዋድደው ሲገምቷት… ግን ግን… ግን ለመሆኑ… የእኛን የአንድ የተራ የደሃውን ኢትዮጵያዊ ነፍስ… ስንት ያወጣል ብለው ቢገምቱ ነው ግን? እውነት በዛሬዋ በአብይ አህመዷ ኢትዮጵያ የአንድ ዜጋ ነፍስ ስንት ያወጣል?
የቀኃሥ ዘመን አዋጅ ማንም ባለቤት አልባ አስከሬን በመንገድ ላይ ወድቆ ቢገኝ የመንግሥት ሆስፒታል ለማዘጋጃ ቤት 30 ብር ከፍሎ ለህክምና ምርምር አገልግሎት እንዲያውለውና ሲያበቃ በክብር እንዲቀብረው ይፈቅድ ነበር፡፡ በዚያም የአንድ ሰው ነፍስ 30 ብር መሆኑን አወቅኩ፡፡ የያኔ 30 ብር የአሁን 3ሺህ ብር አይሆን ይሆን? ግድየለም ይሁን! ያ የነፍስ ዋጋ አይደለም! የሙት አካል ዋጋ ነው! አንዳንዴ ዋጋ የሌለው ነዋሪ ከመሆን እኮ፣ የምር፣ ቁርጡ የታወቀ ዋጋ ያለው ሟች መሆንም ይሻላል እኮ አንድ ፊቱን!
እንደው ሌላው ሁሉ ይቅርብንና - እነ አብይ አህመድ ግን የራሳቸውን ዋጋ እንዲያ ቆልለው - በቢሊየኖች በጀት በሚመደብለት ሪፐብሊካን ጋርድ ሲያስጠብቁ - የእኛን የአንድ ኢትዮጵያዊን ነፍስ ግን በስንት ይሆን የተመኑት? ምን ቢያስቡ፣ እና እንዴት ለአገዛዝ ምቹ ባሮች ሆነን ቢያገኙን ነው እንዲህ ነፍሳችንን አርክሰው በነጻ የገመቱን?
ኧረ ዋጋ ቀርቶ… ስንት እንዳለብን ቢነገረንምኮ ከፍለን እንገላገለውና ነጻ እንወጣ ነበር! ሰው እንዴት የሩሲያን የ19ኛ ክፍለዘመን ድርሰት፣ በዚህ በ21ኛው ክፍለዘመን ላይ ይኖረዋል? እንደ ኒኮላይ ጎጎል ‹‹ሙት ነፍሳት›› ድርሰት እኮ፣ ‹‹ሙት ነፍሳት›› አድርጎ ሊያስቀረን ምን ቀረው የኛው ጉዱ-ካሣ (አብዮት ካሳሁን በላይነህ)!?
በቃን! በቃን! በቃን! በቃችሁ! ኑ እናንተ ደሞ አነግቡልን መሣሪያውን! እስቲ ወግ ይድረሳችሁና እንደቀደሙት መሪዎቻችን ወደ ጦርሜዳው ወረድ ብላችሁ ምንሽር አነጣጥራችሁ ስትታኮሱ እንያችሁ! የሲቹዌሽን ሩሞቹ ጀግኖቻችን! እነ ድል-ቁርሱዎች! እነ ትንታጎች! እነ ሀገር-ወዳዶች! ጀግኖች ነን ያላችሁ - እስቲ እንያችሁ!? እስኪ ከጎራው ዘለቅ በሉና ባሩዱን መትረየሱን ስታንበለብሉት እንያችሁ?
ድል-ቁርሱ ነን ያላችሁ - እስቲ እንያችሁ!
እናቶች የሚጸልዩላችሁ - እስቲ እንያችሁ!
ለዚህች ሀገር ነፍሴን እሰጣለሁ ያላችሁ - እስቲ እንያችሁ!
ከጎራው ዘልቃችሁ - እስኪ እንያችሁ?
እናንተ ሩቅ ሆናችሁ - ቅጽል ስም እያወጣችሁ
በል,በለው ማለት - መች ነው የሚሰለቻችሁ!?
እናንተ በፍጹም አትሞቱም! በሲቹዌሽን ሩም ናችሁ! የደሃው ልጅ ግን ለእናንተ ይሞትላችኋል! በጦር ሜዳው ላይ ነው! ይሰማል ወይ? ያዋጣል? የማን ነፍስ ከማን ያንሳል? የነፍሳችን ዋጋ እንደ ውሎ አበል ተመን ይውጣላትማ!? አለዚያ ንቅንቅ የለም! ሳይስማሙ የምን ንቅንቅ ነው?!! አቦ ጉራጌ! አቦ ጉራጌ! አቦ ጉራጌ!
ያገሩ ጎጆ መርዶ ሆኖ፣ በእናንተ ቤት ድግስ ነው! ሙሉ ነው! እንዲህ ነው ወይ ሀገር? እንዲህ ነው ወይ መደመር? መደመሩ አንዳችን አፈር፣ አንዳችን ችግኝ፣ አንዳችን ጌቶች፣ አንዳችን አደግዳጊዎች፣ አንዳችን መከራና ገፈት ተቀባዮች፣ አንዳችን በአክሮባቲስት ሹፌሮች ተዝናኞች.. የምንሆንበት ነበር ማለት ነው? እንዲህ ነው እንዴ የመደመር ስሌቱ?
አንድ ቀን የዚህ ወደሞት የምትማግዱት የሚሊየኖች ድሆች እናቶች እንባ ጎርፍ ሆኖ ይወስዳችኋል! አንድ ቀን በደሙ የምትነግዱበት የዚህ ምስኪን ህዝብ ሀዘን ደራሽ ሆኖ ቤታችሁ ይገባል! ጠራርጎም ይወስዳችኋል! አንድ ቀን በአክሮባቲስት ሹፌሮች እየተነዳችሁ በህዝቡ ፊት ትቀበራላችሁ! አንድ ቀን በቁማችሁ እኩያው ልትሆኑት ባልፈቀዳችሁትና በናቃችሁት ህዝብ ፊት፣ በሞታችሁ እኩያ ሆናችሁ ታሸልባላችሁ!
እስከዚያም የድሃው ደም በእጃችሁ ላይ ነውና የህሊና ሠላም አይኖራችሁም! በሄዳችሁበት ትደነግጣላችሁ! ጥላችሁን የማታምኑ ተቅበዝባዦች ትሆናላችሁ! አምላክ ይፋረዳችኋል! የምስኪኑ ነፍስ ይፋረዳችኋል! ከታሪክና ከፈጣሪ ፍርድ የሚያመልጥ ማንም የለምና፣ የኢትዮጵያ አምላክ ብድራችንን ይክፈለን እንደየሥራችን፣ እንደየግፋችን መጠን! መንግሥቱ ነዋይ እንደዚያ ነበር ያለው!
ዛሬ ሀገሬ ብሎ ወጥቶ በየተራራው ክልትው ብሎ የቀረውን፣ ለገዢዎች እርካብና መንበር ሲባል እርስ በእርሱ የተላለቀውን፣ የተማረከውን፣ የተሰቃየውን፣ የአሞራ ራት የሆነውን፣ አስታዋሽ ያጣውን - የሚያምነው የቸገረውን ምስኪኑን እውነተኛ ሀገር-ወዳድ ኢትዮጵያዊ ወገናችንን - የኢትዮጵያ አምላክ በሚያውቀው እርሱ ብድራቱን ይመልስለት!