15/08/2026
ወ/ሮ #ደስታ #ገብሩ በኢትዮ ሶማሊያ ድንበር ቶጎ ውጫሌ ጦር ግንበር በ1956 ዓ.ም
ወ/ሮ ደስታ ገብሩ ከታዋቂው አባታቸው ከከንቲባ ገብሩ ደስታና ከእናታቸው ከወ/ሮ ካሣዬ የለምቱ በ1913 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ አባታቸው ከንቲባ ገብሩ አጼ ምኒልክ ዘውድ ከመጫናቸው ከዛሬ 145 አመት በፊት በሚሲዮናውያን አማካኝነት ከበጌምድር ወደ ውጭ ተልከው ከፍተኛ ት/ት ከተከታተሉት ጥቂት ኢትዮጵያውያን መካከል አንዱ ናቸው፡፡ ከአጼ ምኒልክ ዘመነ መንግስት ጀምሮ እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የመጀመሪያዎቹ የስልጣን ዘመንም በከፍተኛ ኃላፊነት አገራቸውን አገልግለዋል፡፡
ወ/ሮ ደስታ ገብሩ በአዲስ አበባ የስዊድን ሚሽን ት/ቤትና በእቴጌ መነን አዳሪ ት/ቤት ከመጀመሪያዋ የኢትዮጵያ ፓርላማ ሴት አባል እህታቸው ወ/ሮ ስንዱ ገብሩ ጋር ትምህርታቸውን ሲከታተሉ በመቆየት ፋሺስት ኢጣሊያ በ1928 ዓ.ም ኢትዮጵያን ሲወር ትምህርታቸውን አቋርጠዋል፡፡ የፋሺስት ኢጣሊያን ወረራ ተከትሎ፣ አባታቸው ከንቲባ ገብሩ ቤተሰቡን ይዘው ወደ ነቀምትና ጎሬ በመሄድ በራስ እምሩ የሚመራውን የጥቁር አንበሳ አርበኞች ቡድን ተቀላቅለዋል፡፡
ይህንን ተከትሎም ፋሺስት መሸሻና ደበበ የተባሉትን የከንቲባ ገብሩን ወንድ ልጆች እአአ በየካቲት 1937 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከገደለ በኋላ፣ ከንቲባ ገብሩን ከቀሪ ቤተሰቦቻቸው ጋር በመያዝ ወደ ኢጣሊያ አገር አዚናራ እስር ቤት እስከ ነጻነት ድረስ አስሮ አቆይቷቸዋል፡፡ ወ/ሮ ስንዱ ገብሩ ከኢጣሊያ ከእስር ተለቀው እንደመጡ በአዲስ አበባ የእቴጌ መነን ት/ቤት በመምህርነት አገልግለዋል፡፡
ወ/ሮ ደስታ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበርንም ከተመሰረተበት ከ1928 ዓ.ም ጀምሮ ከ30 አመት በላይ በበጎ ፈቃደኝነት አገልግለዋል፡፡ ወ/ሮ ደስታ የኢትዮጵያ ሴቶች በጎ አድራጎት ድርጅትን በም/ፕሬዚዳንትነት መርተዋል፡፡ የወታደር ሚስቶች የበጎ አድራጎት ማህበርንም በ1956 ዓ.ም በማቋቋም ማህበሩን በፕሬዚዳንትነት አገልግለዋል፡፡
ወ/ሮ ደስታ በቶጎ ውጫሌ ግንባር የሶማሊያ ጦርን ለመመከት ኮ/ል አብዲሳ አጋን ጨምሮ በ1956 ዓ.ም ለዘመተው የኢትዮጵያ ጦር በጦር ግምባሩ በመገኘት በበጎ አድራጎት ስራ ተሳትፈዋል፡፡ ወ/ሮ ደስታ ገብሩ የታዋቂው ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ የሌ/ጄኔራል ከበደ ገብሬ ሚስትና በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳም የሚገኙት ፕያኖ ተጫዋቿ መነኩሴ የእማሆይ ጽጌ ማርያም እህት ነበሩ፡፡
ምንጭ፣ ቆፍጣናው ወታደር ሌ/ጄኔራል ከበደ ገብሬ፣ ከ1910-1967 ዓ.ም፣ በታምራት ከበደ/ሺበሺ ለማ፣ 2007 ዓ.ም
በአስተያየት መስጫው ላይ የተቀመጠው የከንቲባ ገብሩና የቤተሰቦቻቸው ምስል ሲሆን፣ ፎቶግራፉ በ1920ዎቹ እንደተነሳ ይታመናል፡፡