29/04/2026
የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ለሰመራ-ሎግያ ከተማ የዲጂታል አድራሻ ስርዓትን ሊተገብር ነው።
ሰመራ ፣ሚያዝያ 21 ፤2018 ( አፋ.ብ.መ.ድ )
ሚያዚያ 21 ቀን 2018 ዓ.ም የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት በአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ከሰመራ-ሎግያ ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ለመዘርጋት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመ፡፡
የመግባቢያ ስምምነቱን የኢንስቲትዩቱ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ በላቸው ፀሐይ እና የሰመራ- ሎግያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አብዱ ሙሳ ፈርመውታል፡፡
በስምምነቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢንስቲትዩቱ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ በላቸው ፀሐይ በዲጂታል-ኢትዮጵያ 2030፤ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት ትግበራ በማሳደግ ከዲጂታል አገልግሎቶች ጋር በማቀናጀት ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሂደት ውስጥ የአስቻይነት ሚና እንዳለው እና በቀዳሚነት የአድራሻ ሥርዓት የሚያስፈልጋቸው ሴክተሮች ጋር ተግባራዊ እንዲደረግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
ም/ዋና ዳይሬክተሩ አክለው የዲጂታል አድራሻ ስርአቱ (eDAS) አስተዳደራዊ፣ ዲጂታል ኢኮኖሚያዊ፣ ለSmart-City ግምባታ እና ማህበራዊ አገልግሎቶችን ቀልጣፋ እና ተደራሽ ለማድረግ፣ ዘላቂ የኢኮኖሚ እድገትን፣ የከተሞችን ምቾት እና የዜጎችን ሁለንተናዊ ደህንነት ለማረጋገጥ ዓይነተኛ ሚና ይኖረዋል ብለዋል።
የሰመራ-ሎግያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አብዱ ሙሳ በኢንስቲትዩቱ ለከተማው አስተዳደሩ ለተሰጠው እድል ምስጋናቸውን ያቀረቡ ሲሆን ዲጂታል አድራሻ ከተማችንን በማዘመን ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ተመራጭ የሚያደርግ በመሆኑ አጠቃላይ ስራው እስኪጠናቀቅ ድረስ አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ለስራው ስኬታማነትም የከተማ መስተዳድሩ አስፈላጉውን ሀሉ ትብብርና እገዛ በማድረግ ሀላፊነቱንበአግባቡ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ከንቲባው ጨምረው ገልጸዋል።
የዲጂታል አድራሻ ስርአቱ (eDAS) በ73 የኢትዮጵያ ከተሞች ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልፀው የሰመራ-ሎጊያ ከተማ አስተዳደር የዲጅታል አድራሻ ስርዓት ፕሮጅክት በአጭር ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ስራው ተጠናቆ አገልግሎት ላይ የሚውል እንደሆነ በኢንስቲትዩቱ የዲጂታል የአድራሻ ስርዓት ኘሮጀክት ማናጀር አቶ አግማሴ ገበየሁ ገልፀዋል።
አፋር ብዙሀን መገናኛ ድርጅት