25/08/2026
የሀረሪ ክልል ወጣቶች በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ መሆኑ ተገለጸ
ወጣቶች በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች በመሳተፍ ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ እንደሚገኙ በብልፅግና ፓርቲ የሀረሪ ክልል ቅርንጫፍ የወጣቶች ክንፍ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሙስጠፋ ኢሊያስ ገለጹ፡፡
የጽሕፈት ቤት ኃላፊው በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የተከናወኑ ሥራዎችን አስመልክተው እንደገለጹት፤ ባለፉት አመታት ሰው ተኮር የሆኑ የበጎ ፈቃድ ተግባራትን በማከናወን ማህበራዊ ኃላፊነቱን ሲወጣ ቆይቷል ብለዋል።
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መረዳዳትን ባህል ከማድረግ ባለፈ ማህበራዊ ትስስርን በማጠናከር የወጣቶችን ሕብረ ብሔራዊ አንድነት የሚያጎለብት ተግባር መሆኑንም ገልጸዋል።
ከለውጡ ወዲህ ትኩረት የተሰጠው ይህ የበጎ ፈቃድ አገልግሎትም የህብረተሰቡ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች በማቃለል ረገድ የማይተካ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል።
ወጣቶች በአረንጓዴ አሻራ፣ በፅዳት፣ በደም ልገሳ፣ በማዕድ ማጋራት፣ በቤት እድሳት፣በተለያዩ ሆስፒታሎች ላይ የሚገኙ ወገኖችን በመንከባከብና ድጋፍ በማድረግ፣ የአርሶ አደሮች እርሻ የማረስና ሌሎችም ዘርፎች ላይ በርካታ ስራዎችን እየሰሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በመርሃግብሩም ከ50 ሺህ በላይ ወጣቶች እየተሳተፍ መሆኑን ወጣት ሙስጠፋ ኢሊያስ ገልጸዋል።
በጎ ፈቃድ አገልግሎት የእርስ በእርስ መተሳሰብን እንዲሁም ሁለንተናዊ ትብብርና መተጋገዝን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል።
ከዚህ በተጨማሪም የዜጎችን አብሮነትና ወንድማማችነት የበለጠ እንዲጎለብት በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋልም
የተጀመረው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራ የተለዩ የትኩረት መስኮች መነሻ ያደረገና ተጨባጭ ለውጥ ሊያመጣ በሚችል አግባብ ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።