05/07/2026
ምክር ለወጣት እንግሊዝኛ መምህራን!!!
አሁን የምታስተምሩበት ትምህርት ቤት እና አሁን የምታገኙት ገቢ ለእንተ የሚገባችሁ ላይሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ዛሬ በወጣትነታችሁ ይህን ነገር ለመቀየር የማትሰሩ ከሆነ አሁን ካላችሁበት ደረጃ ንቅንቅ ሳትሉ እንደምታረጁ አትጠራጠሩ፡፡ ቀጥሎ የሚመጣው ጥያቄ እንዴት አድርጌ ነው ይህን ነገር የምለውጠው የሚል ነው የሚሆነው፡፡ ለዚህ ደግሞ የኔን ዕውቀትና ልምድ ላካፍላችሁ!
የመጀመሪያው የቤት ስራችሁ ሁለትም ይሁን ሦስት ዓመት ይፍጅባችሁ ጊዜ ወስዳችሁ የራሳችሁን የእንግሊዝኛ ክህሎቶች በትክክል መጠቀም በሚያስችል ደረጃ ለመገንባት ስሩ፤ በተለይ የመናገርና የመፃፍ ክህሎታችሁ ላይ ትኩረት ሰጥታችሁ ስሩና እናንተም በኩራት የምትጠቀሙበት ለሌሎችም ማሰልጠን የምትችሉት ትክክለኛ ክህሎት ገንቡ፡፡ ይህን በማድረግ ሂደት ጥንቅቅ ያለ ክህሎት እስክትገነቡ ሳትጠብቁ አጠገባችሁ ያሉ የእናንተን ድጋፍ የሚፈልጉ ሰዎችን እያገዛችሁ እያስተማራችሁ ተማሩ፤ እያሰለጥናችሁ ሰልጥኑ፡፡ ያኔ ክህሎታችሁ በተግባር የተፈተነ እና በልምድ የዳበረ ይሆናል፡፡
ቀጥሎ ደግሞ ጊዜ የለኝም፣ ድካሙስ የሚል የሰነፍ ሰበባችሁን ወደጎን አድርጉና ከመደበኛ ስራችሁ ውጭ ያለውን ጊዜ አሁን ወጣት እያላችሁ ድካማችሁን ተቋቁማችሁ በአካባቢያችሁ ያሉ ተማሪዎችን በማገዝ እራችሁንም ማሕበረሰባችሁንም የምትጠቅሙ ሁኑ፡፡ ይህን በምታደርጉ ጊዜ ለምትሰጡት አገልግሎት ለዕውቀታችሁ፣ ለጊዜያችሁና ለጉልበታችሁ የሚመጥን የማሕበረሰባችሁን አቅም ያገናዘበ ክፍያ ማስከፈል ጀምሩ፡፡ ይህን ማድረጋችሁ በዕውቀት፣ በክህሎትና በገቢ አቅም እያደጋችሁ እንድትሄዱና ስራችሁን ከፍ ወዳለ ደረጃ እንድታሳድጉ ብርታት ይሰጣችኋል፡፡
እንደዚህ እየተሻሻላችሁ ስትሄዱ ሙሉ ለሙሉ እራሳችሁን ለመቻል ሽግግር ልታደርጉ ስትሉ ቋሚ ስራችሁን ትታችሁ ወደማያስተማምን ነገር የምትሄዱት ምን አቅብጡዋችሁ ነው የሚል ሙግት ከራሳችሁም ከምታውቋቸው ሰዎችም ይጠብቃችኋል፡፡ ለዚህም የኔን ዕይታ ላካፍላችሁ በመጀመሪያ ቋሚ የሚባል ነገር የለም! ቀጥሎ ሁሉም ነገር አንፃራዊ ነው! አሁን የምንወስነውን ውሳኔ የምንወስነው አሁን ባለን ዕውቀትና ልምድ ልክ ነው፡፡ ዕውቀታችንና ልምዳችን ሲጨምር ውሳኔያችንም አብሮ ይቀየራል፡፡ አሁን የሚከፈላችሁን ቋሚ ደመወዝ ሁለትና ሦስት እጥፍ በትርፍ ሰዓታችሁ እየሰራችሁ ማግኘት ከቻላችሁ የሙሉ ሰዓት ስራ አድርጋችሁ ብትሰሩት ምንድነው ሊፈጠር የሚችለው? ዓላማችሁ የጡረታ መብታችሁን ማስከበር ከሆነ እናንተ አቅም ፍጠሩና የራሳችሁን ተቋም ገንቡ እንጅ የራሳችው ተቋም ስራ አስኪያጅ ሆናችሁ በግል ድርጅት ውስጥ ተቀጥረው እንደሚሰሩ ሰራተኞች የጡረታ መብታችሁን ማስከበር ትችላላችሁ፡፡ ቀጥሎ የሚመጣው የስጋት ጥያቄ ይሄ ሁሉ ባይሳካና እናንተ እንዳሰባችሁት ባይሆንስ ነው? አይገርማችሁም ምንም አይፈጠርም! የተሻለ ዕውቀትና ክህሎት ስላላችሁ በሙያችሁ የትም ተወዳድራችሁ የማሸነፍ አቅም ሲለሚኖራችሁ ወደተቀጣሪነት መመለስ ብትፈልጉ እጃችሁን ተስማችሁ የምትቀጠሩ በባትሪ ተፈልጋችሁ የምትገኙ ባለሙያ ሆናችሁ ነው የሚደመደመው፡፡
እንዴት ልጀምር ካላችሁ ከላይ በነገርኋችሁ መሰረት እራሳችሁን ገንቡ፡፡ ከዛ ያላችሁን ዕውቀትና ክህሎት ለሰዎች በማካፈል ሙያችሁን በደንብ ማስተዋወቅና መሸጥ ጀምሩ፡፡ ያኔ ሰዎች ወደናንተ መምጣት ይጀምራሉ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ 900,000 ገደማ መምህራን ይኖራሉ ተብሎ ይገመታል፡፡ በጣም በተጋነነ ስሌት ከጠቅላላ መምህራን 20% ወይም 180,000 እንግሊዝኛ መምህራን ናቸው ብንል በጣም በትንሹ ከ120,000,000 ሕዝብ ውስጥ 667 ሰዎች የእናነተን ድጋፍ ፈልገው እየጠበቋችሁ ነው ማለት ነው፡፡
እና ምን ትጠብቃላችሁ?