የ ያኪን ስራዎች

የ ያኪን ስራዎች

Share

የተለያዩ የራሴ የስነ ፁሑፍ ስራዎች እና ሌሎች የተለያዩ አዝናኝና አስተማሪ ስራዎች በዚህ ገፅ ታገኛላችሁ። ስለ አብሮነታችሁ በእጅጉ አመሰግናለሁ!

04/04/2025

ሰላም ቤተሰቦቼ!? በያላችሁበት ሰላማችሁ ይብዛ 🙏

እነሆ ብዙ የለፋሁበት ብዙ ሰው የታዘብኩበት "የሕይወት ክር" የተሰኘው ተክታታይ ድራማዬ (የፈጣሪ ድጋፍ ውጤት) ዛሬ አርብ ከሰዓታት በኋላ ክፍል 1 በ " yakin-fb " ዩ ቲዩብ ቻናል ይለቀቃል ገብታችሁ ተመልከቱት ሀሳብ አስተያየት ስጡበት subscribe በማድረግም ቤተሰብ ሁኑ!

yakin-fb 👈 ብላችሁ you tube ላይ search በማድረግ ቤተሰብ በመሆን አጋርነታችሁ አረጋግጡልኝ። አመሰግናለሁ!!!

Photos from የ ያኪን ስራዎች's post 16/09/2024

በመኖር መንገድ መሀል "እግረ መንገድ ማግባት"

ገና ሲፈጥረው ማልዶ ሳይበረዝ ልብ ስስ ነው! ሲከፋው ቶሎ ዘንበል ይላል! አንገት መድፋት ሲችልበት! ማልቀስ ሲያውቅበት!
ልብ ደስታውም ቅርብ ነው! በሳቅ፣ መደሰት፣ መውደድና ማፍቀር መለያው ነው! ልብ ደግ ነው! መቸር ደስታው ነው!

በሁለቱም ሁኔታ ውስጥ ሆኖ ግን አንድ የማይረሳው የዘወትር ተግባሩ ለሰውነት ክፍሎቻችን በተገቢው መንገድ ደም ማስተላለፉን ነው። ለሰከንድ ስራውን ቢዘነጋ ሕይወት ቀጥ ትላለች። ታዲያ ልብ ለምን ይክፋው!? ወደ ዋናው ጉዳዬ ልግባ።

በማህበራዊ ኑሮዬ ብዙም ተግባቢ አይደለሁም። መግባባት አለመቻል ሳይሆን ከሰው ጋር መሆንን አለመፈለግ። እስካሁን ባሳለፍኩት እድሜይ 3/4ኛ የሚሆነው እድሜዬ ብቻዬን ያሳለፍኩት ይመስለኛል። ይህ ማለት አልፎ አልፎም ቢሆን የምቀርባቸው ስዎች የሉም ማለት አይደለም።

ከእለታት አንዱ ቀን ከምቀርባቸው ሰዎች ከአንዷ ጋር መገናኛ አካባቢ (ሞቢል ጋር) በሚገኘው ሰላም ታወር ሁለተኛ ፎቅ ላይ ቁጭ ብለን ሻይ እየጠጣን ስለ ሕይወት ስናወጋ ስለ ስራና ሌሎችም ወሬዎች ካወራን በኋላ ስለ ፍቅር ሕይወት ማውራት አስከተልን።

እድሜሽ እየቆሰቆሰው ነው። እያየሁሽ ልታረጂ ነው። ሰላሳ ለመግባት ጥቂት ቀረሽ። የፍቅር ሕይወትሽ እንዴት ነው? ምንድነው እቅድሽ? ይህንን ጥያቄ ባልጠየኳት ብዬ ተረበሽኩ።

እያየኋት ቀዩ ፊቷ ከፍም እሳት ቀላብኝ። አጓነበሰች! ጠረጴዛው ላይ አፈጠጠች። በሁለቱም እጆቿ የስኳር እቃውን ታሽከረክራለች። መሀላችን አስፈሪ የሆነ ዝምታ ሰፈነ። በመሀል ቀና ብላ አየችኝ። የሚያማምሩት አይኖቿ እንባ አቅረዋል። ካልወረድኩ እያሉ ተፈታተኗት። ላለማልቀስ ታገለች። ላለመሸነፍ በረታች። በየመሀሉ ወፈር ያሉት ቀይ ከንፈሮቿን በምራቋ እያረጠበች ይበልጥ ለመብላት የሚያስጎመጅ ቀይ ስጋ መሰሉ።

ይበልጥ አስተውዬ እያየኋት ምነው ችግር አለ? ብዬ ጠየኳት። "አይ የለም" የሷ መልስ ነበር። እና ለምንድነው የተረበሽው? ስል የሀዘኗን መንስኤ ለማወቅ በመጓጓት ጠየኳት። አይገርምም!? ሰዎች ያዘኑበት ነገር ለማወቆም ያጓጓል። ራሴን ታዘብኩት። ግን የምር በሁኔታዋ ተከፍቼ ነበር። ከቆይታ በኋላ " ፍቅር የሚባለው ነገር ያደክማል አይደል?" ብላ በረጅሙ ተነፈሰች። እኔ'ንጃ ያደክማል እንዴ? ጥያቄዋን በጥያቄ መለስኩ። አስተውላ አየችኝ። እጆቼን በእጆቿ ያዘች። ጎን ለጎን በተቀመጥንበትን ሶፋ ራሷን አመቻችታ ወደ'ኔ ተጠግታ አንገቷን ሰበር አድርጋ ትከሻዬን አስደገፈችው። ትንሽ እዛው ቆየች። ቀና ብላ አየችኝ። ጥሩ ጣዕም ያለው ሞቃታማው ትንፋሿ ፊቴን ሙሉ ፊቴን ገረፈኝ። በጣም የምንቀራረብ ጓደኛሞች ከመሆናችን የተነሳ ይህ አቀራረቧ ለኔ እንግዳ አልነበረም። አይዞሽ በርቺ በሚል የሀዘን ስሜት ግንባሯን ስሜ ወደ ራሴ አስጠግቼ ሳቅፋት። ይበልጥ ሰነፈች። ማልቀስ መጀመሯን ያወኩት ወፋፍራም እንባዎቹ ሸሚዜን ሲያረጥቡት ነው። ቀና አድርጊያት እንባዋን ጠራረኩላት። ትንሽ ነገር የሚያስለቅሳት ምስኪን እርግብ ነች። የሁሉ ጊዜ እንባወቿን ብንገድብ ሌላ አባይን የሚስተካከል ግድብ ይኖረን ነበር። ሰው የሚያምኑ ስስ ልቦች። ቶሎ የሚከፉ፣ በትንሽ ነገር ወዲያውኑ የሚፈነድቁ። አንዳንድ ልቦች አሉ።

ጨነቀኝ እኮ ይቅርታ ምን ተፈጥሮ ነው? ግራ በተጋባ ስሜት ደግሜ ጠየኳት። "በአጭሩ ላስረዳህ ዝርዝር ውስጥ መግባት አልፈልግም። ከዚህ ቀደም በተለያየ ጊዜ ከተለያዩ 3 ወንዶች ጋር የፍቅር ግንኙነት ነበረኝ። ከአንዱ አንዱ ይሻላል ስል በተስፋ የጀመርኳቸው የፍቅር ግንኙነቶች በተለያየ ምክንያት ሳይሳኩ ቀሩ። ከዛም በኋላ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ሆኜ ሌላ ወንድ ለመቅረብ ሞከርኩ። ይህም ሳይሆን ሲቀር ከሁሉ ነገር ራሴን አራኩ። ከረጅም ጊዜ በኋላ ግን ከድሮዎቹ አንዱ ተመልሶ መጥቶ ካላገባሁሽ በሚል አስጨነቀኝ። እናም የትም ትክክል ካልሆነ እዚሁ ከተላመድኩት ጅብ መቆየቱን መረጥኩ። በቃ መኖሬ ካልቀረ እግረ መንገዴ አግብቼ ትዳር ያዘች ቤተሰብ መሰረተች ልባል ብዬ ወሰንኩ። ከወራት በኋላ አገባለሁ። " ለሷ ከማዘን ውጪ ምንም ማድረግ አልቻልኩም ነበር። ጊዜው ደርሶ ያለችው ሁሉ እንደሆነ በወሬ ነጋሪ ሰማሁ።

ሌላኛው ከዚሁ ጋር የተያያዘ የማስታውሰው ነገር አንዲት በስራ አጋጣሚ ያወኳት ልጅ ነበረች። ይህች እህቴ ከ 16 አመቷ ጀምሮ ከብዙ ወንዶች ጋር ግንኙነት እንደነበራትና ይህም ያዝናናት እንደነበር የነገረችኝ ሲሆን አሁን ላይ የ24 አመት ወጣት ብትሆንም ወደፊት በፍፁም የማግባት ፍላጎት እንደሌላት ጭምር ተማራ ስትናገር አስተውያታለሁ።

ዋናው ማንሳት የፈለኩት ነገር የመጀመሪያ ልጅ ታሪክ እና የሁለተኛዋ ልጅ ታሪክ የሚለየው የመጀመሪያዋ የፍቅር አጋርን ፍለጋ ሲሆን ሁለተኛዋ ደግሞ ስጋዊ ፍላጎትን የማሟላት ጉዞ ነው። ሁለቱም አንድ የሚያደርጋቸው የተከበረው ቅዱስ ገላቸውን ከተለያየ ወንድ ጋር ማርከሳቸው ነው። ምክንያታቸው ለየቅል ቢሆንም ተጠያቂነት ግን አንድ ያደርጋቸዋል። የወንዶችም እጅ አለበት።

የኔን ሀሳብ እዚህ ላይ ገታ ላድርግና የአዳም ረታ "መረቅ" በተሰኘው መፅሐፉ ላይ ገፅ 344 ከላይ ከፃፍኩት ሀሳብ ጋር የሚቀራረብ ፁሑፍ ላጋራችሁ ወደድኩ። እነሆ፡-

.. "ሌላ የምነግርህ ነገር ቢኖር እድሜህ ሳይገፋ ሚስት አግብተህ ልጅ መውለድ እንዳለብህ ነው። ሚስት ስታገባ ወንድ የማታውቅ አግባ። ሀብት ይኑራት አይኑራት አይደለም። መጠንቀቅ ያለብህ ለትዳር ድፍን ሴትን የመሰለ የለም። ለምን? በለኝ 'ለምን' ማለት ጥሩ ነው።

ድፍን ሴት ማለት ላይና ታቿ ልክ እንደ ሸንኮራ አገዳ የተዘጋ ነው። ውስጧ ማንም ያልነካው መረቅ ነው። በማህፀኗ ያለው አየር ክፋት ያልገባው ነው። ምድርና ሰማይ ሲፈጠር አዳምን ያቆመው፣ ከእግዜር ጋር አብሮ የማገው አየር እዛ ነው ያለው።

'ዮሀንስ አፈወርቅ፡- " ' የሀጢያት ምንፃፍ የማታውቅ ነውር የሌለባት ድንግል ሴት ክብር ናት። እንዲህ ያለችቱ ሴት ነፍሳት በፀጋና በክብር በተገኙበት ጊዜ ዋጋዋን ታገኛለች" ' ይላል። በዘመኑ እኮ የበኩር ልጅ እየጠፋ ነው። ... የበኩር ልጅ መጀመሪያ የተወለደ ወይም የተወለደች ማለት አይደለም። ቁጥር አይደለም። ያለ ድንግልና መበ'ከር የለም። ... "

* * * * * /////// * * * * *

ይህን መፅሐፍ ብታነቡት ታተርፋላችሁ። ከማንበብ አትስነፉ።

👉 ሌላኛው ነገር ፡- የሴቶቹን ጉዳይ ወንዶችንም ይመለከታል ባይ ነኝ። ብትችሉ ከጅምሩ ንፁህ ሁኑ። ድንገት ስጋዊ ነገር ቢያሸንፋችሁ እንኳን የኔ ከምትሏት ጋር በንሰሀ ታጥባችሁ አንዱ ሁኑ! አመሰግናለሁ!

08/08/2022

. . . 🤔 🤔 🤔 . . .
(✍️@ያኪን ሀ/ማርያም )

ከየትም ልጀምር ብል ጅማሮ የለሽም
አያልቅበት እሱ ፍፃሜ አልሰጠሽም
ሁሌም ይፈጥርሻል
ሁሌም ይሰራሻል
በማያልቅ ጥበቡ
ባንቺ መጠበቡ
ሸብ አርጎ ወገቡ
አንቺን መስራት ይዟል
ውበትሽ አይሏል
አዳም ባንቺ ፈዟል

አንቺን መሳያ
አንቺን ማድመቂያ
መሬትን ሸራ ሰማይን ብራና
ውቅያኖስን ቀለም
ከጨረቃ ፀሐይ ከከዋክብት ወቅሮሽ
በደም ግባት ሞልቶ አንድ አንቺን አበጀሽ

ደግሞም የሚደንቀኝ ከእቅፌ መኖርሽ
ብወድሽ ወዳጄ ሆኖ መገኘትሽ
ህልም ቅዠት መስሎኝ ላለመንቃት ስጥር
ድንገት እንዳልባንን ስፈራ ስቸር

ቀን ያደምቃል ፀሐይሽ
ምሽት ጨረቃሽ
ተዳምሮ ኮከብሽ
በደስታ ይሞላሉ
በሀሴት ያሰክራሉ

ቀንና ምሽቱ መለየት ተስኖኝ
ቅጥ ያጣው ውበትሽ መዓዛሽ ጠራኝ
ከአደይ አበባ ጎልተሽ የምትደምቂ
በጭጋግ ውርጭ መሀል ነብሴን ምታሞቂ
ንገሪኝ ምን ጉድ ነሽ!?🤦‍♂️
የውበትሽ ጥግስ የት ነው መጨረሻሽ!?🤔
( እኔ'ንጃ )

ይመስለኛል እሱ
የጥበብ ንጉሱ
የእውቀቱ ጥግ ሊያደርግሽ ናሙና
ባንቺ ሁሉን ሊገልጥ ተነሳስቷልና
መጨረሻ አልባው ማየት ነው ጉዱን
አንቺን መፍጠሩን ማቆንጀት ማስዋቡን
ይቀጥል ንጉስ
አንቺን ማስዋብ ሱሱ


እኔም አይታክተኝ አንቺን ማወደሱ!
ውብ ነሽ! የውበት ጥግ
ፀሐይና ጨረቃ - ኮከብ የሚያስፈግግ
በፍቅርሽ ተማርከው - አንቺን የሚያስጠራ
ከነሱ ላቅ ብለሽ - ሆነሽ የሱ ስራ

መሬት ቆዳዋ ስፍቷት - ታየች ተሸማቃ
ሰማይ ኩርምት አለች - መድመቅሽን አውቃ

ምን ይደረግ ታዲያ!?
ጥበቡን ማሳያ
ላይኖርሽ አምሳያ
ሁሌም ሲጠበብ
ውበትሽ ሲያብብ
መደመም ነው ማድነቅ
ስራው ሚስጢር ረቂቅ
ባንቺ ሲራቀቅ!

ሰማይና ምድር - ያልፋሉ እንዳለው
ቃሌ ግን አያልፍም - በሚል እንዳፀናው
ሰማይ ምድር ቢያልፍ
ይፅና እንደ ቃሉ - ውበትሽ አይርገፍ!
* * * * *
20/9/2014 ዓ.ም

15/05/2022

. . . ጊዜ ሲሰግጥ! . . .
(@✍️ ያኪን ሀ/ማርያም)

በጥሎ ማለፍ - እንደ ጉድ
ካለሁበት ፈቅ ሳልል - እሱ ሲነጉድ

መልስ አልሰጥ አለኝ - ህልምህን አልፈታ
ወይ ዝም ብለን አንቀር - አሸልበን ላፍታ
አወዛግቦን ከረምን - የጊዜ ድንፋታ

ህልም አይተነትን - መልስ አይሰጥ
እንዲህ ነው - ጊዜ ሲሰግጥ!

ጊዜ ጊዜ ኖሮት - ራሱን እስኪያደምጥ
ከራሱ አውርቶ - ለኔ መልስ እስኪሰጥ
አብሮ ነው መጃጃል - ወጥሮ መሰገጥ!
ባይዋጥም እንኳን ዝም ብሎ ማላመጥ!
* * * * *
06/09/2014
✍️ መታሰቢያነቱ፡ ሞክሬ ላልተሳኩ
ነገር ግን ጊዜ ለሚጠብቁ ህልሞቼ ይሁን!

✍️ በነገሮች ጨጓራዬ ነዶ፤ ቁርስ ጨጓራ እየበላሁ ታረቀኝ ሆቴል-መገናኛ የተፃፈ!

13/02/2022

. . . ውሸት ነው! . . .
( ✍️@ያኪን ሀ/ማርያም )

ሰው በሞላበት - ተትረፍርፎ ሳለ
ወዳጅ ባላጣበት - ምነው አንቺን አለ
ልቤ አጥብቆ ሻተሽ - ዱካሽ ተከተለ
አንቺ የትም አለሽ - በልቤ የማዝልሽ
አግዝፌ ምስልሽ - በልቤ ማነግሰሽ!
.
.
.
ብዬ ቃላት ላስውብ - ፊደል ልሞሻሽር
በቀላጤው አፌ - በተዋኙ ብዕር
ልዋሽሽ አልኩና - ግጥም ልደረድር
ተውኩት!
ምክንያት ብትይ! በሌለበት እውነት
ይገዝፋል ውሸት! ይመዝናል ሀሰት!
* * * * *
አዳማ- ናዝሬት ( Health international Hotel)
18/5/2014 ዓ.ም

27/09/2021

... ፊደል አልባ ውበት! ...
. (@ ያኪን ሀ/ማርያም )

ልክ ጠዋት ማልዳ
እንደምትወጣ ጎህ ቀዳ
እንደ ፀሐይቱ
የንጋት ብስራቱ
ውበትሽ ይደምቃል
በሐሴት ያሞቃል
እንደ ጥልቅ ውቅያኖስ
በዝግታ 'ሚፈስ
እንደገጠር ፋኖስ
ጨለማን የሚያምስ
ውበትሽ እንዲያ ነው
ቃላት የማይገልፀው
እያዩት የሚያፈዝ
በአግራሞት አፈ 'ሚያሲዝ
አንቺ ማለት ይህ ነሽ
ብለን የማንገልፅሽ
ከሁሉም ልዩነሽ
ከጥቅምት አበባ...
ያውዳል ማዓዛሽ
ይጣራል ወዘናሽ
በምን እንመስልሽ!?
ልዩ ነው መለያሽ
የውበት ታላቁ
ፊደል የሚያስንቁ
በደስታ ሚያከንፉ
ባህር ሚያስቀዝፉ
እልፍ አዕላፍ ውበት
ልክ አልባ መሠጠት
የምሽት ጨረቃ
ያንቺን መኖር አውቃ
በውበትሽ ደምቃ
ባንቺ ተደብቃ
አየን ተዓምር
አንቺውኑ ስትዘክር
ዝም ብዬ ዝም ልበል
የውበትሽን ከፍታ በቃል ከማባብል!
ብቻ ደምቀሽ ኑሪ
በጨለመው ዓለም ፍክት ብለሽ ብሪ
ተዓምራቱ ብዙ! ስራው የፈጣሪ!
11/01/14 ዓ.ም መሶብ ሀበሻ ሆቴል(መገናኛ- አዲስ አበባ)

02/05/2021

. ! የአንድነት ጥሪ! .
(ያኪን ሀ/ማርያም)
✍️ ድምፅ አልባ ፊደላት
ትርጉም አልባ ቃላት
ሰሚ ያጡ
በወጉ ያልተደመጡ

✍️ እኔ አንተን ያላስታረቁ
አንድ ያላረጉን በሕልቁ
ዛሬም ይጮሀሉ አብዝተው
አንድ እስኪያረጉን መች ሰልችተው!?
ይኸው ዛሬም ፊደል ላዋቅር
ቃላትን ልደርድር
አንድ ሆነን አንድነትን እስክንዘክር

✍️ ሕዳጥ ተስፋ አንሸራታን
እህል ይመስል በዘር አጥራን

✍️ የአስተሳስባችን አድማስ ጠባ
ሕይወት ሆነች ትርጉም አልባ

✍️ ወንድሜ ብዬ አላቅፍህ ነገር
ዘር የሚሉት በሽታ ሰርቶ አጥር

✍️ አልስቅልህ ከልቤ
ጎጠኝነት ሸርቤ
የእኔነት ካባ ደርቤ

✍️ ድሮ ቀረ ያኔ
መሆንህ ወገኔ
መቆምህ ከጎኔ

✍️ ናፈቀኝ ያ ትላንት
አንተ ትብስ አንቺ የተባባልንበት!

✍️ አሁንሜ ሳቄ ሳቅህ የውሸት
እቅፌ እቅፍህ የሀሴት
ሁሉም የወረት
ሁሉ ካንገት በላይ
በጎጥ ስንተያይ
ልናልፍ እንደዋዛ
ለዚህች አጭር ዕድሜ ...
'ምትደርቅ እንደ ጤዛ

✍️ ይልቅ ብልህ ከሆንክ....
ዘመነኛ ሆነክ
ዘመኑ ከገባክ...
ከሙዳ አልባ ሙደኞች
ከዘር ቆጣሪዎች
ከጎጥ ቀማሪዎች
ራስህን አርቅ
ከዘመኑ ምጠቅ
ከዘር ጎጠኝነት ከጠባብነት ተላቀቅ!

✍️ ቁጥር ለናፈቃት ለዚህች ትንሽ ዕድሜ
አልሁን ህመምህ አትሁን ህመሜ
በፍቅር እንድንተያይ አንድ እንድንሆን እንደ ጥንቱ
አንርሳ ያ ትላንት የአያቶቻችን የጠዋቱ!
ታሪክ አጠልሽተን አንለፍ በከንቱ!

08/08/2013 ዓ.ም ምሽት 1 ሰዓት ተፃፈ!

Photos 11/10/2019

ትልቅ አድርጓ ፈጥሮናልና በአስተሳሰብ አንነስ

Want your school to be the top-listed School/college in Addis Ababa?

Click here to claim your Sponsored Listing.

Location

Telephone

Website

Address

Addis Ababa