12/05/2026
ቃሉን እንማር /Kalun Enmar
እንደ ዕዝራ ቃሉን የሚፈልግ የሚኖር እና በአግባቡ የሚያስተም https://www.youtube.com/channel/UCNz7MqCOz-nl0B5SITmKMHQ
12/05/2026
የንባብ ክፍል፡- ሰቆቃው ኤርምያስ 1፣ 2፣ 3፣ 4 እና 5
ሰቆ. ኤርምያስ 1፤ ሕዝብ ተሞልታ የነበረች ከተማ እንዴት የተተወች ሆና ቀረች! እንዴት እንደ መበለት ሆነች! ባሪያ ሆናለች፤ ታለቅሳለች የሚያጽናናት የለም፤ ይሁዳ ተማርካ ሄደች፤ ባለጋሮቿ ገዦቿ ሆኑ፤ ከኀጢአት ብዛት የተነሣ እግዚአብሔር ከባድ ሀዘን አምጥቶባታል፤ ጠላቶቿ ሳቁባት፤ ኢየሩሳሌም ከባድ ኀጢአት ሠርታለች፤ ስለዚህ የረከሰች ሆናለች፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ መከራዬን ተመልከት፤ ጽዮን እጆቿን ዘረጋች፤ የሚያጽናናትም የለም።
ሰቆ. ኤርማያስ 2፤ እግዚአብሔር የጽዮንን ሴት ልጅ በቁጣው ደመና እንዴት ጋረዳት! የያዕቆብን መኖሪያ ሁሉ እግዚአብሔር ያለ ርኅራኄ ዋጣቸው፤ በቁጣው አፈረሳቸው፤ ለቅሶና ሰቆቃ በዛ፤ እግዚአብሔር መቅደሱን ተወ፤ ቁስልሽ እንደ ባሕር ጥልቅ ነው፤ ማን ሊፈውስሽ ይችላል? እናቶች ሕፃኖቻቸውን ይብሉን? ካህኑና ነቢዩስ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ውስጥ ይገደሉን? ወጣትና ሽማግሌ አንድ ላይ ወደቁ።
ሰቆ. ኤርምያስ 3፤ በቁጣው በትር መከራ ያየ ሰው እኔ ነኝ፤ ጸሎቴን መስማት አልፈለገም፤ መንገዴን ዘጋ፤ ያለ ረዳት ተወኝ፤ መላገጫ ሆንሁኝ፤ ሆኖም ተስፋ አለኝ፤ ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምሕረት የተነሣ ነው፤ ርኅራኄው አያልቅምና፤ ጌታ አይጥልም፤ ቢያሳዝንም እንደ ምሕረቱ ብዛት ይራራልና፤ መንገዳችንን እንመርምር፤ እንፈትን፤ ወደ እግዚአብሔርም እንመለስ፤ ዐምፀናል፤ ኀጢአትም ሠርተናል እንበል፤ እግዚአብሔር ከላይ ከሰማይ እስኪያይ ዐይኖቼ ዕንባ ያፈሳሉ፤ ፍርዴን ፍረድልኝ!
ሰቆ. ኤርምያስ 4፤ ወርቁ እንዴት ደበሰ! ንጹሑስ ወርቅ እንዴት ተለወጠ! እንደ ወርቅ ይቆጠሩ የነበሩ አሁን እንደ ሸክላ ዕቃ ሆኑ፤ ከውሃ ጥም የተነሣ የሕፃናት ምላስ ከላንቃቸው ጋር ተጣበቀ፤ በራብ ከሚሞቱት ይልቅ በሰይፍ የተገደሉት ይሻላሉ፤ ሴቶች በገዛ እጆቻቸው ልጆቻቸውን ቀቀሉ፤ ይህ ከነቢያት ኀጢአት፣ ከካህናቷም መተላለፍ የተነሣ ሆኖአል፤ ከሰማይ ንስሮች ይልቅ ጠላቶቻችን ፈጣኖች ናቸው።
ሰቆ. ኤርምያስ 5፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ በእኛ ላይ የደረሰውን አስብ፤ ውርደታችንን እይ፤ ተመልከትም፤ እንጨትና ውሃ በክፍያ፤ አባቶቻችን ኀጢአት ሠርተው አለፉ፤ እኛም የእነርሱን ቅጣት ተሸከምን፤ ደስታ ከልባችን ጠፍቷል፤ ወዮልን! ኀጢአት ሠርተናልና፤ ለምን ፈጽመህ ትረሳናለህ? ስለምንስ ለረጅም ጊዜ ትተወናለህ? ወደ አንተ መልሰን እኛም እንመለሳለን፤ ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድስ!
ከተማርኩት፡-
• የኀጢአት፣ እግዚአብሔርን ያለመስማት ውጤት ምን ያህል ከባድ እንደ ሆነ ይህ መጽሐፍ ያሳያል። እግዚአብሔር ባለመስማት በኀጢያታቸው የጸኑትን ይቀጣል፤ ቅጣቱም ከባድ ነው!
• ነቢዩ የቀደመችዋን ኢየሩሳሌም ከፈራረሰችው ጋር እያስተያየ በእግዚአብሔር ፊት ያለቀሰበት መንገድ ልብ የሚነካ ነው!
• ለእግዚአብሔር ፍርድ ዕውቅና በመስጠት በእውነተኛ ንስሐ መመለስ ያስፈልጋል።
• “ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምሕረት የተነሣ ነው፤ ርኀራኄው አያልቅምና፤ ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው፤ ታማኝነትም ብዙ ነው።”
• “እግዚአብሔር ዕድል ፈንታዬ ነው፤ ስለዚህ ተስፋ አደርገዋለሁ። እርሱን ተስፋ ለሚያደርጉት ለሚፈልገውም ሰው እግዚአብሔር መልካም ነው፤ ሰው የእግዚአብሔርን ማዳን ዝም ብሎ ተስፋ ቢያደርግ መልካም ነው።”
• “እግዚአብሔር ሰውን ለዘላለም አይጥልምና፤ መከራ ቢያመጣ እንኳ ይራራል፤ ታላቅ ፍቅሩ አይለወጥምና።”
• “እግዚአብሔር ሆይ፤ ወደ አንተ መልሰን፤ እኛም እንመለሳለን፤ ዘመናችንን እንደ ቀድሞው አድስ!
ቃሉን እንጸልይ፡-
• በግል ሕይወታችን፣ በቤተ ሰባችን፣ በቤተ ክርስቲያንና በአገር ደረጃ ስለ ተለያዩ የፈራረሱ፣ የተበላሹ ነገሮች ወደ እግዚአብሔር እንጸልይ!
• እግዚአብሔር በሥራው ትክክለኛ አምላክ እንደ ሆነ ዕውቅና በመስጠት እውነተኛ ንስሐ እናድርግ!
• እግዚአብሔርን እንደምንታመነው እና ተስፋችን እርሱ ብቻ እንደ ሆነ በመግለጽ እንጸልይ!
ቢያሳዝንም እንደ ምሕረቱ ብዛት የሚራራ አምላክ ተስፋችን ነው! ጸጋ ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 49፣ 50፣ 51 እና 52
ኤርምያስ 49፤ ስለ አሞን የተነገረ መልእክት፤ የአሞናውያን ከተማ የፍርስራሽ ክምር ትሆናለች፤ ስለ ኤዶም የተነገረ መልእክት፤ የልብህ ኩራት አታሎሃል፤ ከዚያ ወደ ታች እጥልሃለሁ፤ ስለ ደማስቆ የተነገረ መልእክት፤ ስለ ቄዳርና ስለ ሐጾር የተነገረ መልእክት፤ ስለ ኤላም የተነገረ መልእክት፤ እግዚአብሔር ይቀጣል፤ የኋላ ኋላ ምርኮን ይመልሳል።
ኤርምያስ 50፤ ስለ ባቢሎን የተነገረ መልእክት፤ እግዚአብሔር የባቢሎንን ንጉሥና ምድሩን ያቀጣል፤ በባቢሎን ውድቀት ድምፅ ምድር ትናወጣለች፤ ጩኸቷም በሕዝቦች መካከል ያስተጋባል።
ኤርምያስ 51፤ እንዲያበጥሯትና እንዲያወድሟት ባዕዳንን በባቢሎን ላይ እልካለሁ፤ እግዚአብሔር ባቢሎንን ያጠፋል፤ ባቢሎን የድንጋጤና የመሳለቂያ ምልክት ትሆናለች፤ ኤርምያስ በባቢሎን ላይ የሚመጣውን ጥፋት ሁሉ በብራና ጥቅልል ላይ ጻፈው፤ ሠራያ ባቢሎን ሲደርስ እንዲያነበውና ሲጨርስ ድንጋይ አስሮበት ወደ ኤፍራጤስ ወንዝ እንዲጥለው ነገረው፤ ባቢሎን እንዲህ ትሰምጣለች፤ ከእንግዲህ አትነሣም፤ ሕዝቧም ይወድቃል።
ኤርምያስ 52፤ የኢየሩሳሌም ውድቀት፤ ሴዴቅያስ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ አደረገ፤ ባቢሎናውያን ይሁዳን ከበቡ፤ ራብ ሆነ፤ ሴዴቅያስ ተያዘ፤ ወንዶች ልጆቹ በፊቱ ታረዱ፤ ባለሥልጣኖቹ ተገደሉ፤ የሴዴቅያስን ዐይን አውጥተው እስከ ዕለተ ሞቱ በእስራት አቆዩት፤ ቤተ መቅደሱ፣ ቤተ መንግሥቱና ቤቶች ሁሉ ተቃጠሉ፤ ሕዝቡ ተማረከ፤ የከበሩ ዕቃዎች ተማረኩ፤ ዮአኪን ተፈታ፤ ከንጉሥ ማእድ በላ፤ ቀለብ ይሰጠው ነበር።
ከተማርኩት ፡-
• በተለያዩ መንግሥታት ላይ የተላለፈው መልእክት እግዚአብሔር በጊዜው የሚፈርድ አምላክ መሆኑን ያሳያል።
• ግፍና በደልን ፈጽሞ ሳይቀጣ የሚቀር የለም። መንግሥታትና ሕዝቦች ሁሉ ለፈጸሙት ግፉና በደል በእግዚአብሔር ጊዜ የእጃቸውን ያገኛሉ።
• ጠንካራውና የማይበገር የሚመስለው ደካማና ርዳታ ፈልጎ የሚያጣበት ጊዜ ይመጣል።
• እግዚአብሔር ሕዝቡን ለመቅጣት/ለማስተማር ባቢሎንን ቢጠቀምም በጊዜው ባቢሎንን የሚቀጣበት መንገድ የሚገርም ነው። በባቢሎን ላይ እንደሚደርስ የተነገረው ነገር አስፈሪ ነው።
• የእግዚአብሔር የበቀል ጊዜ ያስፈራል!
• በመጨረሻው ምእራፍ የኢየሩሳሌም ውድቀት የተተረከበት መንገድ የሚያሳዝን ነው። ሕዝቡ እግዚአብሔርን ባለመስማቱ ለጠላቶቹ አልፎ ተሰጠ።
ቃሉን እንጸልይ፡-
• እግዚአብሔርን ባለመስማት ከፍተኛ ውድቀት እንዳያገኘን በእግዚአብሔር ፊት ራሳችንን እየመረመርን እንጸልይ።
• በእግዚአብሔር ፊት በንስሐ እንቅረብ።
• እግዚአብሔር ሲቀጣ ያስፈራል፤ ምሕረቱን እንለምን።
በዘመናት ሁሉ መካከል የማይደክምና መንግሥቱ ጽኑ የሆነው እግዚአብሔር ብቻ ነው። ጸጋው ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 46፣ 47 እና 48
ኤርምያስ 46፤ ስለ ግብፅ የተነገረ መልእክት፤ የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር መጥቶ ግብፅን እንደሚወጋ ኤርምያስ ያስተላለፈው መልእክት፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን ተማርኮ ከሄደበት ይሰበስባል፤ ዕረፍትም ይሰጠዋል።
ኤርምያስ 47፤ ስለ ፍልስጥኤማውያን የተነገረ መልእክት፤ እግዚአብሔር ፍልስጥኤማውያንን ሊያጠፋ ተነሥቷል፤ የፍልስጥኤማውያንን በደል እና የሚመጣው የእግዚአብሔር ፍርድ ተገልጽዋል።
ኤርምያስ 48፤ ስለ ሞዓብ የተነገረ መልእክት፤ የሞዓብ ውድቀት ተቃርቦአል፤ ጥፋቱም ፈጥኖ የመጣበታል፤ የሞዓብ ትዕቢት፣ ኩራት፣ ትምክሕት፣ የልቡ ማበጥ ይጠፋል። የሞዓብ ኀጢአትና የእግዚአብሔር ፍርድ በዝርዝር ቀርቦአል።
ከተማርኩት፡-
• የእግዚአብሔር መንግሥት፣ አገዛዝ ከምድራዊ መንግሥታት ሁሉ በላይ ነው። እርሱ የመንግሥታትን ሥራ ይመዝናል፤ ለጥፋቶቻቸውም ተጠያቂ ያደርጋቸዋል።
• የትኛውም ኀያል የሆነ ምድራዊ መንግሥት ፍጻሜ አለው።
• “አገልጋዬ ያዕቆብ ሆይ፤ አትፍራ፤ እስራኤል ሆይ አትሸበር፤ አንተን ከሩቅ ስፍራ ዘርህንም ተማርኮ ከሄደበት ምድር አድናለሁ። ያዕቆብ ተመልሶ በሰላምና በርጋታ ይቀመጣል፤ የሚያስፈራውም አይኖርም። አገልጋዬ ያዕቆብ ሆይ፤ አትፍራ፤ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ ይላል እግዚአብሔር፤ …።”
• እግዚአብሔር የተለያዩ መንግሥታትን እንደሚቀጣ መናገሩ የበላይነቱን ብቻ ሳይሆን መንግሥታት ለሥራዎቻቸው ተጠያቂዎች የሚሆኑበት ጊዜ እንደሚመጣ ያሳያል።
• እግዚአብሔር ትዕቢትን፣ ኩራትን፣ ትምክሕትና ጉራን ሁሉ ያጠፋል፤ ያስተነፍሳል!
• ከእግዚአብሔር ፍርድ የሚያመልጥ የለም!
ቃሉን እንጸልይ፡-
• ፍጻሜ የሌላት የእግዚአብሔር መንግሥት በምድር ሁሉ ላይ ከፍ ብላ እንድትታይ እንጸልይ። መንግሥቱ ትምጣ!
• እግዚአብሔር ከትዕቢት፣ ኩራት፣ ትምክሕትና ጉራ እንዲጠብቀን እንጸልይ፤ ልባችንንም እንመርምር።
• የእግዚአብሔር ፍርድ እንዳያገኘን አካሄዳችንን እየመረመርን እንጸልይ።
እግዚአብሔር በመንግሥታትን ሁሉ ላይ የበላይ ገዢና ተቆጣጣሪ ነው። ጸጋው ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 43፣ 44 እና 45
ኤርምያስ 43፤ የኤርምያስን መልእክት ተቃወሙ፤ ዋሽተሃል፤ እግዚአብሔር ወደ ግብፅ አትሂዱ አላለም አሉ፤ እርሱንና ሌሎች ቅሬታዎችን ይዘው ወደ ግብፅ ገቡ፤ ኤርምያስ ግብፅ በባቢሎን እንደምትመታ ተናገረ።
ኤርምያስ 44፤ ወደ ግብፅ የሄዱት ሰዎች ጣዖታትን አመለኩ፤ ኤርምያስ እግዚአብሔር እንደሚቀጣቸው ተናገረ፤ እነርሱ ግን አንሰማም፤ የፈለግነውን ሁሉ እናደርጋለን አሉት፤ ኤርምያስ እግዚአብሔር ፈጽሞ እንደሚያጠፋቸውና ግብፅንም ለባቢሎን አሳልፎ እንደሚሰጥ ተናገረ።
ኤርምያስ 45፤ ኤርምያስ ለባሮክ ያስተላለፈው መልእክት፤ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ማለፉ አይቀሬ ቢሆንም እግዚአብሔር በሄደበት ሁሉ ሕይወቱን እንደሚያተርፍለት ነገረው።
ከተማርኩት፡-
• ኤርምያስ ከእግዚአብሔር ሰምቶ የሚናገረውን ሁሉ እንደሚቀበሉና እንደሚታዘዙ ቃል ቢገቡም መልእክቱን ከሰሙ በኋላ ዋሽተሃል፤ እግዚአብሔር አላለህም በማለት ወደ ግብፅ መሄዳቸው ይደንቃል። የፈለጉትን መልእክት ባለመናገሩ የገቡትን ቃል ሽረው ኤርምያስን እንደ ሐሰተኛ ቆጠሩት።
• “… አገልጋዬን የባቢሎንን ንጉሥ ናቡከደነፆርን እንዲመጣ አደርጋለሁ፤ …” - ይህን የአሕዛብ ንጉሥ “አገልጋዬን” ብሎ መጥራቱ እጅግ ይገርማል። እግዚአብሔር ብዙና ልዩ ልዩ አገልጋዮች አሉት።
• ወደ ግብፅ የሄደው ሕዝብ ጣዖታትን እንዴት እንዳመለከ የተገለጸበት መንገድ እና በኤርምያስ በኩል መልእክት ቢመጣላቸውም እንደውም ይበልጥ እንደሚያመልኩ የገለጹበት መንገድ እጅግ የሚያሳዝን ነው። “አንተ በእግዚአብሔር ስም የነገርኸንን መልእክት አንሰማም፤ እናደርጋለን ያልነውን ሁሉ እናደርጋለን፤ … ለሰማይዋ ንግሥት እናጥናለን፤ የመጠጥ ቁርባን እናፈስላታለን።”
• ባሮክ “በሕመሜ ላይ ሐዘን ጨምሮብኛልና ወዮልኝ፤ ከለቅሶዮ ብዛት የተነሣ ደክሜያለሁ፤ ዕረፍትም የለኝም” ባለ ጊዜ እግዚአብሔር ለራሱ ታላቅ ነገር እንዴት ትሻለህ? በማለት የሞገተበት መንገድ እና በሚሄድበት ሁሉ ሕይወቱን እንደሚያተርፍለት የሰጠው ተስፋ አስተማሪ ነው።
ቃሉን እንጸልይ፡-
• በምንሄድበት ሁሉ የእግዚአብሔር አብሮነትና ትድግና እንዲበዛልን እንጸልይ።
• አገልጋዮች እግዚአብሔር የሚናገረውን ብቻ እንዲናገሩ፣ ሕዝቡም እንዲሰማ እንጸልይ።
• እግዚአብሔር የተናገረውን የሚፈጽም እውነተኛ አምላክ ነው። ምስጋና ይገባዋል።
በድፍረት እግዚአብሔርን አንሰማም፤ የወደድነውን እናደርጋለን የሚሉ ሁሉ ይጠፋሉ! ጸጋው ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 40፣ 41 እና 42
ኤርምያስ 40፤ የዘበኞች አዛዥ ናቡዘረዳን ኤርምያስን አስፈታው፤ ወደ ባቢሎን መሄድ ወይም ወደ ጎዶልያስ ተመልሶ በሕዝቡ መካከል መቀመጥ ቢፈልግ የወደደውን እንዲያደርግ መከረው፤ የጎዶልያስ መሾም እና በምጽጳ ሳለ የብዙዎች ወደ እርሱ መምጣት።
ኤርምያስ 41፤ የናታንያ ልጅ እስማኤልና አብረውት የነበሩ ዐሥር ሰዎች ጎዶልያስን በሰይፍ ገደሉ፤ በማግስቱም ወደ ቤተ መቅደሱ ለመቅረብ የመጡ ሌሎች ሰዎችን ገደሉ፤ ዮሐናንና ከእርሱ ጋር የነበሩ የጦር መኮንኖች እስማኤልን ለመውጋት ተነሱ፤ እርሱም ሸሽቶ ወደ አሞናውያን ሄደ፤ ዮሐናንና ሌሎች ወደ ግብፅ መሸሽ ጀመሩ።
ኤርምያስ 42፤ ኤርምያስ እንዲጸልይላቸው ጠየቁ፤ ኤርምያስም ከእግዚአብሔር የሰማውን እንደሚነግራቸው ገለጸ፤ የምትለንን እንሰማለን አሉ፤ ኤርምያስ በግብፅ ለመኖር ወደዚያ ቢሄዱ ከባድ አደጋ እንደሚያገኛቸው ተናገረ።
ከተማርኩት፡-
• የክብር ዘበኞች አዛዥ የነበረው ናቡዘረዳን ከይሁዳ ወደ ባቢሎን በሚወሰዱት ምርኮኞች መካከል ኤርምያስ በሰንሰለት ታስሮ ባገኘው ጊዜ አስፈታው። በምርኮ እንዳይወሰድ እግዚአብሔር ለኤርምያስ ሰው ሰጠ።
• የናታንያ ልጅ እስማኤልና አብረውት የነበሩ ዐሥር ሰዎች የባቢሎን ንጉሥ ከምርኮ በቀሩት ላይ የሾመውን ጎዶልያስን የገደሉበት መንገድ እና ሕዝቡን ማርኮ ወደ አሞናውያን ለማሻገር ያደረገው ጥረት ይገርማል።
• ኤርምያስ ለተረፈው ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር እንዲጸልይ ተጠየቀ፤ እርሱም እግዚአብሔር ያለውን ብቻ እንደሚነግራቸው አስታወቀ። ከዐሥር ቀን በኋላ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኤርምያስ መጣ!
• “አሁንም የሚያስፈራችሁን የባቢሎንን ንጉሥ አትፍሩ፤ አድናችሁ ዘንድ ከእጁም አስጥላችሁ ዘንድ እኔ ከእናንተ ጋር ነኝና አትፍሩ ይላል እግዚአብሔር!” በአስፈሪ ሁኔታ ውስጥ ለነበሩ ይህን መልእክት በድፍረት መናገሩ አስተማሪ ነው።
• ኤርምያስ የተናገረው የጥፋት ትንቢት ሲፈጸም በዐይኑ የተመለከተ ነቢይ ነው!
ቃሉን እንጸልይ፡-
• እግዚአብሔር ሰው እንዲሰጠን እንጸልይ።
• እግዚአብሔር ያለውን ብቻ በሚነግሩን ሰዎች እንዲባርከን እንጸልይ።
• በነገር ሁሉ ብቻ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር እንዲሆን እንጸልይ።
እግዚአብሔር በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ያልታሰቡ ሰዎችን ያዘጋጃል! ጸጋው ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 37፣ 38 እና 39
ኤርምያስ 37፤ ሴዴቅያስና ሕዝቡ በኤርምያስ የተነገረውን ቃል አልሰሙም፤ ኤርምያስ ምርኮ አይቀሬ መሆኑን ገለጸ፤ ኤርምያስ ታሰረ፤ ተደበደበ፤ በቀን አንድ እንጀራ እየተሰጠው በዘብ ጠባቂዎች አደባባይ ተቀመጠ።
ኤርምያስ 38፤ ይህች ከተማ ለባቢሎን ትሰጣለች፤ በዚህ የሚቀር ይሞታል፤ ኤርምያስ በውሃ ጉድጓድ ውስጥ ተጣለ፤ ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክ ኤርምያስ ከጉድጓድ እንዲወጣ አደረገ፤ ኤርምያስ ለሴዴቅያስ ማድረግ ያለበትን ነገረው።
ኤርምያስ 39፤ የኢየሩሳሌም መውደቅ፤ ሰዴቅያስ ተማረከ፤ ዐይኖቹን አወጡ፤ ባቢሎናውያን ቤተ መንግሥቱንና ቤቶችን አቃጠሉ፤ የኢየሩሳሌምን ቅጥር አፈረሱ፤ ጎዶልያስ ተሾመ፤ አቤሜሌክ ጉዳት እንደማይደርስበት ተነገረው።
ከተማርኩት፡-
• ነቢዩ ኤርምያስ በትክክል ከእግዚአብሔር የሰማውን ቃል ብቻ ብያስተላልፍም ልዩ ልዩ መከራ ደርሶበታል፤ ታስሯል፤ ተደብድቧል፤ ከድቶ ወደ ባቢሎን ሊሄድ ነው በማለት በሐሰት ተወንጅሏል፤ በጉድጓድ ተጥሏል፤ ወዘተ.። እውነትን መናገር ዋጋ ያስከፍላል፤ ዋጋም አለው።
• ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክ ለነቢዩ ኤርምያስ ያደረገው መልካም ነገር ፍሬ አፍርቷል፤ “አንተን ግን በዚያን ቀን አድንሃለሁ፤ ይላል እግዚአብሔር ለምትፈራቸው ሰዎች ዐልፈህ አትሰጥም። እታደግሃለሁ፤ በእኔ ታምነሃልና በሕይወት ታመልጣለህ እንጂ በሰይፍ አትወድቅም፤ ይላል እግዚአብሔር።”
• የኢየሩሳሌም ውድቀት፣ በሕዝቡና በከተማዋ ላይ የሆነው ነገር ልብ ይነካል። እግዚአብሔርን አለመስማት የሚያስከትለው አደጋ ከባድ ነው።
• የሐሰት ትንቢት በመናገር ለሕዝቡ የሐሰት ተስፋ ሲሰጡ የነበሩ ሁሉ ከሰሩ፤ ኤርምያስ እንደ ተናገረው ከተማይቱ ወደቀች፤ ሕዝቡም ተማረከ።
ቃሉን እንጸልይ፡-
• እውነትን በመናገር ዋጋ ለሚከፍሉ ሰዎች እንጸልይ፤ እውነት የሚያስከፍለውን ዋጋ እንድንከፍል ጸጋ እንለምን!
• እግዚአብሔርን ባለመስማት ዋጋ እንዳንከፍል እንጸልይ።
• እግዚአብሔርን በመታመን ትድግናውን እንድናይ እንጸልይ።
እግዚአብሔርን ባለመስማት ከሚመጣ አደጋ ለመዳን በጊዜ አዎንታዊ ምላሽ መስጠት ይበጃል! ጸጋ ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 34፣ 35 እና 36
ኤርምያስ 34፤ ሰዴቅያስ ታልፎ ለባቢሎን እንደሚሰጥና በሰይፍ ሳይሆን በሰላም እንደሚሞት ተነገረው፤ ባሪያዎችን ነጻ አለማውጣታቸውን ተከትሎ ኤርምያስ ያስተላለፈው መልእክት፤ እግዚአብሔር አሳልፎ ይሰጣቸዋል።
ኤርምያስ 35፤ ሬካባውያን የአባታቸውን የኢዮናዳብን ቃል በመጠበቅ፣ የወይን ጠጅ ባለመጠጣት ታማኝነታቸውን አሳዩ፤ የኢየሩሳሌም ሕዝብ ከእነርሱ አልተማረም፤ ጥፋት ያገኛቸዋል፤ ከኢዮናዳብ ወገን የሚያገለግል አይታጣም።
ኤርምያስ 36፤ ባሮክ እግዚአብሔር የተናገረውን ሁሉ ከኤርምያስ አፍ ተቀብሎ በብራና ላይ ጻፈ፤ ለሕዝቡ አነበበ፤ ኢዮአቄም የኤርምያስን ብራና አቃጠለ፤ በሌላ ብራና እንደ ገና ተጻፈ፤ ኤርምያስ በኢዮአቄም ላይ ትንቢት ተናገረ።
ከተማርኩት፡-
• ባሪያን ነጻ የማውጣት ሥርዐት አስተማሪ ነው።
• ሬካባውያን የአባታቸውን ቃል በመጠበቅ ታማኝነታቸውን እንዳሳዩ በመጥቀስ የይሁዳ ሕዝብ ግን ከእነርሱ ሊማር ፈቃደኛ አለመሆኑ የተገለጸበት መንገድ የሚገርም ነው። “… ከሬካብ ልጅ ከኢዮናዳብ ወገን የሚያገለግለኝ ሰው ለዘላለም አይታጣም።”
• እግዚአብሔር ለኤርምያስ የተናገረው ሁሉ እንዲጻፍ እና ሌሎችም ከዚህ ትምህርት እንዲያገኙ መፈለጉ አስተማሪ ነው።
• እግዚአብሔር ለነቢዩ ኤርምያስ እንደ ጸሐፊ እንዲያገለግል ባሮክን ሰጠ፤ ባሮክ ከኤርምያስ አፍ የሰማውን የእግዚአብሔርን ቃል ይጽፍ ነበር።
• ንጉሥ ኢዮአቄም ብራናውና ካቃጠለ በኋላ “ንጉሡ ኢዮአቄም በእሳት ባቃጠለው ብራና ላይ የነበረውን ቃል ሁሉ ከኤርምያስ አፍ ተቀብሎ ጻፈበት፤ ብዙ ተመሳሳይ ቃልም ተጨመረበት” የሚለው ይገርማል።
ቃሉን እንጸልይ፡-
• ከሌላው ሰው ስህተትና ውድቀት መማር እና መመለስ እንድንችል ማስተዋል እንዲበዛልን እንጸልይ።
• እግዚአብሔር በአገልግሎታችን ከጎናችን የሚቆሙ፣ በነገር ሁሉ የሚያግዙ ሰዎች እንዲሰጠን እንጸልይ።
• የእግዚአብሔር ሥራ በማንም በምንም ስለማይቆም እግዚአብሔር ይመስገን።
የእግዚአብሔር ቃል ከትውልድ እስከ ትውልድ ይነገራል፤ ማንም ሊያስቆመውም አይችልም! ጸጋው ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 31፣ 32 እና 33
ኤርምያስ 31፤ ከሰይፍ የተረፈው ሕዝብ በምድረ በዳ ሞገስን ያገኛል፤ በዘላለማዊ ፍቅሬ ወድጄሻለሁ፤ ታላቅ ሕዝብ ሆነው ይመለሳሉ፤ ራሔል አለቀሰች፤ ዐይኖችሽን ከእንባ ከልክይ፤ እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር አዲስ ቃል ኪዳን ያደርጋል፤ ከእንግዲህ ከተማይቱ አትነቀልም፤ አትፈርስም።
ኤርምያስ 32፤ ይሁዳ በባቢሎን ተከባ ነበረ፤ ሰዴቅያስ እንዴት እንዲህ ዐይነት ትንቢት ትናገራለህ በማለት ኤርምያስን አሳስሮት ነበር፤ ኤርምያስ ከአጎቱ ልጅ ከአናምኤል መሬት ገዛ፤ ውሉ ባሮክ ጋር እንዲቀመጥ ሆነ፤ ከምርኮ ተመልሰው እንደ ገና መሬት እንደሚገዙ ተነገረ፤ የኤርምያስ ጸሎትና ከእግዚአብሔር የተቀበለው መልእክት።
ኤርምያስ 33፤ ወደ እኔ ጩኽ እኔም እመልስልሃለሁ፤ ሕዝቤን እፈውሳለሁ፤ በብዙ ሰላምና በርጋታ እንዲኖሩ አደርጋለሁ፤ ኀጢአታቸውን ይቅር እላለሁ፤ የገባሁትን የተስፋ ቃል የምፈጽምበት ጊዜ ይመጣል።
ከተማርኩት፡-
• “በዘላለማዊ ፍቅር ወድጄሻለሁ፤ ስለዚህ በርኅራኄ ሳብሁሽ።”
• “ድምፅሽን ከልቅሶ፣ ዐይኖችሽንም ከእንባ ከልክይ፤ ድካምሽ ያለ ዋጋ አይቀርምና!”
• እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር ስለሚያደርገው ስለ አዲሱ ቃል ኪዳን የተናገረው ትምህርት ሰጪ ነው።
• ኤርምያስ ይሁዳ በባቢሎን ተከባ እና እርሱ በተናገረው መልእክት ምክንያት ታስሮ ሳለ ሕዝቡ ከምርኮ በኋላ ተመልሶ እንደ ገና መሬት እንደሚገዛና እንደሚሠራ ለማሳየት መሬት የገዛበት ታሪክ አስገራሚ ነው።
• የኤርምያስ ጸሎት ድንቅ ነው፤ “አቤቱ ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ ሰማያትንና ምድርን በታላቅ ኀይልህና በተዘረጋች ክንድህ ፈጥረሃል፤ የሚሳንህም አንዳች ነገር የለም፤ … ስምህ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር የሆነ ታላቅና ኀያል አምላክ ሆይ፤ ዕቅድህ ታላቅ፣ በሥራህም ብርቱ ነህ፤ ዐይኖችህ የሰው ልጆችን መንገዶች ሁሉ ያያሉ፤ ለእያንዳንዱም እንደ መንገዱና እንደ ሥራው ትከፍለዋለህ።” ምን ዐይነት አስገራሚ ጸሎት ነው?
• “ወደ እኔ ጩኽ እኔም እመልስልሃለሁ፤ አንተም የማታውቀውን ታላቅና የማይመረመር ነገር እገልጥልሃለሁ”
• “እግዚአብሔር ቸር ነውና፤ ምሕረቱም ለዘላለም ነውና፤ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔርን አመስግኑ፤ …።”
ቃሉን እንጸልይ፡-
• ወደ እግዚአብሔር እንጩኽ እርሱ የማናውቀውንና የማይመረመረውን ያደርጋልና።
• በዘላለም ፍቅሩ የወደደንን፣ ቸርና ምሕረቱ ለዘላለም የሆነውን እግዚአብሔርን እናመስግን።
• የኤርምያስን ጸሎት እንጸልይ፤ ጌታን ታላቅ፣ ኀያል፣ የሚሳነው የሌለው፣ በሥራው ብርቱ፣ ወዘተ. እንበለው።
ቸርና ምሕረቱ ለዘላለም የሆነው እግዚአብሔር አዲስ ኪዳን ከሕዝቡ ጋር ያደርጋል! ጸጋው ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 28፣ 29 እና 30
ኤርምያስ 28፤ ነቢዩ ሐናንያ በሁለት ዓመት ውስጥ የባቢሎን ቀንበር ከሕዝቡ እንደሚሰበር በመግለጽ የሐሰት ትንቢት ተናገረ፤ እርሱ የዕንጨት ቀንበር ቢሰብርም እግዚአብሔር የብረት ቀንበር እንደሚያደርግ ተናገረ፤ ሐናንያ ሕዝቡ በሐሰት እንዲታመን ስላደረገ እግዚአብሔር ከምድረ ገጽ እንደሚያስወግደው ተናገረ።
ኤርምያስ 29፤ በምርኮ ውስጥ ያሉት ሰዎች አትክልት ተክለው ፍሬውን እንዲበሉ፣ እንዲያገቡና እንዲወልዱ እና ሰባው ዓመት ከተፈጸመ በኋላ እግዚአብሔር እንደሚጎበኛቸው ተነገራቸው፤ የሐሰት ነቢያትን በመስማት እንዳይታለሉ አስጠነቀቃቸው፤ ኤርምያስ የሐሰት ትንቢት የተናገረው ሸማያ እንደሚቀጣ ተናገረ።
ኤርምያስ 30፤ የነገርሁህን ቃል ሁሉ በመጽሐፍ ጻፈው፤ እስራኤልንና ይሁዳን የምመልስበት ጊዜ ተቃርቦአል፤ ለያዕቆብ የመከራ ጊዜ ነው፤ ነገር ግን ይተርፋል፤ ምርኮን እመልሳለሁ፤ የእልልታ ድምፅ ይሰማል።
ከተማርኩት፡-
• በነቢዩ ኤርምያስ እና በሐናንያ መካከል የነበረው ትግልና ፍጥጫ በዘመኑ በእውነተኛ ነቢያትና በሐሰተኛ ነቢያት መካከል የነበረውን ሁኔታ ያሳያል። “ሐናንያ ሆይ፤ ስማ! እግዚአብሔር ሳይልክህ ይህ ሕዝብ በሐሰት እንዲታመን አድርገሃል፤ ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡- ከምድረ ገጽ አስወግድሃለሁ፤ …።”
• ነቢዩ ኤርምያስ አስቀድሞ ወደ ምርኮ የተወሰዱት ምርኮው ለሰባ ዓመት መሆኑን በመረዳት እንዲረጋጉ መልእክት ላከላቸው፤ “ለእናንተ ያለኝን ዕቅድ እኔ አውቃለሁ ይላል እግዚአብሔር፤ ዕቅዱም ፍጻሜው ያማረና ተስፋ የሚሰጥ እናንተንም የሚጠቅም እንጂ የሚጎዳ አይደለም።”
• “… በፍጹም ልባችሁም ከፈለጋችሁኝ ታገኙኛላችሁ፤ እኔም እገኝላችኋለሁ ይላል እግዚአብሔር፤ …”
• “እኔ ሳልልከው ሸማያ ትንቢት ተናግሮላችሁ፣ በሐሰት እንድትታመኑ አድርጎአችኋልና፣ … ዘሩን እቀጣለሁ፤ … የሚተርፍ ዘር አይኖረውም፤ … ለሕዝቤ የማደርገውንም መልካም ነገር አያይም።”
ቃሉን እንጸልይ፡-
• እግዚአብሔር ሳይልካቸው ሕዝቡ በሐሰት እንዲታመን የሚያደርጉትን እያሰብን እንጸልይ።
• የሚጎዳንን ሳይሆን የሚጠቅመንን የሚያስብልንን እግዚአብሔርን በመታመን መጽናት እንድንችል ጸጋ እንለምን!
• በፍጹም ልባችን እግዚአብሔርን እንፈልግ፤ በፊቱም ወድቀን ከእርሱ ጋር ኅብረት እናድርግ!
እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያለው ዕቅድ ሁልጊዜም ቢሆን መልካም እንጂ በፍጹም የሚጎዳ አይደለም! ጸጋው ይብዛልን!
የንባብ ክፍል፡- ኤርምያስ 25፣ 26 እና 27
ኤርምያስ 25፤ ኤርምያስ እና ሌሎች ነቢያትን ደጋግሞ ቢልክም አልሰሙም፤ ለባቢሎን ንጉሥ ሰባ ዓመት ይገዛሉ፤ ሰባው ዓመት ካለፈ በኋላ ባቢሎናውያን ይቀጣሉ፤ የቁጣ ጽዋ ይጠጣሉ፤ የእግዚአብሔር ቁጣ ይገለጥባቸዋል።
ኤርምያስ 26፤ ኤርምያስ ለአምልኮ ለተሰበሰቡ ሕዝብ ካልተመለሳችሁ ይህ ቤት እንደ ሴሎ ይሆናል በማለት ተናገረ፤ ተናግሮ ሲጨርስ ይዘውት መገደል አለብህ አሉት፤ ኤርምያስ በድፍረት ተናገረ፤ ሊገድሉት ቢያስቡም ተረፈ።
ኤርምያስ 27፤ የዕንጨት ቀንበር በዐንገቱ አስገብቶ ይሁዳ ለባቢሎን ታልፋ እንደምትሰጥ ተናገረ፤ ሐሰተኛ ነቢያት ይቀጣሉ፤ ሕዝቡና ዕቃዎች ሁሉ ይማረካሉ፤ በኋላ ላይ ወደዚህ ስፍራ አመጣቸዋለሁ።
ከተማርኩት፡-
• እግዚአብሔር ለሕዝቡ ደጋግሞ ቢናገርም ሕዝቡ ለመስማትና ለመመለስ ፈቃደኛ አልሆነም። ቃሉን ስላልሰሙ ለባቢሎናውያን አሳልፎ እንደሚሰጣቸውና ለሰባ ዓመታት እንደሚገዙላቸው ይናገራል። አለመስማት ውጤቱ አደገኛ ነው።
• ኤርምያስ ሕዝብ በተሰበሰበበት ስፍራ እግዚአብሔር የተናገረውን ባስተላለፈ ጊዜ ሕዝብ ሁሉ እንደ ከበበውና ሊገድሉት በእርሱ ላይ እንደ ተነሱ እናያለን። እርሱ ግን በድፍረት፣ “አሁንም መንገዳችሁንና ሥራችሁን አስተካክሉ፣ አምላካችሁ እግዚአብሔርን ታዘዙ” በማለት ከተናገረ በኋላ በእርሱ ላይ መልካምና ተገቢ መስሎ የታያቸውን ሁሉ እንዲያደርጉ ጋበዛቸው። ዋው!
• የሐሰት ነቢያት የሐሰት ትንቢት በመናገር ሕዝቡን በማሳታቸው ከእግዚአብሔር ፍርድ አያመልጡም።
ቃሉን እንጸልይ፡-
• እግዚአብሔር የሚሰማ ጆሮ እና የሚያስተውል ልብ እንዲሰጠን እንጸልይ።
• እንደ ኤርምያስ እግዚአብሔር የተናገራቸውን በድፍረት እና በትክክል የሚናገሩ አገልጋዮች እንዲበዙ እንለምን!
• በእግዚአብሔር ስም የሚነግዱ እና ሕዝቡን ከመስመር የሚያወጡ የሐሰት ነቢያትን በተመለከተ እንጸልይ።
መንገዳችን እና ሥራችን ሁልጊዜ ሊመዘን እና ሊፈተሽ ይገባል! ጸጋው ይብዛልን!
Click here to claim your Sponsored Listing.